የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ክርክር እንዳልገጥም

ላንኳኳ የምትከፍት ፣ ለሻህ የምትገኝ ፣ ለለመነህ የምትሰጥ ፣ ለተማጸነህ የምትደብቅ ፣ ለተጨነቀ የምትደርስ ፣ ለፈረሰበት የምትጠግን ተለማኝ እግዚአብሔር ሆይ ተመስገን ። ትጉሃን መላእክት ሳሉልህ እንቅልፋሙን እኔን ትቀሰቅሳለህ ፣ የተቀደሰ ሰማይ ሳለህ ወዳረከስነው ምድር ትመለከታለህ ። ሳትቸገር ሰውን ትፈልጋለህ ፣ እንኩ ለማለት ደጅ ትጠናለህ ። የተማጸኑብህን አሳልፈህ የማትሰጥ ፣ ሲጠጉህ የምትምረው ፣ ሲርቁህ ተመለሱ የምትለው አንተ ቸር ነህ ። በምድር ላይ መኖሪያ ቤትና መቀበሪያ አፈር ላጣ በሰማይ ርስት ሰፍረህ ትጠብቀዋለህ ። ፍጹም ደሀውን ፍጹም ባለጠጋ ለማድረግ ትተጋለህ ። በምድር የተበደሉትን በሰማይ ትክሳለህ ። ነፍሱ የደቀቀችበትን በምክርህ ትጠግናለህ ። ቆይ እያለ ቀጠሮ ያበዛውን ሰብረህ ትገሥጸዋለህ ።
ጻድቃን አሉኝ ብለህ ኃጥአንን አትንቅም ። አመስጋኙ ዳዊት ሳለልህ የማይረካውን ሳኦልን ትመክራለህ ። በደብርህ የጸና ሙሴ ሳለህ ከደብር በታች የሚበድልህን አሮንን ትታገሣለህ ። የመዓትህን ሰይፍ በትዕግሥትህ ሰገባ ትከተዋለህ ። ቊጣውም ምሕረቱም ያንተ ሲሆን ምሕረትህን ትናኛለህ ። አንተ ታላቅ ነህ ።
ዓይኖቼ ወደ ሞት ሸለቆ ሲመለከቱ አንተ ግን የብርሃን ተራራን ታሳያቸዋለህ ። እግሮቼ መጽናት ሲያቅታቸው አንተ ግን መርገጫውን ዓለት ታደርግላቸዋለህ ። አንደበቴ ምስጋናን ሲነጥፍ አንተ ግን የሚያስደንቅ ነገርን ታደርጋለህ ። እጆቼ ምሰሶ ሲፈልጉ እጆችህን ትዘረጋለህ ። አንድ ጊዜ አስበኝ ስልህ እልፍ ጊዜ ድል ትሰጠኛለህ ። ዝናህን የገደበ ክፉ ፣ ምስጋናህንም የጨረሰ ቅዱስ የለም ። በልደትህ ሰውና መላእክትን ያስማማህ ፣ በመስቀልህ ከጠፋው ዓለም ጋር አንተው ክሰህ የታረቅህ ፣ በትንሣኤህ የድል ሠራዊት ያደረግኸን አንተ ነህ ። ምስጋናችንን ከወደድከው እንካ ተቀበለው ።
የፍቅርህ ብርሃን ልቡናዬን ያብራው ። ልመናዬም በፊትህ ሞገስ ያግኝ ። የደስተኞች ደስታ ያስደስተኝ ። የመልካሞች ሩጫ ያስፈንድቀኝ ። መልካም ዜናን ለመስማት ልቡናዬን አዘጋጅልኝ ። ሰባሪ ቀኖችን ለማለፍ ኃይል ስጠኝ ። የምክርህ ጠል ያረስርሰኝ ። ትምህርትህ በእውቀት ያንጸኝ ። ያማረ አነጋገር ፣ የተወደደ አንደበት ስጠኝ ። የተቀበልሁ ነኝና ለመስጠት እንዳልፈተን እርዳኝ ። ከትልቁ ጌታ ካንተ ጋር ክርክር እንዳልገጥም ማስተዋል ስጠኝ ። ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና /3
የካቲት 17 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ