የትምህርቱ ርዕስ | ውሸት ይወገድ


ውሸት ይወገድ

“ስለዚህ ውሸትን አስወግዳችሁ ፥ እርስ በርሳችን ብልቶች ሆነናልና እያንዳንዳችሁ ከባልንጀሮቻችሁ ጋር እውነትን ተነጋገሩ ።” ኤፌ. 4 ፡25 ።

“ቆሻሻ በአግባቡ ከተወገደ ሀብት ነው” የሚል አባባል ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ይሰማል ። ቆሻሻ በራሱ ሀብት አይደለም ። በአግባቡ ከተወገደ ግን ለጥቅም ይውላል ። በዚህ ምክንያት የተደራጁ ወጣቶች ቆሻሻችንን ከየቤታችን ይወስዳሉ ። እኛ እንኳ የምንጸየፈውን የራሳችንን ቆሻሻ ለሚያነሡልን ወጣቶችና ሠራተኞች ክብር መስጠት ፣ አብረናቸው እንጀራ መቍረስ ይገባናል ። ባለውለታዎቻችን ናቸው ። እነዚህ ሠራተኞች ለአንድ ወር ዘወር ቢሉ ከተማዋ ከተማ አትሆንም ። በሁሉም አገር ቆሻሻ አለ ። በሁሉም አገር ሠራተኞች አሉ ። በሠለጠነ አገር ግን ዝቅ ብለው ለሚሠሩት ክብር ይሰጣቸዋል ። ደመወዛቸውም ላቅ ያለ ነው ። ሥልጣኔው ቆሻሻችን ሀብት ነው ብሎ መጥቷል ። በዚህም ሁሉንም ቆሻሻ በአንድ ላይ በማድረግ ሳይሆን በየመልኩ በማስቀመጥ እንድናሰናዳ ያበረታታናል ። ቆሻሻ ከተቀላቀለ ሀብት አይሆንም ፣ በየመልኩ ሲቀመጥ ግን ሀብት ይሆናል ። ንስሐችንም በአግባቡ ከተወገደ ሌላውን ለማነጽ ሀብት ይሆነናል ። ቆሻሻ በመቀመጡ ሳይሆን በአግባቡ በመወገዱ ሀብት ነው ። በመቀመጡ ግን በካይ ነው ። እንዲሁም ስህተታችንን አፍነን በመኖራችን ፣ ካባ አልብሰን በመንከባከባችን ሳይሆን በትክክለኛው መንገድ ንስሐ በመግባታችን ፈውስ ይሆናል ። ቆሻሻ ምንም ወርቀ ዘቦ ግምጃ ቢያለብሱት ቆሻሻ መሆኑ አይቀርም ። ቢሸፈን ሽታው ያውካል ፣ በበሽታነቱ ጤናን ያቃውሳል ። ስህተትንም ቢቀባቡት ጥቅም የለውም ። ቢያስወግዱት ግን ከመሳሳት በላይ ነው ። በመልኩ ማስቀመጥም መልካም ነው ። ለስህተታችን መነሻውንና ጉዳቱን መመዘን መቻል ፣ ኃላፊነት መውሰድ ፈውስን ያፈጥናል ።

ቆሻሻ መወገድ አለበት ። በዚህ ዓለም ላይ ካሉ ቆሻሻ ነገሮች አንዱ ውሸት ነው ። ቆሻሻ ዓይንን ፣ አፍንጫን ያውካል ። ውሸትም ሰላምን ያሳጣል ። ቆሻሻ ያቆሽሻል ። ውሸትም ይበክላል ። ቆሻሻ ሰው እንዲርቀን ያደርጋል ፤ ውሸትም ወዳጅ ያሳጣል ። ቆሻሻ ካለ ሰው እቤታችን ባይመጣ እንወዳለን ፣ ውሸትም የድብብቆሽ ኑሮ ያመጣል ። ቆሻሻን ማስወገድ አለብን ። ያቆሸሹትን ልጆቻችንን ግን አናስወግድም ። እንዲሁም ውሸትን ማስወገድ እንጂ ውሸታሞችን መግደል አይገባንም ። የውሸታሞች መሞት የውሸት መሞት አይደለም ። የውሸት መሞት ግን የውሸታሞች መሞት ነው ። ውሸት ኃያል አይደለችም ። ጨለማ በሻማ ብርሃን ይጠቃል ፣ ውሸትም በትንሽ እውነት ይሸነፋል ። ብርሃን በሰፋ ቍጥር ጨለማ ይሸሻል ፣ እውነትም ሲገዛ ውሸት ድል ይነሣል ። የብርሃን አለመኖር የጨለማን መኖር ያስከትላል ። የእውነት አለመኖርም ውሸትን በግድ ያመጣል ።

የእኛን ዘመን ስንመለከተው ውሸት እንደ እውነት የሚታይበት ፣ ውሸታሞች ከእውነተኞች ይልቅ አጋፋሪና ጋሻ ጃግሬ ያገኙበት ነው ። ከመቀመጫቸው ሳይነሡ ፣ ከቤታችው ሳይወጡ ለሚዋሹ ሰዎች ብዙዎች አለሁ ብለው ይቆሙላቸዋል ። የውሸት ደጋፊ እየበዛ ይመስላል ። እውነት ከውሸት በላይ የሚያበሳጨው ትውልድ ከመጣ ውሸት እየገዛን እንደሆነ ማሳያ ነው ። ውሸት ብዙ ዘርፎች አሉት ። ፖለቲካ የሚወልደው ዓይናውጣነት እርሱ ውሸት ነው ። እውነት ብለን የነገርነውን እውነት ብሎ ይቀበላል ብለው ሕዝብን እንደ ፈጠሩት የሚያስቡ ፖለቲከኞች ውሸትን የመንገዳቸው ስልት ያደርጓታል ። ሽንገላም የውሸት ቅርንጫፍ መሥሪያ ቤት ነው ። ሽንገላ በአፍ ያኑርልኝ እያሉ በልብ ደግሞ በመብረቅ ያንድድህ ማለት ነው ። “እባብ በአንድ ራስ ሁለት ምላስ” እንዲሉ ሸንጋይም እንዲሁ ነው ። ሸንጋይ እንደ እባብ በጣም ለስላሳ ፣ በጣም መርዛም ነው ። ኃይለኛና ቍጡ ሰውን እንጠላዋለን እንጂ ብዙ ጊዜ ውስጡ ሐቀኛ ነው ። ሰሚ ስላጣ ግን ቍጠኛ በመሆኑ እናወግዘዋለን ። ሸንጋይ አይቆጣም ፣ ረጅም ሞት እንድንሞት ግን ያደርገናል ።

የሰጡትን ቃል ማፍረስ ፣ መሐላን በገንዘብ መለወጥ እርሱ ውሸት ነው ። ምክንያተኝነትም የውሸት አካል ነው ። የዲፕሎማሲ ቋንቋና አካሄድም ለውሸት ያደላ ነው ። ዲፕሎማሲ ሁሉም ትክክል ነው ብሎ ማለፍና ያለመፍረድ አካሄድ ነው ። ፍርድ መስጠት ካልተቻለ ሰላም ሊመጣ አይችልም ። የቤትና የደጅ አመል መያዝ ሁለት ዓይነት ሰው መሆን ውሸት ነው ። ለውዳሴ ከንቱ መጾምና መጸለይ ውሸት ነው ።

ውሸት በሰማይ ርስትን ፣ በምድር ክብርን ያሳጣል ። “አፍና ቅብቅብ ሁልጊዜ አያበላም” እንዲሉ ውሸትም ሁልጊዜ አያኖርም ። ውሸትን ማስወገድ ይገባል ። ምንም ካባ ቢያለብሷት ፣ ንግግርን ቢያሰማምሩላት ውሸት ውሸት ናት ። ውሸት እንደ ጥላሸት የምታቆሽሽ ፣ የነካነውንም ሰው የምታረክስ ናት ። ውሸት ሚዛናዊነትን መጣል ነው ። የሚዋልል ሚዛን እርሱ ውሸታም ነው ። ውሸት ፍርድ እንዲዛባ ፣ ጨዋዎች አንገት እንዲደፉ ፣ አገር እንዲታወክ ያደርጋል ። “ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው” እንዲሉ ። ዐፄ ቴዎድሮስ “እንኳን በጦርነት በወሬም አልተሸነፍንም” አሉ ይባላል ።

እርስ በርሳችን እውነትን መነጋገር ይገባናል ። ምክንያቱም ግራ እጅ ቀኝ እጅን አይዋሸውምና እኛም እርስ በርሳችን እውነት መነጋገር ይገባናል ። አካል ነንና ።

ለውሸት ጊዜ ከመስጠት ፣ ውሸትን ከማራገብ ፣ ሳናጣራ ከማውራት ፣ ሰማሁ ብሎ ከመለፍለፍ መራቅ ይገባናል ። ውሸታም አይደለሁም ብሎ ውሸታን ማድነቅና መርዳት እርሱ ውሸታምነት ነው ።

እውነትን እንለማመድ ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 10 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም