መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (32)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (32)

17. ማኅበራዊ ኑሮ ይኑርህ

አንድነትን በሚመለከት አራት ዓይነት ኅብረቶች አሉ ። የመጀመሪያው ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ያለው አንድነት ነው ። ሁለተኛው ሰው ከራሱ ጋር ያለው አንድነት ነው ። ሦስተኛው ሰው ከሰው ጋር ያለው አንድነት ነው ። አራተኛው ሰው ከአማኝ ጋር ያለው አንድነት ነው ። ከእግዚአብሔር ጋር ያለን አንድነት እርሱን በማወቅ ፣ በማምለክና ትእዛዛቱን በመፈጸም ፣ በንስሐ በመታደስ ላይ የተመሠረተ እንዲሁም የሚቀጥል ነው ። ሰው ከራሱ ጋር ያለው አንድነት ከእግዚአብሔር ጋር ባለው አንድነት ላይ የሚመሠረት ነው ። ሰው ከራሱ ጋር መለያየት ካመጣ ፣ ውስጣዊ ግጭት ካለበት ሰላምና ደስታ እንዲሁም የመኖር ፍላጎት እየራቀው ይመጣል ። ሰው ከሰው ጋር ያለው አንድነት ከራሱ ጋር ባለው አንድነት መሠረት ላይ የሚቆም ነው ። ከራሱ ጋር አንድ ያልሆነ ከሌላው ጋር አንድ ሊሆን አይችልም ። ሰው በማመን እርሱን ከሚመስሉት ጋር አንድ የሚሆንበት ዘላቂ አንድነት አለ ። ይህን አንድነት ልዩ የሚያደርገው በሰማይም የሚቀጥል በመሆኑ ነው ።

አማኒ የሆነው ወንድማችን ዘመዳችን ፣ ጎረቤታችን ፣ የቅርብ አገልጋያችን ላይሆን ይችላል ። ያለን ግንኙነት መንፈሳዊ ነው ። ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም እንድንኖር መጽሐፍ ያዝዘናል (ሮሜ. 12፡18)። አንዳንዴ አዳጋች ይሆናልና ቢቻላችሁስ የሚል ሚዛን ያስቀምጧል ። ከተቻለን ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም መኖር መልካም ነው ። ሰዎች ግን የእኛ እምነትና ህልውና እየረበሻቸው ሊጣሉን ይችላሉ ። ክርስቲያን በምንም መንገድ ሌላውን የሚያውክ ሊሆን አይችልም ። እርስ በርሳቸው የዘረኝነት ችግር ቢኖርባቸውም ጌታችን ግን ከአይሁድ ወገን ተወልዶ የሳምራውያን ወዳጅ ነበረ ። ሰው ያገለላቸውን ቀራጮችና አመንዝሮች ከእርሱ ጋር አብረው እንዲበሉ ይጋብዛቸው ነበር ። ክርስቲያን ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር መስፈርት የሚያደርገው ሃይማኖቱን ወይም እንደ እኔ ካላመኑ የሚለውን አመለካከት አይደለም ። ክርስቲያን በመጽሐፍ እንጂ በሰይፍ የሚያሳምን አይደለምና ።

ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር መዋሸት አለብን ማለት አይደለም ። ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር የራሳችንን አመለካከትና ሃይማኖት እያከበርን የሌሎችንም ማክበር ነው ። የሃይማኖትህ መሪ የሆነው አባት ከቡዲስት ወይም ከአረሚ ጋር ሰላም ሲባባል ስታይ የምትበሳጭ ከሆነ ይህችን ዓለም ያንተ እምነት አባላት ብቻ እንዲኖሩባት እየፈለግህ ነው ። የራስን ይዞ የሌላውን ማክበር ይቻላል ። ሰዎች ያመኑበትን በጥላቻ ለማስጣል ስንሞክር የበለጠ እንዲያከሩ እናደርጋቸዋለን ። ምንም ውክልና የሌላቸው ለቤተ ክርስቲያን መልስ እንሰጥላታለን የሚሉ ወጣቶች በየጊዜው በሃይማኖት ስም ጥላቻን ሲዘሩ ይታያሉ ። እዚህ ያለውን አይሁድ ስትነካው ኢየሩሳሌም ያለው ክርስቲያን መኖሪያ ያጣል ። ሁሉም አገር አለውና ። እዚህ ያለውን ሙስሊም ስትነካው ግብጽ ያለው ክርስቲያን መሸበር ይጀምራል ። የዚህች ዓለም ሰላም የቆመው በሰው ልጆች ሁሉ ነጻነት ላይ ነው ። የራሱ እምነት ያሳረፈው ሰው የሌላውን በመንቀፍ ጊዜውን አይፈጅም ።

ማኅበራዊ ኑሮ በመከባበር ላይ የተመሠረተ ነው ። ማኅበራዊ ኑሮ በብዙ መንገዶች ሊጎዳ ይችላል ። የብቸኝነትና የጭንቀት መንፈስ ሲታገለን ማኅበራዊ ኑሮአችን እየተጎዳ ይመጣል ። መሸሽን ገለል ብሎ መቀመጥን እንወዳለን ። አንዳንድ ጊዜም ከትዳራችንና ከልጆቻችን መሸሽ ይታየናል ። የብዙ ትዳር ችግር ማንም ያላወቀው ጭንቀት ነው ። መነጫነጩ ፣ ስካሩ ውጤት ነው ። መነሻው ግን ጭንቀት ነው ። ሥሩን ካልፈወስን ቅርንጫፉ አይድንም ። ስለ ሰዎች ያለን ተገቢ ያልሆነ አመለካከት ይኖራል ። ይህ ከቤተሰብ ፣ ከአስተዳደግና ከደረሰብን ጉዳት የተነሣ የሚመጣ ነው ። በዚህ ምክንያት ከማኅበራዊ ኑሮ እንርቃለን ። ልጆች ሲያድጉ ከሰው ጋር እንዲቀላቀሉ ፣ ሰርግም ልቅሶም እንዲያዩ ተደርገው ሊሆን ይገባል ። ዛሬ ብንሸፍናቸው ነገ ብቻቸውን ይጋፈጡታል ። ልጆችን ተክቶ የሚኖር ወላጅ ሞቱን የረሳ ወላጅ ነው ። ዘመናዊነት ማኅበራዊነትን እየናደ ነው ። የትዳር ክፍተቶች ፣ የፍቺ መበራከቶች ማኅበራዊነትን ይጎዳሉ ። የሚሰሙና የሚታዩ ዘግናኝ ወንጀሎች ሰውን ፈሪ በማድረግ እንዲራራቅ ያደርጉታል ። ወንድ ልጃቸውን ለሴትም ለወንድም አደራ ብለው ለመሄድ የተቸገሩ ወላጆች አሉ ። የሚሰሙት ነገር ሕሊናቸውን አርክሶታል ፣ ልባቸውን ፈሪ አድርጎታል ። የገዛ ሴት ልጃቸውን ለአባት ትተው መሄድ የሚፈተኑ እናቶችን እናውቃለን ። ማኅበራዊነት በአባትና በልጅ መካከል ከፈረሰ ሌላ ቦታ መጠበቅ ከባድ ነው ።

ዘመናዊው ዓለም የግል የሆኑ ነገሮችን በማብዛት አንድነትን የማፍረስ ዘመቻ ላይ ነው ። በየጊዜው በላቦራቶሪ ተመርተው በሚለቀቁ በሽታዎች ሰው ሰውን እንዳይቀርብ ሰይጣናዊ ተልእኮአቸውን እየተወጡ ነው ። በዚህ ምክንያት የሰው ልጅ በብቸኝነት ዕድሜው እያጠረ ይመጣል ። ማኅበራዊነት ዕድሜን ይቀጥላል ፣ ደስታንም ይሰጣል ። አብረው ካልበሉ ፣ አብረው ካልተደሰቱ ፣ አብረው ካላለቀሱ የዚህ ዓለም ኑሮ ሊገፋ አይችልም ። ራስ ወዳድነትና ስስት ፣ ሁሉንም ነገር ስሌት ውስጥ ማስገባት የማኅበራዊነት ጠላት ነው ። ለሌሎች ስንኖር ሌሎች ለእኛ ይሞቱልናል ። የምናጭደው ከዘራነው በላይ ነውና ። ደግሞም ውጤቱን በማሰብ ሳይሆን በራሱ ትልቅ ደስታ በመሆኑ ማኅበራዊነት ሊጠነክር ይገባዋል ። አንተም ማኅበራዊነት አስፈላጊህ ነውና የሠራኸውን የግል ደሴት አፍርሰህ ከሰው ተቀላቀል ! ሞኝ አትሁን ከምትሰጣቸው የሚሰጡህ ይበልጣል ! ፌስ ቡክ ላይ ልቅሶ መድረስ ፣ ቲክ ቶክ ላይ ሙሾ ማውረድ ቁምነገር አይምሰልህ ፣ የቀኑ የወሬ ጥማትህ ማሟያ ወይም ምን ላውራ ለሚለው ጭንቀትህ ማረፊያ ነው ! ማኅበራዊነት አካላዊነት ነው ! መሄድ ፣ ጊዜ መስጠት ፣ አቅፎ ማጽናናት ፣ በጎደለው መሙላት ነው !

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 14 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም