መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ወደምንኖርባት ከተማ

የትምህርቱ ርዕስ | ወደምንኖርባት ከተማ

በሁከት ውስጥ ጸጥታ ፣ በጦርነት ውስጥ ሰላም ፣ በመክነፍ ውስጥ ጽሞና ፣ በሽብር ውስጥ መረጋጋት ፣ በድንጋጤ ውስጥ ብርታት ፣ በኀዘን ውስጥ ደስታ ፣ በጥዝጣዜ ውስጥ ዕረፍት ፣ በኑሮ ውስጥ ክብረት ፣ በሞት ውስጥ ሕይወት የምትሰጥ የዓለሙ ፈጣሪ ፣ የዘላለሙ ቅዱስ አንተ ነህ ። ሁሉን አውቃለሁ የሚል ትውልድ ፣ ሁሉም የእኔ ነው የሚል ወገን ፣ ሁሉ ሞቶ እኔ ልኑር የሚል ሕዝብ ፣ ሁሉም ከንቱ ነው ከእኔ ውጭ የሚል ፖለቲከኛ ፣ ሁሉም ፈሪ ነው የሚል የተደበቀ አዋጊ በበዛበት ዘመን ፤ እኛ ስንናገር ያንተን ድምፅ መስማት አቅቶን  ፣ የራሳችንን መንገድ ስንከተል ካንተ መንገድ ወጥተን አንተ ግን በትዕግሥት ታየናለህ ። የሚያስጨንቀው እያሳቀን ፣ ባልበደልነው መናዘዝ ሲያምረን ፣ ግብዝነት መሬት ጥሎን ስንንፈራፈር ፣ ለእግዚአብሔር ነገ ለገንዘብ አሁን ስንል ፣ የሰማነውን መቋቋም አቅቶን ሌላ ለመስማት ስንፋጠን ፣ ከዓይናችን መጠን በላይ አይተን ሌላ ለማየት ስንንቀዠቀዥ እያየኸን ዝም ብለሃል ። ጌታ ሆይ ወደ ልባችን ስንመለስ ሰላም እንልሃለን ።
ሽማግሌዎች ብላቴና ለመሆን ሲያምራቸው ፣ ወጣቶች የቤትህን ትቢያ ሲልሱ ፣ ሕፃናት ያወቁ መስሎአቸው ሁሉንም ሲታዘቡ ፣ የሙት ልጆች እያሉ ሌላ ትውልድ ሲያምረን ፣ የጠራነውን ሳናስተዳድር ሌላ ሲናፍቀን አንተ ታየናለህ ። እንቢ ስንልህ ዛሬም ትጠብቀናለህ ። የወሬ ነፋስ ቤታችንን ሲነቅለው ፣ የሐሜት ማዕበል አገራችንን ሲያፈርሰው ፣ መለያየት ቤተ ክርስቲያንን ሲያሳንሳት እያየህ ነው ። ለፍላጎታችን አትተወን ። ጥንስሱ እንዲህ ያሰከረን መጠጡ እንዴት ሊያደርገን ነው ? እባክህ መልሰን ። የተቀበለንን ወዳጅ ስንገፋ ፣ አገር ያላመደንን አገር ስናሳጣ ፣ የፈረደልን ላይ ስንፈርድበት ፣ የሸፈነንን ስንገልጥ ፣ የሾመንን አርባ ስንገርፍ እያየኸን ነው ። ጠላትን አይደለም ወዳጅን መውደድ አቅቶን ፣ ወርቅ ላበደረን ጠጠር እየመለስን ነው ። አዎ እያየኸን ነው ። የምንሠራውን እናውቀው ዘንድ እርዳን ።
ለነቢያት የትንቢትን መንፈስ የሰጠህ ፣ በመምጣትህ ዜና ሕዝብህን ያረጋጋህ ዛሬም እመጣለሁ ብለህ አረጋጋን ። ያንተ መልእክተኞች እያነሱ ሰው ሠራሽ ሰባክያን እየበዙ እንዳይመጡ እባክህ እርዳን ። ሁሉም ነገር ጥያቄ ሲሆንብን የሁሉም ነገር መልስ እኔ ነኝ በለን ። ድምፅህን ነፍሳችን ታውቀዋለች ። በልብ ስትናገራት ትሰማሃለች ። ማዕበሉን ስትገሥጽ ማዕበሉም ላንተ ቃል ጆሮ አለው ። ነፋሳት የሚገዙልህ የሚናወጠውን መርከብ ጸጥ አድርገው ። ነገሬ አይሰማም ፣ ቃሌ ክብር አላገኘም ለሚለው ወዳንተ ቢጸልይ እንደምትሰማው አሳውቀው ። ወደማይሰሙን የጮህንበት ዘመን ያብቃና ወደምትሰማን መጸለይ ይሁንልን ። ወደማይሰሙን ነገሥታትና አለቆች የጮህንበት ዘመን ይብቃና ወደ ዘላለሙ ንጉሥ መጮህን አስተምረን ። የክለሳ ኑሮ ሲያደክመን ፣ የረገጥነውን መልሰን ስንረግጥ ፣ የበረሃ አዙሪት ሲገጥመን ፣ የተፋነውን ዳግም ስንልስ እባክህ መንገዱን አሳየን ። ወደምንኖርባት ከተማ በሰላም ፣ በቶሎ አድርሰን ።
ብዙ ዘርቶ ጥቂት አለማጨድ ፣ ብዙ ወድዶ ምንም አለመወደድ ፣ ብዙ ሠርቶ ትንሽ አለመመስገን ፣ ብዙ ሰጥቶ ብዙ መሰደብ የገረመው ትውልድ አለና ሰው አደባባዩን ሲያይ አንተ ግን ወደ ጓዳዎች ተመልከት ። አዋቂና ሰላምን ሰደን ከማሳደድ እባክህ ጠብቀን ። ስምህ ቡሩክ ይሁን ፣ የማይጠገብ ዝማሬ ለውለታህ ይቅረብ ። ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና /6
የካቲት 21 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም