የትምህርቱ ርዕስ | ወርቀ ደሙ

“በውድ ልጁም ፥ እንደ ጸጋው ባለ ጠግነት መጠን ፥ በደሙ የተደረገ ቤዛነታችንን አገኘን እርሱም የበደላችን ስርየት ። ጸጋውንም በጥበብና በአእምሮ ሁሉ አበዛልን ።” ኤፌ. 1 ፡ 7-8 ።

እግዚአብሔር የጸጋ አምላክ ነው ። ጸጋውም ባለጠጋ ነው ። እግዚአብሔር አለ ፣ ጸጋው አለ ፣ የጸጋው ባለጠግነት ደግሞ አለ ። እግዚአብሔር የነገር ሁሉ ሥር መሠረት ፣ ጅማሬ ሳይኖረው ሁሉን ያስጀመረ ነው ። ጸጋው ሥጋና ነፍሳችንን ያገኘንበት ፣ ተበላሽተን እንደገና የተሠራንበት አምላካዊ መግቦት ነው ። የጸጋው ባለጠግነትም መንፈስ ቅዱስን የተቀበልንበት ፣ የአገልግሎት ስጦታዎችን ያገኘንበት ፣ ቤተ ክርስቲያንን /መንፈሳዊ ቤተሰብን ያተረፍንበት ፣ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬና ስጦታዎችን ያገኘንበት ፣ ተቆጥሮ በማያልቅ ፣ በሰፊ እጅ የተሰፈረ መኖሪያችን ነው ። በምድር ላይ ባለጠጋ ተብለው የሚጠሩ አሉ ። እውነተኛው ባለጠጋ ግን ጸጋ መንፈስ ቅዱስን የተቀበሉ ናቸው ። በምድር ላይ ሦስት ነገሮች ገዥዎች ናቸው ። እውቀት ፣ ሥልጣንና ሀብት ። እውነተኛው እውቀት እግዚአብሔርን ማወቅ ነው ፣ ከመንግሥት ሥልጣንም የክህነት ሥልጣን ይበልጣል ። ሀብተ መንፈስ ቅዱስም ከቁሳቁስ ይልቃል ። እግዚአብሔርን በማወቅ ውስጥ ራስን መግዛት አለ ። በአገልግሎት ውስጥም የጨለማውን ኃይል ማሸነፊያ ሥልጣን አለ ። መንፈሳዊ በረከትም ሰጥተን የማያልቅብን ብዙ ሀብት ነው ። ስለዚህ ምእመናን ገዥዎች ናቸው ። እውቀት ፣ ሥልጣንና ሀብት አላቸውና ።

ባለጠጋ ተብሎ የሚጠራ ሰውን እናስታውስ ። ቤት ንብረት ያለው ሰው ባለጠጋ ይባላል ። ባለጠጋ መባሉ የተሰጠው እንጂ የባሕርይ ገንዘቡ አይደለም ማለት ነው ። በእውነትም ዕራቁቱን ወደ ምድር መጥቶ ዕራቁቱን ይመለሳል ። የትላንት ባለጠጎች የዛሬ ድሆች ናቸው ። የዛሬ ድሆችም የነገ ባለጠጎች ናቸው ። የተራ ዓለም እንጂ ቋሚ ዓለም አይደለም ። ተረኛ ባለጠጋ ፣ ተረኛ ትልቅ ሰው ይታያል ። ተራው ሲያበቃ ለቀጣዩ ጥሎ ይሄዳል ። ሲያጣውም ይገባኛል ብሎ አይከራከርም ። ዓለም የእኔ የማትባል ናት ። ሲገዙና ሲነዱ የነበሩ በእስር ቤት ፣ በስደት ዘመናቸውን ሲገፉ ይገባኛል ብለው ግን ሲካሰሱ አይታዩም ። በሕይወት መኖራቸውንም እንደ ዕድል ቆጥረውት ታሪካቸው የልጆች ማሳደጊያ ተረት ይሆናል ። የነበራቸው ሁሉ የባሕርይ ገንዘባቸው ሳይሆን የመንገድ ስንቃቸው ነበር ። ሰው ስንቁን ሊጨርስ ይችላል ፣ ጣቶቹን ግን አይጨርስም ። ቤቱን ትቶ ይሰደዳል ፣ ኩላሊቱን ትቶ ግን አይሰደድም ። የባሕርይ ገንዘብ ከህልውናው ጋር የሚኖር ነው ። ገንዘብ የመንገድ ስንቅ ነው ። ሀብታምነትም ለጊዜው ነው ፣ እውነተኛ ሀብት ክርስቶስ ብቻ ነው ። ይዘው ሲገኙ እንጂ ነበረኝ ቢሉ ማንም አያምንም ። ዓለም ስትሄድ አሻራ እንኳ ሳትተው ነው ። ሲረታ የማያውቅ ሞኝ ፖለቲከኛ ነው ።

እግዚአብሔር የሥጋና የነፍስ ባለቤት ነው ። ሆድን ፈጥሮ እንጀራን አይነሣም ። ነፍስንም ፈጥሯልና ቃሉን ይልካል ። በመግቦቱ አድልኦ የሌለው ሥጋና ነፍስን ፈጥሮ የሚያኖር ነው ። እውነተኛው ባለጠግነት ግን ሀብተ መንፈስ ቅዱስ ነው ። ሰባኪው ደሀ ቢሆን ፣ ካህኑ ምስኪን ቢሆን ትልቁን ሀብት ግን ይዘዋል ። ናኝተውት የማያልቅ ሀብት ፣ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ነው ።

ጸጋው መዳናችን ነው ። በዚህ ውስጥ ብዙ ሀብታት አሉ ። መንፈስ ቅዱስ ባይተዋርነት እንዳይሰማን ወደ እኛ የመጣው ድኅነት በመፈጸሙ ነው ። የሙት ልጅ ስሜት እጓለማውታነት እንዳያሰቃየን መንፈስ ቅዱስ ከእኛ ጋር ነው ። እርሱ በበረሃ የተገኘ የሕይወት ምንጭ ነው ። ቤተ ክርስቲያንም የጸጋው ባለጠግነት መገለጫ ናት ። በቤተ ክርስቲያን ሰዎች በየዕለቱ ከነፍስ እስራት ይፈታሉ ። ዓለም ሁሉ የኰነነው በቤተ ክርስቲያን ግን ጸሎተ ንስሐ ይደገምለታል ። ብቻዬን ነኝ ለሚለው ብዙ ወንድሞችና እኅቶችን በቤተ ክርስቲያን ያገኛል ። እንደ ክርስቶስ የሚያዛምድ የለም ። ይህ መንፈሳዊ ዝምድና ቀሎባቸው ወንድም እኅቶችን የሚገፉ ወዮላቸው ።

“በደሙ የተደረገ ቤዛነታችንን አገኘን” ይላል ። ቤዛ ክፍያ ከሆነ የተከፈለው ደግሞ ደሙ ነው ። የደም ክፍያ በየዘመናቱ አለ ። የደም ክፍያ ለአገር ፣ ለህልውና ይከፈላል ። ክርስቶስም የገዛን በብር ሳይሆን በንጹሕ ደሙ ነው ። አንድ ወርቅን እናስታውስ፡- ይህ ወርቅ በነጋዴ እጅ ሳለ ተወልውሎ በመስተዋት ይቀመጣል ። በገዥው እጅ ግን የአካሉ ዘመድ ሁኖ ፀሐይና ዝናብ እየተፈራረቀበት ይኖራል ። ነጋዴው ቢወለውለው ሊሸጠው ነው ፣ የማለዳ ጸሎቱም “ከእጄ በወጣልኝ” የሚል ነው ። ወርቁን ሳይሆን ወርቁ የሚያስገኘውን ነገር ይፈልጋል ። ስለዚህም ከማይወደው ጋር ያ ወርቅ ተወልውሎ ይኖራል ። ገዥው ግን አብሮት ቢጎሳቆልም ጌጡ ፣ የቃል ኪዳን ምልክቱ ፣ የስጦታ ልኩ አድርጎ ይይዘዋል ። ለመታጠብ ሲያወልቀው ለደቂቃ እንኳ አያምነውም ። ወርቅ ይሰለባልና አታውጡት የሚባለው ከመሰሰት የተነሣ ነው ። ይህ ወርቅ ፀሐይና ዝናብ ቢፈራረቅበትም የሚኖረው ከሚወደው ጋር ነው ። እኛም ከሚሸጡን ጋር በዓለም ተወልውለን ፣ በውዳሴ ከንቱ አንቱ ተብለን ኖረናል ። ምነው በሄደልን እያሉን በፊት ለፊታችን ግን አትለየን ከሚሉን ጋር ፣ የእኛ ሳይሆን የእሴታችን አፍቃሪዎች ከሆኑ ጋር አሳልፈናል ። የገዛን ክርስቶስ ግን ፀሐይና ዝናብ ቢኖረውም በእውነት ይወደናል ። እርሱ አካሉ አድርጎናል ። “አልለቅህም ከቶም አልተውህም” በሚል ኪዳን ይዞናል ።

በደሙ ዋጋነት ፣ በቤዛነቱ ደረሰኝ የተቀበልነው የኃጢአታችንን ስርየት ነው ። ብዙ ሰው በሱስ ውስጥ የሚኖረው ስርየትን ስላላገኘ ለመርሳት ብሎ ነው ። ስርየት በመጠጥም ፣ በወርቅም አይገኝም ። በወርቀ ደሙ ዋጅቶ ፣ የነፍስ ዕረፍት የሰጠን ጌታ ስሙ ቡሩክ ቅዱስ ይሁን ። አሜን ! የሚሰማ ሁሉ አሜን ይበል !

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /15

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 26 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም