መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ወደ ሰማይ ልውጣ

የትምህርቱ ርዕስ | ወደ ሰማይ ልውጣ

 የማያምን ሰው ጠፈረ ሰማይን ያያል ፣ የሚያምን ግን ከሰማዩ በላይ ያለውን ዙፋንህን ያያል ። አንተም የተሰወርህ ስትሆን ለምትወደው ግን ራስህን ትገልጣለህ ። ለሚሻህ የጌትነትህን ምሥጢር ታብራራለህ ። የኪሩቤል ሠረገላ አንተን አይችልህም ። በሰማይ ትኖራለህ ብንልም ስለ ልዕልናህ ለመናገር እንጂ ሰማይ ወስኖህ አይደለም ። የኃጢአተኛው ኃጢአት አያረክስህም ። በሽተኞችን አትሸሽም ። የደካማው ድካም አይገርምህም ። የድሀው ልመና አያሰለችህም ። በርህን የሚያንኳኳ አይረብሽህም ። ተራዬ መቼ ነው ? የሚሉህ አያበሳጩህም ። ከገናኖች በላይ ገናና ነህ ። ከልዑላንም በላይ ልዑል ነህ ። ያልተቀበልህ ባለጠጋ አንተ ነህ ። ያልተቸርክም ቸር አንተ ብቻ ነህ ። በሰማይ ሠራዊት ፣ በምድር አማንያን ፣ በሞቱትና በሕይወት ባሉት አንደበት ትመሰገናለህ ። አዳራሽህ እልፍኝ ነው ፤ እልፍኝህም አዳራሽ ነው ።ለሚያምኑህ እልፍኝህ አዳራሽ ነው ፤ የተገለጠ እንጂ የተሰወረ ነገር የለህም ። ለማያምኑህ ግን አዳራሽህ እልፍኝ ነው ። የተገለጠው ቃልህ እንኳ ስውር ይሆንባቸዋል ።
እመጣለሁ ትላለህ መቼ እንደምትመጣ የሚያውቅ ማንም የለም ። ስለ ዘመኑ እንጂ ስለ ቀኑ ከቅዱሳንህም ሰውረሃል ። በመሰወርም ትባርካለህ ። ቀኑን ብናውቀው ከቀኑ በፊት እንሞት ነበረ ። በአቅማችን ልክ ያስተማርከን አንተ ነህ ። ክብርህን የዘመረ ፣ ምስጋናህን አሟልቶ ያቀረበ ማንም የለም ። ትጉሃን ከትጋታቸው በላይ ትሆንባቸዋለህ ። ምስጋናህን ባይፈጽሙትም መርካትን ግን አትከለክላቸውም ። አንተ በመታወቅም ታስደንቃለህ ፣ ባለ መታወቅም ታስደንቃለህ ። ውለታህ እንቅልፍ የለሽ ያደረጋቸው ብዙ ቅዱሳን አሉህ ። እኔ ግን ጭቃ እያላቆጥሁ ፣ መሬት ለመሬት እሳባለሁ ። የደመናውን መጋረጃ ፣ የሰማዩን መንጦላዕት ገልጬ ፣ የማይጠቀለለውን ሥላሴነትህን ፣ የማይከፈለውን መለኮትህን ላመሰግን ገና ነኝ ። እባክህን ከምስጋናሀ በዓል ላይ አድርሰኝ ። በዓል ሁኖ ለዘላለም ይኑር ። ከሙሽርነት በኋላ ወደ ትግል አልግባ ። ባንተ ደስ እንዳለኝ ልቅር ። ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና/12
መጋቢት 3 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም