የትምህርቱ ርዕስ | ዋጋ አለኝ

“በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ።” 1ጴጥ. 1፡19 ።
የአሜሪካው ፕሬዝዳንት የነበሩት ቶማስ ጃፈርሰን “ፕሬስ ከሌላት አገር” ወይም “አገር ከሌለው ፕሬስ” የቱን ትመርጣለህ ? ተብዬ ብጠየቅ ሳላመነታ የምመርጠው ነገር ቢኖር ሁለተኛውን ነው ካሉ በኋላ፡- “ፕሬስ ከሌለው አገር ፣ አገር የሌለው ፕሬስ ይሻላል” ብለዋል ። መንግሥት ያለ ፕሬስ ራሱን ማየት አይችልም ፣ ያለ ጋዜጠኞች ሊቆም አይችልም ማለት ነው ። ጋዜጠኝነት ሙያው ሲከበር ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ ነው ፣ ሙያው ሲቀል ደግሞ ነፍስን እየሸጡ መኖር ነው ።
ሰይጣንም ራሱን የሚያየው እንደ ጨለማው መንግሥት ነውና የራሱ ፕሬስ አለው ። የሰይጣን ፕሬስ ክፋት የሞላበት ወሬ ነው ። በዚህ ዓለም ስንኖር ከውስጣችን የምንሰማው ድምፅ አለ ። በዙሪያችንም የከበበን ወሬ አለ ። ሰይጣን ሰዎችን የሚዋጋባቸው ዋነኛ ነገሮች በውስጣችን ድምፅ በማሰማትና በዙሪያችን ወሬን በማራገብ ነው ። ሰይጣን ታላላቅ ውድመት የማድረግ ሥልጣን ቢሰጠው የሚያስቀረው ነገር ቢኖር ወረኞችን ነው ። ያለ ወረኞች ሰይጣን ግቡን መምታት አይችልም ። ሰይጣን በኢዮብ ላይ ብዙ ውድመት እንዳደረሰ መጽሐፍ ይነግረናል ። ብላቴናዎች ሁሉ ሲያልቁ አንዱ ግን ተረፈ ። ወደ ኢዮብም መጣ፡- እኔም እነግርህ ዘንድ ብቻዬን አመለጥሁ አለው።” ኢዮ. 1፡15 ። በዚህ የሰይጣን ጥፋት ለኢዮብ ወሬውን የሚያቀብል አንድ ሰው አልተነካም ። እሳት ከሰማይ ወድቃ በጎቹንና እረኞቹን ስትፈጅ አንዱ ወረኛ ግን አልተነካም ። ወደ ኢዮብ ዘንድ መጥቶ፡- እኔም እነግርህ ዘንድ ብቻዬን አመለጥሁ አለው።” የሚያስፈልጉት ብዙ አይደሉም ፣ አንድ ወረኛ በቂ ነው ። ከእሳቱ በላይ ጻድቁን በወሬ እፈታዋለሁ ብሎ ሰይጣን አሰበ ። በግመሎች ላይ አደጋ ሲደርስም አንዱ ወሬ ነጋሪ ተረፈ ። ወደ ኢዮብም መጥቶ፡- እኔም እነግርህ ዘንድ ብቻዬን አመለጥሁ አለው።” ኢዮብ. 1፡17 ። ሰይጣን ዋነኛ አሳቡ የኢዮብን ንብረት ማፍረስ ሳይሆን እምነቱን መናድ ነው ። እምነትን ከሚጎዱ ነገሮች አንዱ ወሬ ነው ። የኢዮብ ልጆች በዐውሎ ነፋስ በተገደሉ ጊዜ አሁንም አንድ ወሬኛ ተረፈ ። እርሱም ለኢዮብ፡- እኔም እነግርህ ዘንድ ብቻዬን አመለጥሁ አለው።” ኢዮብ . 1፡19 ። ኢዮብ ግን ያሸነፈው ወሬውን ባለማዳነቅ ነው ። ኢዮብ እነዚህ ሁሉ ነገሮች አንድ ዘመን አልነበሩትም ነበር ። ከሀብትም ፣ ከአሽከርም ፣ ከልጆችም በፊት ግን እግዚአብሔር ነበረ ። ከቀን በኋላ በመጣ ነገር አምላኬን አላማርርም አለ ። ራቁቴን ከእናቴ ማኅፀን ወጥቻለሁ ፥ ራቁቴንም ወደዚያ እመለሳለሁ እግዚአብሔር ሰጠ ፥ እግዚአብሔርም ነሣ የእግዚአብሔር ስም የተባረከ ይሁን ።” ኢዮብ . 1፡21 ።
ሰይጣን አማረልኝ ብሎ አስቀድሞ የተናገረው ነገር ነበር ። ምድርን ሁሉ ዞርሁአት” ኢዮብ . 1፡7 ። ሰይጣን ዘዋሪ ነው ። ሥራ ፈትና ምድርን ሁሉ ሲዞር የሚውል ነው ። ዘዋሪ ደግሞ ወረኛ ነው ። ስለዚህ ሰይጣን በየትኛውም ዘመን እንዳይጠፋ የሚንከባከበው አረም ቢኖር ወሬ ነው ። ወሬ ድንጋጤ ያመጣል ፣ የሰውን ተስፋ ይመታል ፣ ጅምሮች እንዳይቀጥሉ ያደርጋል ። የተሰለፈን ጦር ይበትናል ፣ ንጹሕ ልብን ያቆሽሻል ፣ የፍቅር እይታን ይለውጣል ፣ ኅብረትን ያፈርሳል ። ወሬ የሰይጣን ትልቅ መሳሪያ ነው ። ወሬን የምናሸንፈው በእግዚአብሔር ቃል ነው ። ወሬ እንደ ሰይጣን ሥራ ፈትና ዘዋሪ ያደርጋል ። ወሬ ሰላምን ያውካል ።
በውስጣችን ከምንሰማቸው ድምፆች ፣ ሰይጣን በወሬኞች ከሚያሰማን አሉታዊ ንግግሮች አንዱ ዋጋ የለህም የሚል ነው ። ዋጋ የለህም የሚል ድምፅ በደረቁም ይመጣል ፣ ተቀባብቶም ይመጣል ። ሰው የመኖር አምሮቱ የሚጨምረው ለራሱ ዋጋ እንዳለው መንገር ሲችል ብቻ ነው ። ሰዎች ወደቀ ሲባል ተሰበረ ብለው ማውራታቸው ፣ በግነት ሰይጣንን ማገልገላቸው ፣ ክፉውን ነገር መደጋገማቸው እርግጥ ነው ። ይህንን ድምፅ ግን ልናስተውለው ይገባል ። ወሬ የሰይጣን ትልቅ የፕሬስ ድርጅት ነው ። ብዙ ሰዎች ሳያውቁት በዚህ ድርጅት ውስጥ ያለ ደመወዝ ይሠራሉ ። ሰይጣን ያለው ሀብት ገሀነመ እሳት በመሆኑ ያንን እንዳያካፍላቸው መፍራት ይገባቸዋል ።
ዋጋ የለህም ለሚለው ድምፅና ወሬ ሐዋርያው ጴጥሮስ መልስ ይሰጣል ። “በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ” ይላል ። ዋጋ የለህም የሚለውን ድምፅ የሚያመጣው አለማወቅ ነው ። ስናውቅ ግን በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተገዛን እንረዳለን ። መዋጀት ማለት በዋጋ መግዛት ማለት ነው ። በዚህ ዓለም ላይ ብዙ የመግዣ ገንዘቦች እንዳሉ ሐዋርያው ጠቅሷል ። እነዚህም በዋናነት ሦስት ናቸው ፡-
1-  ብርና ወርቅ
2-  እንስሳት
3-  ደም
የብርና የወርቅ ክፍያ ለሚገዛው ነገር የሚመጥነውን በመክፈል መውሰድ ነው። የእንስሳት ክፍያ ለካሣ አንዳንድ ጊዜ በልዋጭ የሚገበያዩበት ነው ። የደም ክፍያ ግን ለአገር ለወገን የሚከፈል የታላቅ ፍቅር መግለጫ ነው ። በደም ዋጋ የተገኘ ነገርም በቀላሉ የሚሰጥ አይደለም ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የገዛን በብርና በወርቅ አይደለም ። በወርቀ ደሙ ገዝቶናል ። በእንስሳት መሥዋዕትነት ሳይሆን ውድ ነፍሱን በመስጠቱ አድኖናል ። ስለዚህም ተገዝተናል ። የተገዛ ነገር፡-
1-  ባለቤት አለው ። የሚቆረቆርለት ፣ የሚዋጋለት ባለቤት ያለው ነገር ቢኖር የተገዛ ብቻ ነው ። እኛም በክቡር የክርስቶስ ደም የተገዛን ነንና ባለቤት አለን ። ባለቤታችንም ክርስቶስ ነው ። እርሱ ስለ እኛ ይቆረቆራል ፣ እርሱ ስለ እኛ ይዋጋል ።
 
2-  ዋጋ አለው ። የተገዛ ነገር ዋጋ አለው ። ዋጋ የከፈለለት ወገንም አለው ። የተገዛው ነገር የራሱንም ዋጋ አያውቅም ፣ የገዛው ብቻ ያውቃል ። ገዢው ብዙ ድካሙን አፍስሶ ይገዛዋል ። ክርስቶስም ከሊቶስጥራ እስከ ቀራንዮ መስቀል ተሸክሞ በደሙ ገዝቶናል ። ዋጋችንም እግዚአብሔር ነው ። ዋጋ የለኝም ማለት ክርስቶስ የለኝም ማለት ነው ።
3-   አፍቃሪ አለው ። ነጋዴው ከቤቱ ሲወጣ ያ ዕቃ ዛሬ ከእጄ በወጣልኝ በማለት ነው ። ገዥው ደግሞ በእጄ ባስገባልኝ በማለት ነው ። ነጋዴው መገላገል ሲፈልግ ገዥው ደግሞ ይዞ መግባት ይፈልጋል ። ያልወደደውን የሚገዛ የለም ። የገዛን ጌታም ይወደናል ።
4-   ጥበቃ አለው ። የተገዛ ነገር ገዥው ነፍሱን ከፍሎ ይጠብቀዋል ። ሌባ ቢመጣ ተናንቆ ያስጥለዋል ። ተገዝተናልና እኛም አምላካዊ ጥበቃ አለን ።
5-   ማስቀመጫ አለው ። የተገዛ ነገር የሚቀመጥበት ስፍራ አለው ። እኛም ተገዝተናልና ቤተ ክርስቲያን መኖሪያችን ናት ።
6-   ለገዛው ይኖራል ። የተገዛ ነገር ከመገዛቱ በፊት ተቀባብቶ የተቀመጠ ነበር ። ከተገዛ በኋላ ግን ያገለግላል ። ሲቆሽሽ ይታጠባል ። ቀባብቶ ቢያስቀምጠው ነጋዴው እንዲሄድለት ይፈልጋል ። ቢቆሽሽና ቢያገለግልም ገዥው ግን ይወደዋል ። ብንደክም ፣ ብንዝልም የሚወደን አለ ።
7-   የተገዛው ለአገልግሎት ነው ። እኛም በክርስቶስ ሞት የዳነው ወይም የተዋጀነው ለማገልገል ነው ። እርሱ ሲገዛን ካልሳሳ ፣ ለማገልገልም መሳሳት የለብንም ። 
ጌታችን የገዛው ሙት የሆነውን ይህንን ማንነት ነው ። ወደ ሞት እየሄዱ ላሉ ሰዎች ደም መስጠት ሕይወት መስጠት ነው ። ክርስቶስም ደሙን አፍስሶ ሕይወትን ሰጥቶናል ። እኛ ገዥ ብንሆን ኑሮ ይህን ማንነት አንገዛውም ነበር ። መቃብርን ልደት ማድረግ የሚችል ጌታ ግን ገዝቶታል ። አዎ ዋጋ የለኝም አትበሉ ፣ ዋጋችሁ ትልቅ ነው ። እርሱም የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ።
ጌታ ሆይ ያልከው ላይቀር መጨነቄ ከቶ ለምንድነው ? ድካሜና ሩጫዬ ዕረፍት አልሰጠኝም ። ዕረፍት የሰጠኝን ቃልህን ማክበር ይሁንልኝ ። ዋጋ ቢስነት እንዳይሰማኝ ልቤን በዋጋዬ ልክ ሙሉ አድርግልኝ ። ሁልጊዜ በጸናው ማንነት አንተን ማስከበር ይሁንልኝ ። በአማኑኤል ስምህ ፣ በፈሰሰው ደምህ ፣ በእንተ ማርያም እምህ አሜን ።
የዕለቱ መና 14
ግንቦት 13 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም