መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት 3

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት 3

2- በየዕለቱ አንብብ

አንድ ነገር ሳታውቅ የዋልህባትን ቀን እንደኖርህባት አትቍጠራት ። አንድ ነገር ሳታውቅ ፣ አንድ በጎ ነገር ሳትከውን ከዋልህ ቀኑን ኖርኩበት አትበል ። በዚህ ዓለም ላይ የሥጋ ድንግል ክብር አለው ። የእውቀት ድንግል ግን ክብር የለውም ። እውቀት እንዳይነካህ ተጠንቅቀህ የምትኖር ከሆነ ሞተህ የምትኖር ነህ ። ድንግል አእምሮ የያዘ ሰው የሚያሳዝን ፣ ጎስቋላ ነው ። ብዙ ሰው ማወቅ የማይፈልገው ተሳስተሃል መባልን ስለሚፈራ ነው ። እስከ ዛሬ እውቀት የመሰለው ነገር አሁን እውቀት አይደለም ቢባል የኖረበት ዘመን በዜሮ የተባዛ ይመስለዋል ። ይህችን ዓለም ለመሰናበት አንድ ደቂቃ ቢቀርህም ለመታረም ዝግጁ ሁን ። የሚጸናው የመጀመሪያው ሳይሆን የመጨረሻው ነው ። ታርሞ እንደ መሞት ያለ ክብር የለም ። ብዙ ሰዎች እንደ አዋቂ የሚያዩት ደፋር መሃይም ማወቅ አይፈልግም ። ምክንያቱም ሲያነብና ሲማር ያዩት እንደሆነ የሚንቁት ይመስለዋል ። የሚያሳፍረው በእጅ መጽሐፍ መያዝ ሳይሆን የስካር ብርጭቆ መጨበጥ ነው ። ለንስሐና ለእውቀት ጊዜ አለፈ አይባልም ።

እምነት ያለ እውቀት አለማመን ነው ። ፍቅር ያለ እውቀት ልማድ ነው ። ምግባር ያለ እውቀት የአጋጣሚ ጥረት ነው ። ትዕግሥት ያለ እውቀት እያረሩ መሳቅ ነው ። ተስፋ ያለ እውቀት የራሱ ጉዳይ ብሎ መሪውን መልቀቅ ነው ። ሀብት ያለ እውቀት ከልክ በላይ በታኝ ወይም ከልክ በላይ ስስታም የሚያደርግ ነው ። እውቀት ከተለያየ መንገድ ይገኛል ። የመጀመሪያው ከመጽሐፍ ነው ። ሁለተኛው ከአዋቂዎች ነው ። ሦስተኛው የዘመን ባለጠጋ ከሆኑ ሽማግሌዎች ነው ። አራተኛ ከድሆች ነው ። አነባበቡን ካወቅህበት ሰው ሁሉ መጽሐፍ ነው ይባላል ። ያለ እውቀት የሚደረግ ነገር ሁሉ በሰማይም በምድርም ዋጋ አያሰጥም ። በእውቀት የምናደርገው ነገር ደስታ አለው ። ያመነውን ያወቀ አያፍርም ። የሚወደውን ያወቀ ዋጋ መክፈል አይፈራም ። መጽሐፍ ቃሉን የማያጥፍ ወዳጅ ነው ። በዚህ ዓለም ላይ ብዙ መጻሕፍት ቢኖሩም ቅዱስ የሚል ስያሜ የተሰጣቸው የብሉይና የሐዲስ መጻሕፍት ናቸው ። እነዚህ የሕግ ፣ የጸጋ ፣ የበረከት ፣ የሕይወት መገኛ ናቸው ። በየዘመናቱ የነበሩ አማኞችን ተመሳሳይ ቋንቋና ተመሳሳይ ሕይወት እንዲኖራቸው ያደረጉ ናቸው ። ብሉያትና ሐዲሳት ለእምነት ምስክር የሚጠሩ ናቸው ።

የዕለቱን ተግባር ከመጀመርህ በፊት በማለዳ ተነሥተህ አንብብ ። የምታነበውም መጽሐፍ ቅዱስን ፣ የተባረኩ እጆች የጻፉአቸውን መጻሕፍት ፣ የእግዚአብሔርን ትልቅነት እየተናገሩ የሚሰብኩህን ሊሆን ይገባዋል ። ደግሞም የታሪክ ፣ የምክር ፣ የመጽናት መጻሕፍትን አንብብ ። ቀኑን ኃይል ይዘህ ለመቀላቀል ያግዝሃል ። እውቀት ጋሻ ነውና የሚወረወረው ጦር አያገኝህም ። አእምሮ ማረፊያ ይፈልጋልና በማለዳ መስኩን ልትሰጠው ይገባሃል ። ደግሞም ሆድህ እንጀራን እንደ ጠየቀህ አእምሮም እውቀትን ይጠይቅሃል ። በማንበብህ ከመርሳት በሽታ ትድናለህ ። አእምሮ ካላነበብህበትና እውቀትን ካልቀሰምህበት እየዛገ ይመጣል ። እውቀትን በሚመለከት መገብየትና መቅሰም የሚሉ ቃላት ይደመጣሉ ። ገበያ ሁሉም ምርት አለው ። ገበያ የምንወጣው ግን የሚያስፈልገንን ለመግዛት እንጂ ገበያ ያለውን ሁሉ ይዞ ለመምጣት አይደለም ። ስናነብ የማነበው የቱን ነው ? በማለት መምረጥ ያስፈልጋል ። የጥንቆላ ፣ የሐተታ መናፍስት መጻሕፍትን በማንበብ አእምሮአቸውን ያጡ አሉ ። መቅሰም የሚለው ቃል ለእውቀት ይነገራል ። መቅሰም የንብ ተግባር ነው ። ንብ ከቆሻሻ ሳይሆን ከአበባ ትቀስማለች ። ከመልካም መጻሕፍት መቅሰም ይገባል ። ግን እንደ ንብ ታታሪ መሆን ግድ ይላል ።

የዓይን ብርሃን ፣ የማንበብ እውቀት ኖሮት የማያነብ ዓይናቸውን ያጡ ያዝኑበታል ። ያልተማሩ አባቶችና እናቶች ይረግሙታል ። መጻሕፍትን ለማየት የተፈጠረውን ዓይን ፊልም በማየት የሚፈጁት ንስሐ መግባት ያስፈልጋቸዋል ። መጽሐፍን ዋጋ ከፍሎ ማግኘት ፣ ደግሞም ማንበብ ይገባል ። መጽሐፍን ገዝቶ አለማንበብ ወዳጅን እቤት ጋብዞ እንደ ማኩረፍ ነው ። ከሕይወት ሥነ ሥርዓት አንዱ ማንበብ ነው ። እያነበብን ነው ። በማኅበራዊ ሚዲያ ቀኑን ሙሉ እናነባለን ። የምናነበው ግን ሐሜትን ነው ። የምናነበው የተቆራረጠ አሳብን ነው ።

ስናነብ ምን ይከሰታል ? አእምሮአችን ይበለጽጋል ። ሕይወትን የምናይበት መነጽር ይለወጣል። ምክንያታዊ እንሆናለን ። ከጭፍን እይታ እንድናለን ። የሰውን ዋጋ እናውቃለን ። የምንናገረው ቁምነገር እናገኛለን ። በአሳብ ላይ ተንተርሰን ከሰዎች ጋር እንወያያለን ። ካላነበብን የምንሆነው አሁን እየሆንን ያለነውን ነው ። እወቀትን የተራቡ አእምሮዎች አራዊት ይሆናሉ ።

መጽሐፍ ጓደኛ ነው ፣ አሳብን ይካፈላል ። መጽሐፍ ጓደኛ ነው ፣ ያዋራል ። መጽሐፍ ጓደኛ ነው ፣ ብቸኝነትን ይዋጋል ። አንብቡ ! አንብቡ ! አንብቡ ! ኧረ እባካችሁ አንብቡ !!!

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 11 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ