የትምህርቱ ርዕስ | ዘወረደ

እንኳን ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ታላቅ ጾም አደረሳችሁ !

“በውድ ልጁም እንዲያው የሰጠን የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ ይህን አደረገ ።” ኤፌ. 1 ፡ 6 ።

እግዚአብሔር አብ ሰው ሁን ፣ ሙትላቸው ብሎ ወደዚህ ዓለም የላከው አንድ ልጁን ነው ። አንድ ልጁን ለድግስ እንኳ የሚልክ ወላጅ በሌለበት ዓለም አንድ ልጁን ሞትን ቅመስ ብሎ ላከው ። አንድ ልጁን ለበደለ ባሪያ የሚሰጥ ጌታም ከእግዚአብሔር አብ በቀር ማንም የለም ። ፈቃዳቸው ግን አንድ ነውና አብ ቢልክ ወልድም ፈቅዶ ነው ። በፈቃድ አንድ እንደሆኑ በሥልጣንም አንድ ናቸው ። እግዚአብሔር ይህን ዓለም በመፍጠር ከገለጠው ፍቅር ይህን ዓለም ለማዳን የገለጠው ፍቅር ይበልጣል ። ሰውን ለመፍጠር ወደ መሬት ዝቅ ያለው ፣ ሰውን ለማዳን በበረት ተወለደ ። ሰውን ለመፍጠር እጆቹ በጭቃ የተለወሱ ሰውን ለማዳን በችንካር እጆቹ በደም ራሱ ። ሰውን ለማዳን ሰማያዊው ምድራዊ ሆነ ። እርሱ ምድራዊ ካልሆነ እኛ ሰማያዊ መሆን አንችልምና ። ምድር እንኳ የማትገባን ሁና የስቃያችን ስፍራ እንድትሆን ተፈርዶ ሳለ ሰማይን የምንወርስ ሆንን ። እኛ ከበደልነው መድኃኔ ዓለም የካሰው በለጠ ። ባለ ዙፋኑ ባለ በረት ሆነ ። እኛም ያለንን በረት ሰጠነው ፤ እርሱም በየማኑ መቀመጥን ለቤተ ክርስቲያን ሰጠ ።

ሁሉ ግዛቱ ሳለ ተሰደደ ተባለ ። መግደል እየቻለ ሞተ ። ወዳልተለያት ዓለም መጣ ተብሎ ተነገረለት ። ከዚህ በፊት ያልነበረውን ወልደ እጓለእመሕያው መባልን ገንዘብ አደረገ ። ከዚህ በፊት አባቱን በሁሉ ታዝዞ ሳለ ሙት ለሚለው ትእዛዝ ግን ለመጀመሪያም ለመጨረሻም ጊዜ አንዴ ታዘዘ ። በሚገድል አምላክ የሚኮራው የሰው ልጅ አምላኬ ሞተልኝ ብሎ ይመካ ዘንድ ትሕትናን አገነነ ። አምላክነቱ ሳይለወጥ ሰው ሆነ ። ሰውነታችን ሳይለወጥ አማልክት ዘበጸጋ ተባልን ። ያለ ልክ ዝቅ ስላለ ያለ ልክ ከፍ ከፍ አለን ። ደጋኑ ወደ ኋላ በተሳበ ቍጥር ቀስቱ ርቆ ይሄዳል ፤ እርሱ ዝቅ ባለ መጠንም የሰው ክብር ከፍ ብሏል ። ከመሬት በታች የተፈረደበት የአዳም ሥጋ ከመናብርትና ከሥልጣናት በላይ በዙፋን ተቀመጠ ። የመንግሥተ ሰማያት ጌታ ዘመዳችን ሁኗልና መንግሥተ ሰማያት የማያሰጋን ሆነ ።

እግዚአብሔር ይህን ዓለም ለማዳን ውድ ልጁን ሰጠ ። አብ ፈቀደ ስንል ወልድም ፈቀደ ማለታችን ነው ። ወልድ አዳነ ስንልም አብም አዳነ እያልን ነው ። በማዳን አንድ ናቸውና ። አዳምን የፈጠሩ እጆች አዳምን ለማዳን ተቸነከሩ ። ፍጠረኝ ሳይለው ፈጥሮታልና አድነኝ ሳይለው ሊያድነው ሞተ ። ፍቅር ማሳሰቢያ ሳያሻው የሚያስብ ፣ ያለ ጠያቂም መልስ የሚሰጥ ነው ። ሰው ግን እንደ ቀላል እንዳይቆጥረው 5500 ዘመን የዝግጅት ጊዜ ሰጠ ። የጸሎታችን መልስ የሚዘገየው ደጅ የጠናንበትን ነገር ቶሎ እንደማንተወው ስለሚያውቅ ነው ።

ሰው ለማዳን የምንወደውን መስጠት ግድ ይላል ። እግዚአብሔር ይህን ዓለም ለማዳን የሚወደውን አንድ ልጁን ሰጠ ። የምንጥለውን መስጠትማ መገላገል ነው ። ለሚገላግሉንም ዋጋ እንከፍላለን ። የምንወደውን መስጠት ግን ዋጋ መክፈል ነው ። የምንወደውን ካልሰጠን የምንወደውንም እንዲያው በነጻ ካልሰጠን ሌሎችን መታደግ አንችልም ። እግዚአብሔር ግን የሰጠው አንድ ልጁን ነው ። አንድ ልጁን ያለ እናት የወለደ እግዚአብሔር አብ አዳምን አባትም እናትም ሁኖ የጸጋ ልጅነት ሰጠው ። እግዚአብሔር አብ የሚወደውን ልጁን እንደ ሰጠን ተናግሯል ። በዮርዳኖስ የሰማነው ድምፅ ይህ ነው ። በአብና በወልድ መካከል ያለው ፍቅር ሊተረጎም አይችልም ። ወላጆች ከልጃቸው ጋር ያላቸው ፍቅር ይቀጥላል ፣ ልደቱ ግን በተከፍሎ ነው ። ልጁ ያለ ወላጆቹ የሚቀርበት ነገር አለ እንጂ አይሞትም ። አብ ወልድን የወለደው ግን ያለ ተከፍሎ ነው ። ያለ ልጁ የኖረበትና የሚኖርበት ዘመን የለም ። ለዘላለም ከአባቱ ያልተለየ ልጅ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው ።

ልጅ መባልም የአካልና የክብር ስም የሆነው ለወልድ ነው ። የአብና የወልድ የፍቅር ግንኙነት እኛ የእግዚአብሔር ልጆች ከሆንበት ጸጋ ጋር ምንም ግንኙነት የለውም ። ያገሬ ሞኝ “ኢየሱስም ልጅ ነው ፣ እኔም ልጅ ነኝ” ይላል ። እርሱ ራሱ ለይቶ፡- “ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ” አለ ። ዮሐ. 20፡17። ደባልቆ ወደ አባታችን አላለም ። የእርሱ ልጅነት የባሕርይ የእኛ የጸጋ ነውና ። እግዚአብሔር አብም ምንም እንኳ ዮሐንስ መጥምቅ ልጁ ቢሆንም ከክርስቶስ ጋር ደባልቆ የምወዳችሁ ልጆቼ አላለም ። የምወደው ልጄ አለ እንጂ ። በመልክ የሚመስለው ፣ በባሕርይ የሚተካከለው ልጁ አንድ ነው ። የፀሐይ ብርሃን ከፀሐይ ሳይለይ ወደ ዓለም ይመጣል ፣ ክርስቶስም ከአብ ሳይለይ ወደ ዓለም መጥቷል ። ምስጋናና ክብር ይድረሰው ። ዘወረደ ብለን በዐቢይ ጾም የመጀመሪያ እሑድ የምንዘምረው ምሥጢረ ሥጋዌን ነው ።

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /12

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 20 ቀን 2014 ዓ.ም.

እባካችሁ ለሌሎች አካፍሉት

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም