መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » የሕይወቴ ሕይወት

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወቴ ሕይወት

የጽርሐ አርያም ጉልላቱ ፣ የጥልቀት መሠረቱ ፣ የአድማሳት ወደብ ፣ የሰማይ ሰማይ ፣ የሕይወቴ ሕይወት አንተ እግዚአብሔር ነህና አመሰግንሃለሁ ። በልብ ሙላት አንተን እንዳወድስ ፣ በውስጥ ቅንነት ወገኔን እንዳገለግል ፣ በመንፈስ ኅብረት እንድሰበሰብ ፣ በተባባሪነት መልካም ከሚሠሩት ጎን እንድቆም ፣ ከሁኔታዎች በላይ ያለውን እውነት እንዳይ ፣ ተራራውን በድል እንድወጣ ፣ በሸለቆውም ተስፋ እንዳደርግ ፣ በጸሎት እንድተጋ ፣ ከበዛ ዝና ጥቂት ትሩፋት እንዲኖረኝ እለምንሃለሁ ። ጸሎትን የሚያህል ሥራ እንደሌለ ፣ ሥራንም የሚቀድስ ጸሎት እንደሆነ ፣ እየሠሩ መጸለይ ፣ እየጸለዩ መሥራትን እንዳውቅ እለምንሃለሁ ። ለአዲሱ አዳም ፍቅር ብታሳየው አይደንቅም ፣ ለወደቀው አዳም ስላሳየኸው ፍቅር አመሰግንሃለሁ ። ከፍታም ዝቅታም አንተን አይለውጥህም ። ሰብአዊውን በአምላካዊ ፣ ቁሳዊውን በሰማያዊ ነገር እንድለውጥ እመኛለሁ ። የላቀ ክብር ላንተ በመስጠት የላቀ በረከት እንደማገኝ ተስፋ አደርጋለሁ ። ቆዳ ካልተወጠረ ተፍቆ ለስልሶ ልብስ አይሆንም ። ሸራውም ካልተወጠረ ሥዕል አይወጣውም ። አንተም በቅንዋት ተወጥረህ በቀራንዮ መብል ሆንከኝ ። እባክህን እንድወጠር ለሠዓሊው ግልጽ እንድሆን አስተምረኝ ። ሠዓሊ በሸራ ላይ ሲስል ፣ አንተ ግን በልብ ሰሌዳ ላይ ትስላለህ ። ሠዓሊ ፍጥረትን ሲስል አንተ ግን አንተነትህን በልቤ ትቀርጻለህ ። ሸራው ልቤ ውጥር ያለ የተገለጸ ይሁንልህ ። ሸራው የራሱን ቀለም ይዞ አይጠብቅም ፣ ባዶ ሁኖ ይጠብቃል ። እኔም ባዶነቴን ይዤ እጠብቅሃለሁ ፤ አንተነትህን በእኔ ላይ ሣል ። እኔን በእኔ ውስጥ ሲያገኙ የሸሹ ፣ አንተን በእኔ ውስጥ ሲያገኙ ይመጣሉ ። ደስ ላለመሰኘት ከወሰነ ማጉረምረም ፣ መኖርን ከተንገፈገፈ ምሬት ፣ የእብድ ጭምት ከሚያደርግ ማስመሰል ፣ አቅልን ከሚያስት ቍጣ ፣ ሁሉን ከሚያፈርስ ግንፍልተኝነት ፣ ሰውን ከሚያጠለሽ ሐሜት ፣ ራስን ከሚክብ ጉረኝነት አድነኝ ። በሰማይ የምለብሰውን ነጭ ልብስ ዛሬ በቅድስና አልብሰኝ ። በቤትህ እንድትጋብዘኝ በቤቴ እንድጋብዝህ አድለኝ ። አሜን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 16 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም