የትምህርቱ ርዕስ | የሁሉ ቤዛ

 “ራሱንም ለሁሉ ቤዛ ሰጠ ፥ ይህም በገዛ ዘመኑ ምስክርነቱ ነበረ”
                                             1ጢሞ. 2፡6
ጠላትን ስለ መውደድ ያስተማረው ክርስቶስ ለጠላቱ ሞቶ ፍቅሩን የገለጠ ነው ። ኃጢአት ከእግዚአብሔር ጋር ጠላት ፣ ከዲያብሎስ ጋር ወዳጅ የሚያደርግ ነው ። የሰው ልጅ በልጅነት ጀምሮ በጠላትነት እንዳይፈጽም ጌታችን ልዋጭ ሁኖ ወደ ዓለም መጣ ። ልጅ ጠላት ሲሆን ምንኛ ከባድ እንደሆነ የደረሰበት ብቻ ያውቀዋል ። የገዛ ልጃቸው ያሳደዳቸውና በአፋር በረሃ ያሰራቸው አንድ ሰው፡-
አለህም እንዳልል እንዲህ ይደረጋል ፣
የለህም እንዳልል ይመሻል ይነጋል ፣
ልጅ እንዴት ባባቱ መድኃኒት ይምሳል ?

ብለዋል ። ነቢዩ ዳዊትም የገዛ ልጁ አቤሴሎም ባሳደደው ጊዜ፡- “አቤቱ የሚያስጨንቁኝ ምንኛ በዙ” የሚለውን መዝሙር ሦስትን ጸለየ ። ሳሚ የተባለ ሰውም በሰደበው ጊዜ የገዛ ልጄ እንዲህ ካደረገኝ ከአንተማ ምንም አልጠብቅም ብሎ ስድቡን ናቀው ። አዳም የእግዚአብሔር ልጅ ነው ። አዳም ግን ከዲያብሎስ ጋር ተሻርኮ የእግዚአብሔር ጠላት ሆነ ። እግዚአብሔር መንግሥቱን በቅጠል ያገኘው ይመስል እርሱም አምላክነትን በቅጠል ለማግኘት ሞከረ ። ውጤቱ ግን “የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች” ሆነ ።
ክርስቶስ ለጠላቶቹ ሞተ ብለን እየሰበክን የገዛ ወዳጆቻችንን መውደድ አቅቶናል ። ብዙ ሰው ጠላትን ለመውደድ ከራሱ ጋር ይታገላል ። ጠላትን የመውደድ መነሻው ወዳጅን መውደድ ነው ። ጌታችን ለሁሉ ራሱን አሳልፎ ሰጠ ። ለሁሉ መጸለይ አቅቶን ፣ የጸሎት አድልኦ የምንፈጽመው እኛ ክርስቶስ ለሁሉ እንደ ሞተ ብናውቅ ደስተኛ እንሆን ነበር ።
ክርስቲያን ነን የምንለው ሳይቀር ቅድሚያ የምንሰጠው ለሥጋ ዝምድና ነው ። መንፈሳዊ ወዳጅነትን በመዝሙር እንጂ በተግባር አናውቀውም ። የእኛ ለሆኑት እንኖራለን ፣ እንሞታለን ፣ እንዘርፋለን ፣ እንዋሻለን ። ከሚሰርቁ ሰዎች ጀርባ የሚሰረቅላቸው ሰዎች አሉ ። ሁሉንም መሣሪያ ተግባር ላይ የምናውለው ፣ “ጦርነት ሕግ የለውም” የምንለው ፣ “በቆሻሻ ውኃም ቢሆን እሳትን ማጥፋት ይቻላል” ብለን የምንፎክረው የእኛ ለምንላቸው ሰዎች ነው ። ታስረው ያልጠየቅናቸው ብዙ ወዳጆቻችን አሉ ። ምክንያቱ የእኛ ስላልሆኑ ነው ። የሥጋ ወንድማችን ቢሆን አንጨክንም ነበር ። ብዙ ድካማቸውን ያወራንባቸው ፣ ሲወራባቸው ለሌሎች ያስተጋባንባቸው ሰዎች አሉ ። ቤተሰቦቻችን ቢሆኑ አናደርገውም ነበር ። የምንኖረው በሥጋ አጥር ውስጥ እንጂ በመንፈሳዊ ከፍታ አይደለም ። አገር ጥለን ተሰድደን የምንረዳቸው ወገኖች አሉን ፣ ለቤተ ክርስቲያን ብለን ግን አገር ጥለን ላንሰደድ እንችላለን ። ከክርስቶስ ይልቅ እኛ የሚለው ወይም የእኔ የሚለው ነገር ይጎላብናል ። ሲወድቁ አልፈናቸው የሄድናቸው ብዙ ወገኖች አሉ ። የእኛ የምንላቸው ሰዎች ስላልሆኑ ነው ። ለራበው ባዳ እጸልያለሁ እንላለን ፣ ለራሳችን ሰው ግን እንጀራ ቆርሰን እንሰጣለን ። እኛ በመንፈሳዊ ዓለምም የምንኖረው ሥጋዊውን ቤተሰብ ነው ። ክርስቶስ ግን ለሁሉ ራሱን ሰጠ ።
“ራሱንም ለሁሉ ቤዛ ሰጠ” የሚለውን ቃል ደግመን እናስበው ። ብዙ ነገሮችን ለብዙ ሰዎች ሰጥተናል ። ለጥቂት ሰዎች ራሳችንን እንደ ሰጠን እንናገራለን ። ሲበድሉን ግን ባበላናቸው ልክ እናስተፋቸዋለን ። የኪሱን ገንዘብ ፣ የአእምሮውን እውቀት ፣ የሙያውን አሥራት የሚሰጥ ከተገኘ ቡሩክ ነው እንላለን ። ክርስቶስ ግን የሰጠው ራሱን ነው ። አስቀድሞ ሁሉን ሰጠን በመጨረሻ ራሱን ሰጠን ። ክርስቶስ ራሱን የሰጠው ለሁሉ ነው ። ለልጆቻቸው ሲሉ እሳት ውስጥ የገቡ ደግ እናቶች ፣ ለአገራቸው ሲሉ የተሠዉ ታማኝ ወታደሮች አሉ ። የክርስቶስ ግን ልዩ የሚያደርገው ቤዛነት ነው ። ቤዛ የሚሆን አምላክ ብቻ ነው ። ምክንያቱም በዚህ ልክ መውደድ የሚችል እርሱ ብቻ ነውና ። በስሜት የሚሞቱ ፣ ይህን ከማይ አብሬ ልለቅ የሚሉ አሉ ። ቤዛነት ግን የታሰበ ደግነት ነው ። ቤዛነት ስለ ጠፋ ንብረት የሚከፈል ንብረት አይደለም ። ቤዛነት ራስን መስጠት ነው ። ቤዛነት ሕጋዊ የማዳን መንገድ ነው ። ሕጋዊ ስንል የባሕር ላይ ወንበዴዎችን ፣ ዓለም አቀፍ ማፊያዎችን የሚያደራድሩ ሕጋዊ ተቋማት አሉ ። ቤዛነት ግን ከቅዱስ እግዚአብሔር የመጣ የተቀደሰ የማዳን መንገድ ነው ።
ቤዛ የሚሆን ዘመድ ነው ። ክርስቶስ ለእኛ ቤዛ ለመሆን በድንግል ማርያም በኩል ዘመዳችን መሆን ይገባው ነበር ። ጥቂት ሥጋ ከመርፌ ትወጋ እንዲሉ እንዲቆረቆርልን ፣ ሕጋዊ ከፋያችን እንዲሆን ዘመዳችን መሆን አስፈለገው ።የብሉይ ኪዳን የቤዛነት ፍቺ የተወሰደን ርስት ለማስመለስ የቅርብ ዘመድ የሚከፍለው ዋጋ ነው ። ወንድምህም ቢደኸይ ከርስቱም ቢሸጥ ፥ ለእርሱ የቀረበ ዘመዱ መጥቶ ወንድሙ የሸጠውን ይቤዠዋል” ይላል ። ዘሌዋ. 25፡25 ።
አዳም የሸጠው ልጅነት የተባለውን ርስቱን ነው ። ሁለተኛ ካልተወለድን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ላንገባ ወጥተን ነበር ። ሁለተኛ እንድንወለድ የእግዚአብሔር ልጅ ሁለተኛ መወለድ ነበረበት ። እኛ ከእግዚአብሔር እንድንወለድ እርሱ ከሰው ተወለደ ። ሰማያዊው ምድራዊ ካልሆነ አፈር ትሆናለህ የተባለው የሰው ልጅ ሰማያዊ መሆን አይችልም ። ርስት አስመላሹ የቀረበ ዘመዳችን ነውና ዋጋ ከፍሎ ተቤዠን ።
ሰው ቢታሰር በገንዘብ ይፈታል ። ቢበድል ንብረት ካሣ ይሆንለታል ። የጠፋቸው ነፍስ ግን ነፍሱን የሚሰጥ ካላገኘች ልትድን አትችልም ። ከጠቡ ያለበት አስታራቂ መሆን አይችልም ። ስለዚህ ነቢያት አበው ዋጋ ከፍለው ሊያድኑን አልቻሉም ። ክርስቶስ ግን ንጹሕ ነውና በሞቱ አዳነን ። መላእክት ምንም ቢወዱን ስለ እኛ ቤዛ የሚሆኑበት ሥጋ የላቸውም ። በተፈጥሮአቸው ረቂቃን ናቸውና ። ክርስቶስ ግን ሥጋ ለብሶ ቤዛ ወይም ልዋጭ ሆነን ። ሞታችንን ለራሱ ወስዶ ሕይወቱን ለእኛ ሰጠን ። አንድ መልአክ አስገድሎ ቢያድነን ኑሮ እግዚአብሔር ፍቅር ነው ብለን ለመናገር ባልበቃን ነበር ።
ጌታችን ይህን ማድረጉ በገዛ ዘመኑ ምስክርነቱ ነበር ። ቤዛነቱ የመሰከረው ማዳን የእግዚአብሔር መሆኑን ነው ። በእኛ ጊዜ ሳይሆን በገዛ ዘመኑ የሆነ ነው ። ያለ እግዚአብሔር ጊዜ ውብ የሚሆን የለምና ።
ክብር ምስጋና ሞቶ ላዳነን ክርስቶስ ይሁን ።
1ጢሞቴዎስ /27/
ታኅሣሥ 25 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም