የትምህርቱ ርዕስ | የሁልጊዜው ጎበዝ

“ውኆቻቸው ጮኹ ተናወጡም፥ ተራሮችም ከኃይሉ የተነሣ ተናወጡ።” (መዝ. 45 ፡ 3 ።)

ተራሮች ወደ ባሕር ልብ ሲወሰዱ ከሚከሰቱ ነገሮች አንዱ የውኆች ጩኸትና መናወጥ ነው ። እንደ ተራራ የገዘፈ ቁመናና ስም ፣ ዝናና ከበሬታ ያላቸው ሰዎች ድንገት ሲወድቁ ዓለም በወሬ ይናወጣል ፣ በሰበር ዜና ይወጠራል ። የማይጠፉ የሚመስሉ ሲጠፉ ፣ ዘላለም ኗሪ ነን ያሉ ሲታጠፉ ብዙ ጩኸት ይሰማል ። ግንዱን የተደገፉ ግንዱ ሲወድቅ አብረው ይወድቃሉ ። በገናና ሰዎች ስምና ዝና የሚኖሩም የታመኑባቸው ቀን ሲከዳቸው ፣ እነርሱም በጨለማ ይዋጣሉ ። የበሉትን የሚያስተፋ ፍርሃት ይከባቸዋል ። በምን ቀን በእገሌ ፎከርኩ ? እስኪሉ ድረስ ጸጸት ያሰቃያቸዋል ። የቀን ጌቶችን መታመን መጨረሻው ሐፍረት ነው ። በእግዚአብሔር የሚታመኑ እርሱ ይሰጠኛል ብለው ይሰጣሉ ፣ በሰው የሚታመኑ ግን የሌላውን ይቀማሉ ። በእግዚአብሔር የሚታመኑ ዝቅ ይላሉ ፣ በሰው የሚታመኑ ግን አምባውን ካልሞላን ይላሉ ። በእግዚአብሔር የሚታመኑ የነገውን ያስባሉ ፣ ከነገም አልፈው ስለ ዘላለም ያሰላስላሉ ፤ በሰው የሚታመኑ ግን የአሁን ብቻ ሰው ሆነው ይኖራሉ ። በእግዚአብሔር የሚታመኑ ነገ የማይደገም ንግግር አይናገሩም ፣ በሰው የሚታመኑ ግን ለአንደበታቸው ልጓም የለውም ። አዎ የታመኑባቸው ተራሮች ሲሰወሩ ብዙዎች በልባቸውም በአፋቸውም ይጮኻሉ ። መደበቂያም እስኪያጡ ይናወጣሉ ። የሰደቡአቸው ሰዎች ፣ የገፉአቸው ድሆች ፊት ለፊታቸው ድቅን ይሉባቸዋል ። “የጊዜ እንጂ የሰው ጀግና የለውም” እንዲሉ ደፋሩ ፈሪ የሚሆንበት ጊዜ ይመጣል ።

ውኆቻቸው ይጮኻሉ ። ተራሮች ወደ ባሕር ልብ ሲገቡ ፣ ኃያላን ሲወድቁ በእጃቸው የበሉ ይጮኻሉ ። እነዚህ መንገድ የሚሸኙ እንጂ አብረው መከራ የሚቀበሉ አይደሉም ። የበላ ሆድ መከረኛ ነውና ትንሽ ቡፍ ፣ ቡፍ ይላሉ ። እነዚህ ሰዎች ተራሮቻቸው በጸኑ ዘመን እነርሱ እንጀራ ስለጠገቡ የሌላውን ረሀብ ሐሰት ነው ይሉ ነበር ። የእንግሊዝ ንግሥት ልጅ ፣ “ሰው ተራበ” ቢሏት “አይስክሬም አይበሉም ወይ?” አለች ይባላል ። ሰው በአእምሮው ማሰብ ትቶ በጎሣ ፣ በገንዘብ ካሰበ ከአራዊት እየከፋ ይመጣል ። ሰው ስለ ራሱ ድሎት መናገር ይችላል ፣ እገሌ አልራበውም ማለት ግን ተገቢ አይደለም ። ተራሮች ሲነዋወጡ የነገዱ ፣ ያናገዱ ይጮኻሉ ። የማይናወጠውን ዙፋን ፣ መንበረ ሥላሴን የተጠጉ ግን እንደ ከበሩ ይኖራሉ ። ሟች ሰው በሟች ላይ ተስፋ ማድረጉ ይገርማል ። ሕያው እግዚአብሔርን ትቶ “ሞተ” በሚል በሁለት ፊደል በሚዘጋ ሰው መታመን ሞኝነት ነው ። ዘመናችን የቲፎዞ ዘመን ነው ። ፀሐፊም ፣ ደራሲም ፣ ሰባኪም ፣ ዘማሪም በእምነት ሳይሆን በሚጨፍሩ ሰዎች ተደግፈው ቆመዋል ። በሚላሉ የሰው እጆች ላይ ፣ በሚዝሉ የሥጋ ለባሽ ክንድ ላይ የተሳፈራችሁ አሁኑኑ ካልወረዳችሁ ፣ ለራሳችሁም ለሚወዱአችሁም ማፈሪያ ትሆናላችሁ ። እግዚአብሔር ብዙ ነገሮችን በትዕግሥት ያልፋል ፣ ከንቱ ትምክሕትን ግን ፈጥኖ ያዋርዳል ።

በዓለም ላይ ክብር ከሸሸ በኋላ እንደ ገና የመመለሱ ነገር ከባድ ነው ። “ቆብ የሚቀደደው አንድ ጊዜ ነው” ይላሉ ። እግዚአብሔር የሰጠንን ዕድል በአግባቡ ካልተጠቀምን እንደገና ላይኖረው ይችላል ። ተራሮች ወደ ባሕር ልብ ሲወሰዱ አብረው የተሻረኩ ባለጠጎችና ኃያላን ሊጮኹ ይችላሉ ። እግዚአብሔር ሲጥል የሚያነሣ የለምና ጩኸታቸው ከንቱ ሆኖ ይቀራል ። የጠለቀችን ፀሐይ ማንም ብርቱ ሊያወጣት አይችልም ፣ የጠለቀ ዕድልም በማንም ብርታት አይመለስም ። ዕድል ከሄደ አይመለስም ። መልካም ሰውም ከሄደ አይመለስም ። እግዚአብሔር ዕድልና መልካም ሰው ሲሰጠን ፈጣንና ብልህ መሆን አለብን ።

ነቢዩ ዳዊት በሌላ ስፍራ፡- “አንተን ተስፋ የሚያደርጉ አያፍሩም በከንቱ የሚገበዙ ያፍራሉ” ብሏል። (መዝ. 24 ፡ 3 ።) በነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ ብሏል፡- “እኔንም በመተማመን የሚጠባበቁ አያፍሩም።” (ኢሳ. 49 ፡ 23 ።) ዳዊት ሳኦልን ተመክተው የነበሩ ሲወድቁ ፣ የንጉሥ ልጅ ቁራሽ ሲያርበት ፣ አገር የመራው ንጉሥ ቀባሪ ሲያጣ ፣ ልዑላን በዱር ሲቀሩ ፣ ልዕልቶች የአሽከር መጫወቻ ሲሆኑ አይቷል ። እርሱም በዘመኑ ሁሉ በሌላ በመመካት እግዚአብሔርን ላለማሳዘን ጥሯል ።

በመቀጠልም፡- “ተራሮችም ከኃይሉ የተነሣ ተናወጡ ።” አለ ። የአዋቂዎች እውቀት አለማወቅ ሆነ ፣ የባጠጎች ወርቅ ወደ ዝገት ተለወጠ ፣ ዝነኞች መኖሪያቸው ዋሻ ሆነ ፣ ይሰጡ የነበሩ የልመና ዕድልም ተነፈጉ ፣ ሰው ሁሉ ይሸታቸው የነበሩ ልብሳቸው በላያቸው ላይ አለቀ ። ሰውን ከአንበሳ ጋር እያታገሉ ይዝናኑ የነበሩ ፣ በዕብደት ተቀጡ ። በእግዚአብሔር ኃይል ፊት የቆመ አንድም ብርቱ የለም ። እግዚአብሔር ሲነሣ በፊቱ የሚቆም ጀግና የለም ። የሁልጊዜውን ጎበዝ እግዚአብሔርን ተተገኑ ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 18 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም