ዕድሜአችሁ እየገፋ ሲመጣ የምትማሩት ቁም ነገር አለ፡-
1- ሁሉም ሰው እንደ እኔ ያስብ ከሚል አዙሪት ትወጣላችሁ ።
2- ሁሉም ሰው ይወደኛል ከሚል ሞኝነት ትላቀቃላችሁ ።
3- ለመወደድ ብላችሁ የምትለፉትን ልፋት ትቀንሳላችሁ ።
4- ምቀኛ አያሳጣኝ ብላችሁ ትጸልያላችሁ ፣ ምቀኛ ራስን ያስችላልና ።
5- በማታ የተገኘ ዘመድ ንብረት ፈላጊ መሆኑን ትረዳላችሁ ።
6- ቅዱሱ ጌታ ያለው እንደማይቀር አምናችሁ መደንገጥና መሸበር ታቆማላችሁ ።
7- ሽንገላንና የቀዘቀዘ ሰላምታን ትጸየፋላችሁ ።
8- የማትወዱትን ሰው ለመውደድ ማስመሰል ታቆማላችሁ ።
9- በቁንጅናና በቁመና መማረክ ታቆማላችሁ ፣ ብዙ ጊዜ የላይ ግንባታው ያማረ ውስጡ የፈረሰ ነውና ።
10- ከሩቅ ዘመድ የቅርብ ጎረቤት እንደሚሻል ገብቷችሁ ማኅበራዊ ኑሮን ታከብራላችሁ ።
11- በወደቀ ሰው መፍረድ ታቆማላችሁ ።
12- እፍ ያነዳል ፣ እፍ ያጠፋልና የወረት ፍቅርን ታርቃላችሁ ።
13- እያንዳንዱን ቀን እንደ መጨረሻ ቀናችሁ በማሰብ ሥራችሁን ይዋል ይደር ማለት ትጠላላችሁ ።
14- ወረቀት የያዘው ነገር ወሳኝ መሆኑን ታምናላችሁ ።
15- የሰውን አደራ ትመልሳላችሁ ።
16- በይሉኝታ ኃላፊነት ውስጥ መግባት ታቆማላችሁ ።
17- የሚወዳችሁ ጥቂት ሰው እንደ ሆነ ተረድታችሁ ለዚያ ሰው ትኖራላችሁ ።
18- ልጅም ቢሆን የሚወድደው ሲኖር መሆኑ ገብቷችሁ ማባከን ታቆማላችሁ ።
19- ስትናደዱ መናገርን ፣ ስትደሰቱ በስሜት ቃል መግባትን ትሸሻላችሁ ።
20- በማይመለከታችሁ በሰው ጉዳይ መግባት ታቆማላችሁ።
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 8 ቀን 2017 ዓ.ም.