የትምህርቱ ርዕስ | ወዳጄ ሆይ

ቁመህ ስትሄድ የተቀመጡ ሰዎች ይተቹሃል ። የማይሠሩ እጆች ያሏቸው የሚሠሩ አፎች አሏቸው ። የሚሮጥ መስመሩን ያያል ፣ የተቀመጠ ዙሪያውን ያማትራል ። አንድ ብቻዬን ነኝ ምን ይመጣብኛል አትበል  ፤ መከራ የመጣ ቀን አንድ ራስህ ከሚሊየን በላይ ያስጨንቅሃል ። ጠቃሚዎችህን ስታመሰግን ያልጠቀሙህ የመሰሉህን አትርገም ። ለሺህዎች እየተናገርህ ለአንድ ሰው መልእክት አታስተላልፍ ፣ አሽሙር የሚባለው ይህ ነውና ። አሽሙር ለማይሰማ ሰው የሚሰሙትን ልቦች ማደፍረስ ነው ። ያልመሰለህ ነገር ያልሆነ ነገር አይደለም ፣ ድርጊትን በስሜትህ አትለካው ። ዋሽተህ ከመከበብ እውነት ተናግረህ በዱር ማደር ይሻላል ። በዓለም ላይ ትልቁ ቅዠት ዓለምን የግልህ ለማድረግ ያሰብህ ቀን ነው ። ትልቅ መሳሳት ሁሉ ይወደኛል ብሎ ማሰብ ነው ። ትልቅ ድፍረት ሁሉን አውቃለሁ ብሎ መፎከር ነው ። ትልቅ ውድቀት አዋቂን ትቶ ከቢጤ መምከር ነው ።
ወዳጄ ሆይ
ጽጌረዳ ከእርሷ የሚበልጡ እሾሆች አሉባት ፣ አንተም ጠላቶቼ በዙ ብለህ አትደንግጥ ። ብርቱካን ጣፋጭ ነው ፣ ቆዳው ግን መራራ ነው ፣ የምትወዳቸው ሰዎችም በአስቸጋሪ ሰዎች መካከል ይኖራሉ ። አንድ ነገርን በሚያስገኘው ጥቅም ከለካኸው ነጋዴ ነህ ፣ በሚያመጣው ዝና ከተመንከው ቲያትረኛ ነህ ። አስመሳዮች የውሸት አልቅሰው የእውነት የሚያስለቅሱ ናቸው ።
ወዳጄ ሆይ
ሰዎች የሚወዱህ ስለወደድሃቸው ነው ፤ የሚርዱልህ ግን ስላስደነበርካቸው ነው ። የሥጋ በሽታ ፈውስን ሲፈልግ የነፍስ በሽታ ግን የበለጠ በሽታ ላይ ይውላል ። ማብረጃው የማይሠራ መኪና የሚያምርበት ሲሄድ ሳይሆን ሲቆም ነው ። ለስልሶ መናደፍ እባብነት ነው ። ሁለንተናው የማይመች ሰው ጊንጥ ነው ። ሁሉ በሽተኛ ከሆነ ሐኪም ፣ ሁሉ ተናጋሪ ከሆነ አድማጭ ፣ ሁሉ ዘማች ከሆነ አዝማች ፣ ሁሉ መሪ ከሆነ ተመሪ ሊጠፋ ነው ። የትላንት ሕመም ዛሬ ላይ እንዳይደገም ጥንቃቄ ጠባቂ ነው ። ማመስገን ባለ ዕዳነትን ማውረድ ነው ። የታሠረ ሰው ሲሄድ የሚደርስ ይመስለዋል ። ፍቅርን ወደ ኋላ የጣለና የገፋ ወደፊት አያገኘውም ። መገኘት ማለት መኖር አይደለም ፣ ድንጋይ ዕድሜው ከእኛ ቢበልጥም እየኖረ አይደለም ። ሰውን ስለ ልብሱ እንጂ ስለ ልቡ አስተያየት አትስጥ ፤ ልቡን የሚያውቀው እግዚአብሔር ነውና።
ወዳጄ ሆይ
ቃል የሰበረውን መረቅ አይጠግነውም ፤ እጅ የሰበረውን ግን ቃል ይጠግነዋል ። ሰዎች እንዲያውቁህ የምታደርገው ጥረት ባለማወቅ ይደመደማል ። ደም ስታፈስ የልጅ ልጆችህ የሚከፍሉትን ዕዳ ታኖራለህ ። እውቀትን እንጂ ደምን የሚያወርስ ባይወልድ ይሻለዋል ። እንባ አምላክ እንዳለው አትርሳ ። እንባ ሲወርድ ውኃ ፣ ሲመለስ እሳት ነው ፤ እንባ ሲወርድ ይበርዳል ፣ ያረፈበትን ግን ያቃጥለዋልና ሰዎች እንዳያለቅሱብህ ፍራ ።
ወዳጄ ሆይ
የቀኑ ትኩሳት ለፍላፊ አያድርግህ ፣ “ጊዜ የሰጠው ዘፈን እንቅርት ያፈርጣል” የተባለውን አትርሳ ። ኃጢአቴ በዛ ፣ ጽድቄ አነሰ የሚል ጠፍቶ ጽድቄ በዛ ፣ ኃጢአቴ አነሰ የሚል ትውልድ ምንነቱ ባልታወቀ ደዌ ይማስናል ። የሌላውን ቤት የሚያፈርስ የእርሱ ቤት ነገ እንዲፈርስ ሰይፍ ያቀብላል ።  ባለቀው ነገር አትዘን እርሱን ለመጨረስ ዕድሜ የሰጠህን ጌታ አመስግን ። ጭር ባለው መንገድ መሄድ ስትፈራ የሚርመሰመሰው ሰውም ጠቃሚህ እንደሆነ ተረዳ ። ሰይፍ በሰገባው ይያዛል ፣ እግዚአብሔር በሰጠው ኪዳን ይለመናል ።
ምክር /24
ጥቅምት 22 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም