የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

የሕይወት ሥነ ሥርዓት (25)

13. ንግግርህ ብቁ ይሁን (ሸ)

19. በሰው ቍስል አትፍረድ

የወደቀ ሰው የሚፈልገው የሚያነሣው እጅ እንጂ ስለ ውድቀቱ ጥናት የሚሠራበት ፈራጅ አይደለም ። የራሳችን ችግር ተራራ አህሎ ፣ የሰዎች ውጣ ውረድ አንሶ የሚታየን ጊዜ ብዙ ነው ። ኃጢአትን በሚመለከት የራሳችን ትልቅ በደል ቅንጣት ፣ የሰዎች ትንሽ ስህተት ቁልል ሁኖ ይታየናል ። ሰዎችን ከደረሰባቸው ችግር በላይ የሚከብዳቸው በየጊዜው የሚያስተናግዱት የሌሎች የፍርድ ቃል ነው ። ደካማ ሰዎች የሰውን መታመም ፣ መቸገርና መዋረድ ሲያዩ እነርሱ ቅዱስ ፣ ያ ሰው ርኩስ መስሎ ይታያቸዋል ። ይህች ዓለም ግን ለክርስቶስ ሕመምን ፣ ረሀብን ፣ ጥማትን ፣ ውርደትን የከፈለች ዓለም ናት ። እውነተኛው ፍርድ ያለው በሰማይ ነው ። ውድቀት የራሱ ሆነ ድምፅ አለው ። ሰውን ውድቀቱ የሚናገረውን ያህል የእኛ ቃል ሊናገረውና ሊገሥጸው አይችልም። ፈሪሳውያን ሁሉንም እጦት ከኃጢአት ጋር ያያይዙት ነበር ። ሰው የሚታመመው ፣ የሚያጣው ባለማመኑ ነው የሚሉ ዘመናዊ ፈሪሳውያንም በዚህ ዘመን አሉ ። እነዚህ ሰዎች በብዙ አቋራጭ መንገድ እንደሚጓዙ ሕሊናቸው ያውቀዋል ።

በሰው ቍስል እንጨት መስደድ ለተቀባዩ ከባድ ፣ ላቀባዩ ግን ቀላል ነው ። በእኛ ቍስል ላይ ግን የሐኪም እጅ ፣ የመድኃኒት ጠብታ ሲያርፍ እንሳቀቃለን ። በሰዎች ቍስል ላይ ሌላ ቍስል ለመጨመር ግን አንፈራም ። በራሳችን ላይ ግን የመፍትሔ እጆችንና ሥራዮችን ሳይቀር እንሸሻለን ። ለሰው መርዝን በደስታ እንበጠብጣለን ፣ ለእኛ ግን መድኃኒቱንም አጥብቀን እንመረምራለን ። “ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ” ማለት ተጠንቀቅለት ፣ ይቅርታ አድርግለት ፣ አስብለት ማለት ነው ። በእኛ አገር ብዙ ችግር አለ ። ትልቁ ችግራችን “ምን ይሉኛል?” የሚለው ከንቱ ስጋት ነው ። ያልተገነባው ማንነታችን በሚሉን ነገርና በሚሰጡን ክፉ ስም ይፈራርሳል ። ቀላል ሰው በጥቂት ምስጋና ደመና ይነካል ፣ በጥቂት ነቀፋ መቀመቅ ይወርዳል ። አራት አምስት ልጅ የቀበሩ የሚያሳስባቸው ከራሳቸው መጎዳት ፣ ከልጆቻቸው ማለቅ በላይ “ምን ይሉኛል?” የሚለው ፍርሃት ነው ። ለሁሉም ነገር አስተንትኖ መስጠት ግዳጅ የሚመስለው የአገሬ ሰው ፣ የራሱን ትቶ በሰው ቤት ላይ የሚውል የሚያድረው ወገኔ ፈውሱ መቼ ይሆን! ይህችን ጽሑፍ በምንጽፍባትና በምናነብባት ቅጽበት በሰው ላይ ነገር የሚሠሩ ፣ የስም ጥላሸት የሚቀቡ ብርቱ ሥራ እንደ ያዘ ተጠምደዋል ። በልመና ስንዴ መኖራችን አያሳቅቀንም ። ለልመናም ብቁ አይደላችሁም ተብለን ገሸሽ ሲያደርጉን እናኮርፋለን እንጂ ይህን ታሪክ ለመለወጥ ወኔ ያጥረናል ። አናበድራችሁም ሲሉን ጭልም ብሎብን እንደናበራለን እንጂ “እንዴት አድርገን ለችግራችን ሞትን እንክፈለው” የሚል ጥንካሬ ርቆናል ።

በሰው ቍስል ላይ መፍረድ ትልቅ ጭካኔ ነው ። ጨካኝ ብለን የምንጠራቸው ሰይፍ የሚዙ ፣ ጥይት የሚተኩሱ ሰዎችን ነው ። ትልቁ ጭካኔ ግን በሰው ቍስል ላይ መፍረድ ነው ። ጫካ ላይ ቆመው ሰውን የሚያስጨንቁትን ብቻ ሳይሆን በከተማ ያሉትን ግፍ የማይፈሩ ጠበቃና ዳኞችን ፣ ሐኪምና ባለሙያዎችን አሸባሪ ብለን ለመጥራት ድፍረት ያስፈልገናል ። ሁሉም በአቅሙ የሚበድልባት አገር መፍጠራችን በእውነት ያሳዝናል ። አዎ በሰው ቍስል መፍረድ ትልቁ የአንደበት ውድቀት ነው ። የወደቀን ሰው እንዲነሣ ከማገዝ ውጭ ምንም ዓይነት አሉታዊ ድምፅ ማሰማት አይገባንም ። ሃይማኖት ማለት የወደቀውን አዳም የፈለገ ፣ የበዳይን ሞት ሞቶ የካሰውን አምላክ ማመን ነው ። ሰዎች የሚወድቁት አንዳንዴ መንገዱ ጠፍቷቸው ነው ፣ ሌላ ጊዜ የሚዘሉት መስሎአቸው ገደሉ ሰፍቶባቸው ነው ፣ አንዳንዴም እነሣለሁ ሲሉ ይወድቃሉ ፣ አተርፋለሁ ሲሉ ይከስራሉ ፣ አስደስታለሁ ሲሉ ያሳዝናሉ ። አላዋቂነታቸውም የውድታቸው ምክንያት ይሆናል ። ለመማር ፣ በርታ ለመባል ዕድሉን ባለማግኘታቸው ሰሰዎች ይወድቃሉ ።

የእግዚአብሔር እጆች የወደቀን ለማንሣት ተዘርግተዋል ። እኛ ባናነሣቸው እንኳ በወደቁት ላይ ምሣር ማብዛት አይገባንም ። ምሣር ወይም መጥረቢያ የምናበዛበት ዛፍ ትላንት በልምላሜው ደስ ያሰኘን ፣ በአበባው ተስፋ የሰጠን ፣ በፍሬው ያጠገበን ፣ በጥላው ያሳረፈን ፣ በውዝዋዜው አየሩን የቀዘፈልን ፣ በውበቱ ቤታችንን ውድ ያደረገልን ነው ። ይህ ዛፍ ሲወድቅ ግን ሁሉም መጥረቢያ ይዞ ይከተክተዋል ። ሰው ዛፍ አይደለም ፣ ወድቆ አይቀርም ፣ ይነሣል ። ዛፍ ሲያድግ ድምፅ የለውም ፣ ሲወድቅ ግን ድምፁ ይሰማል ። ስናድግ ብዙ ሰው እንዳላየ ያልፈናል ፣ ቅናቱ ዱዳ ያደርገዋል ። ስንወድቅ ግን ሁሉ ይሰማዋል ። በወደቀው ዛፍ የቆሙት ቢስቁ ያ የወደቀ ዛፍ የመጥረቢያ እጀታ ሁኖ ሊቆርጣቸው እንደሚመጣ ቋሚዎች ይዘነጋሉ ። ዛሬ እያስጨነቁን ያሉት ትላንት ወደቁ ብለን የሳቅንባቸው ፣ ወይም ገፍትረን የጣልናቸው ወገኖች ናቸው ። ንስሐ እስካልገባን በገመድነው ጅራፍ እየተገረፍን እንኖራለን ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ግንቦት 14 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ