መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (27)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (27)

13. ንግግርህ ብቁ ይሁን (ቸ)

22. የሰውን ምሥጢር ለማወቅ አትከጅል

ሰዎች እንዳንተ ናቸው ። አካላዊ መዋቅራቸው ከአንተ ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ ሁሉ ውስጣዊ ስሜታቸውም ተመሳሳይ ነው ። ሰውን ከሰው ልዩ የሚያደርገው ችግሮችን የሚፈታበት ጥበቡ ፣ ነገሮችን የሚቀበልበት ልቡ ነው ። ከዛሬ ሦስት ሺህ ዓመት በፊት የተጻፈ ምክር ዛሬ ላይ የሚሠራው በዚያ ዘመን ከነበሩት ሰዎች ጋር የኑሮ ዝምድና ስላለን ፣ ተመሳሳይ የሕይወት ገጽታ ስለምናስተናግድ ነው ። በሥልጣኔ ብንለያይም በመወለድ ፣ በማደግ ፣ በሞት ሕግ ተመሳሳይ ነን ። ሁላችንም ለመኖር እንበላለን ። ደስታችንም በሌሎች ጉድለት ውስጥ ተቀምጧል ። የሌሎችን ጉድለት ስንሞላ የእኛን ደስታ እንቀበላለን ። ሰዎች የራሳቸው ምሥጢር እንዲኖራቸው መፍቀድ ያስፈልግሃል ። ሚስትህም ልጆችህም ካንተ ጋር አንድ አካልና የአካል ክፋይ ቢሆኑም የራሳቸው ግላዊ ሕይወት እንዳላቸው ማመን ያስፈልግሃል ። ወደው ፈቅደው እስኪያሳውቁህ ድረስ ቀና ሰው መሆን አለብህ ።

መንፈሳዊ አገልጋይና ካህን በሆንህ ጊዜ እንደ መርማሪ ፖሊስ የሰዎችን ኃጢአት ለማወቅ አትፈልግ ። ኑዛዜ ማለት ሰዎች ፈቅደው የተናገሩት ስህተት እንጂ እኛ ለማወቅ ያደረግነው ጥረትና ውጤት አይደለም ። የሰዎችን ገመና ተገልጦ ባየህ ጊዜ ለማየት አትጓጓ ። ስለሌሎች አንተ ጋ ሲወራ ፣ ስላንተ ደግሞ ሌሎች ጋ እየተወራ ነው ። ስላልሰማነው እንጂ ሁላችንም ስም አለን ። የሰው ልጅ ሥራ ሲፈታ እንኳን መሰሉን ድንጋይንም ያማል ። ሰዎች ወደው ፈቅደው የነገሩህን በጸሎተኛ ልብ ስማ ። አንዳንድ ችግር እየጸለዩ ካልሰሙት የአሳብ ውጊያ የመንፈስ ትግል ይፈጥራልና ። ችግሩን ከሰማህ በኋላ ስሜታቸውን ተካፈለው ። ነገር ግን ያለ ምክር አትስደዳቸው ። ወዳጅህ በለመነህ ጊዜ ሳንቲም ማጣትህ ይቆጫል ። ለአንድ ቀን እንኳ አልሆንኩትም ያሰኛል ። ሰዎች ባማከሩህ ጊዜ ምክር ካጣህ በመጡበት ስሜት ይመለሳሉ ። ምክር እንዲኖርህ ተመከር ። መምህራንን ተወዳጅ ፣ መጻሕፍትን ቤተ ዘመድህ አድርግ ። ከዚህች ሰዓት በኋላ የመኖር አቅም ላይኖራቸው ይችላልና ዝም ብለህ አትሸኛቸው ።

አንዳንድ ሰዎች በራሳቸውና በቤታቸው ምን እየሆነ እንዳለ አያውቁም ። ሳያውቁት ወደ ድብርት ውስጥ እየገቡ ነው ። አካላዊና ሥነ ልቡናዊ መታወክ እየደረሰባቸው ነው ። የላኛው አካል የውስጠኛውን ሰውነት በጥቂቱም ቢሆን ይናገራል ። ይልቁንም ፊት የልብ አደባባይ ነውና ፊታቸውን አይተህ ልባቸውን ለማወቅ ይቻልሃል ። ጨዋታቸው ሲቀንስ ፣ መሄድ ሲያቅታቸው ፣ ላለመደሰት ሲሞክሩ ፣ ሁሉንም ነገር በዜሮ ሲያባዙ ፣ ከሰው ሲሸሹ ፣ ምሬት ሲያበዙ ፣ … አንድ ችግር ውስጥ እንዳሉ ምልክት ነው ። በዚህ ጊዜ በዘዴ ማማከር ይገባል ። አንዳንድ ጊዜ ምን ሆነሃል ብሎ መጠየቅ ይቻላል ። ሌላ ጊዜ ደግሞ ዙሪያ ገባውን በወሬ በማነሣሣት ሰውዬው ራሱ የውስጡን እንዲናገር መርዳት ይገባል ።

የሰዎችን ምሥጢር ለማወቅ የምሻው ለምንድነው ? ብለህ ራስህን ጠይቅ ። የሰማሁትን ምን መፍትሔ ሰጥቼዋለሁ ብለህ ራስህን ገምግም ። ምሥጢር የማወቅ ጥማት አንድ ቀን የማይሸከሙት አደጋ ላይ ይጥላል ። የደኅንነት ሠራተኞች ለመንግሥታቸው ጆሮ ሆነው ምሥጢር ቢያነፈንፉ ደመወዝተኞች ስለሆኑ ነው ። በነጻ ምሥጢርን ማነፍነፍ ግን ወሬ መውደድ ነው ። “እሺ እባክህ” ፣ “ተው እንጂ” ፣ “ይገርማል” ፣ “አያድርስ ነው” ፣ … የሚሉ ቃላት የወሬ ነዳጅ ናቸው ። ምሥጢሩ የሚያድን እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን ማወቅና መፈጸም እርሱ የሐዲሱ ኪዳን በር ነው ።

የሰዎችን ምሥጢር ማወቅ መፈለግ ከአንተ ጋር የሚመሳሰል ሰው አግኝቶ ለመረጋጋት ነው። አንተ የምትሠራውን ኃጢአት የሚሠራ ከሆነ ብቻዬን አይደለሁም ብሎ ለመደሰት ነው ። አንድን ነገር ስትፈልግ ለምንድነው የምፈልገው ? ብለህ ራስህን ጠይቅ ። ነገር ግን መፍትሔ ፈላጊ ወንበር ላይ ስትቀመጥ ሰዎችን እየጠየቅህ ፈውስና መልስ ማዘጋጀት ሙያ ነው ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ግንቦት 26 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም