መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት 4

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት 4

3- ንጽሕናህን ጠብቅ

ንጽሕና ከሃይማኖት ጋር በጣም የተያያዘ ነው ። በአይሁድ ፣ በክርስትና ፣ በእስልምና ሃይማኖት ንጽሕና ትልቅ መስፈርት የሚሰጠው ነው ። ሃይማኖት ስለ ሥጋና ነፍስ ንጽሕና የሚያስተምር ነው ። “ገላ ቢያድፍ በውኃ ፣ ነፍስ ቢያድፍ በንስሐ” እየተባለ የሚነገረው በሥጋም በነፍስም ንጹሕ መሆን ስለሚገባ ነው ። የብሉይ ኪዳን የሥርዓት ሕግ በዋናነት ንጽሕና ላይ አትኩሮት ያደርጋል ። ስለ ማኅበረሰብ ጤናም ግድ ይለዋል ። እግዚአብሔር ውኃን የፈጠረው እንድንታጠብ ነው ። እያንዳንዱ እስራኤላዊ ግላዊ ንጽሕናውን መጠበቅ እንዳለበት ትእዛዝ ተሰጥቶታል ። ተላላፊ በሽታ የያዘው እንደሆነው የማግለያ ቦታዎች ተለይተዋልና እስኪድን ድረስ በዚያ ማሳለፍ ነበረበት (ዘሌዋ. 15)። ዛሬ ወረርሽኝ ሲከሰት የማቆያ ጣቢያ ሲዘጋጅ እናያለን ። ይህ ግን ከዛሬ ሦስት ሺህ ዓመት ጀምሮ በእግዚአብሔር ሕዝብ የተለመደ ነበር ። የማኅበረሰብን ጤና መጠበቅ ተገቢ ነው ። ተላላፊ በሽታ ይዞ ፣ ያንን መደበቅና ሌላውን ሰው ተጠቂ ማድረግ እንደ መግደል ይቆጠራል ። እስራኤላዊ ሰፈሩን የማጽዳት መለኮታዊ ትእዛዝ ነበረበት ። ዛሬ ራሱን የሚያጸዳ ሰው ቤቱን ያዝረከርካል (ብዙ ጊዜ የቆንጆ ቤት ዝርክርክ ነው)። ቤቱን የሚያጸዳ ደግሞ ሰፈሩን ያቆሽሻል ። በየመንገዱ የበሉበትን ተወጋጅ ነገር የሚጥሉ ፣ ከቤታቸው ወጥተው ደጅ ላይ የሚሸኑ ብዙ ናቸው ። እኛ ያቆሸሽነውን የሚጠርጉ አንዳንድ ልበ ቅን ሰዎች በየሰፈሩ አሉ ። እነዚህን ሰዎች ከማመስገን ይልቅ እንደ ተለከፉና በየቆሻሻው እንደሚንከራተቱ መቍጠር ይቀናናል ።

ሰፈሩን የማያጸዳ ክርስቲያን በብሉይ ኪዳን ቢሆን ትልቅ ቅጣት ይጠብቀው ነበር ። የአንድ አገር ሥልጣኔ የሚለካው በንጽሕናው ፣ ቆሻሻን በሚያስወግድበት መንገድና ቆሻሻን እንደ ሀብት በሚጠቀምበት አሠራር ነው ። በእግዚአብሔር ድንኳን በሚቀርበው አገልግሎት ተረፈ መሥዋዕቱን የማስወገጃ ትእዛዝ ነበረው ። ከሰፈር ውጭ አውጥተው እንዲጥሉ ወይም እንዲቀብሩ ታዘዋል ። ንጽሕናን መጠበቅ ፣ ቆሻሻን በተገቢው መንገድ ማስወገድ አምልኮት ነው ። አምልኮ መዘመር ፣ መቀደስ ብቻ አይደለም ። ንጽሕናን መጠበቅም አምልኮ ነው ። ሥጋዊ ንጽሕና ማለታችን ነው ። ገላ መታጠብ ፣ ልብስ ማጠብ ፣ ቤት መጥረግ እያልን ነው ።

በቃና ዘገሊላ ስድስት የድንጋይ ጋኖች ነበሩ ። እንደ አይሁድ ልማድ የማንጻት ሥርዓት ለመፈጸም የተቀመጡ ነበሩ ። ሰርገኛው ሲገባ እየታጠበ መግባት ነበረበት ። ዛሬ እንኳ ሰርግ ቤት ውኃ አይቀመጥም ። ንጽሕና ትልቅ ዋጋ ያለው ነገር ነው ። ጌታችን ውኃውን ወደ ወይን ጠጅ የለወጠው በእነዚህ ጋኖች ላይ ውኃ ከተጨመረ በኋላ ነው ። (ዮሐ. 2 ፡ 6 ።) በምሴተ ሐሙስ የደቀ መዛሙርቱን እግር አጥቧል ። የቍርባን ቅዳሴ ሲከናወንም በሁሉም አብያተ ክርስቲያናት መታጠብ ግድ ነው ። እየበረታን ስንመጣ እያንዳንዱ ቀዳሽ ልብሰ ተክህኖውን ከመልበሱ በፊት ሙሉ ገላውን ታጥቦ መሰየም አለበት ። ይህ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ይደረጋል ። በእስልምናም ከጸሎት በፊት መታጠብ ግዳጅ ነው ። በአላዋቂነት “እግዚአብሔር ያለው ልባችሁን ታጠቡ ነው ፣ እግራችሁን አይደለም” እያልን እንተቻለን ። እኛም እግር መታጠቢያ ቢኖረን ክብር እንጂ ውርደት አይደለም ። ጫማ አውልቀን ስለምንገባ ፣ ስለምንሰግድ መንጻት ግድ አለብን ። በእውቀትም በሕይወትም የበረቱ አባቶች ንጹሐን ነበሩ ። ለመጸለይም ንጹሕ አካልና አካባቢ ያስፈልገናል ። ተባይ እየጨፈረብን መጸለይና መመሰጥ ሊኖር አይችልም ። በግብጽ ላይ ከወረደው መቅሰፍት አንዱ ቅማል ነው (ዘጸ. 8 ፡ 16) ። ተባይን እንደ በረከት የሚያይ ካለ ጤንነቱ መገምገም አለበት ።

ንጹሕ ልብስ የሚለብስ ፣ ሽቱ የሚቀባ መነኵሴ ሲገጥመን እንደ ዓለማዊ ሰው ማየት የተለመደ ነው ። የሽቱ ቅመማውን ሳይቀር ለሙሴ ያስጠናው ራሱ እግዚአብሔር መሆኑን እንዘነጋለን (ዘጸ. 30፡23፣34)። ብፁዕ ቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ሽቱ ተቀቡ ተብሎ መጽሐፍ ተጽፎባቸዋል ፣ ብዙ ስድብ አስተናግደዋል። ንጽሕናን መጠበቅ ዓለማዊነት ሳይሆን መንፈሳዊነት ነው ። ዓለምን ከንቱ ነው የምንለው ለገንዘብ ባለመስገብገብ ፣ ወንድምን ከወደቀበት በማንሣት እንጂ በመቆሸሽ አይደለም ። የክርስትናው ትእዛዝ ራስህን ካድ እንጂ ራስህን ጣል የሚል አይደለም ። መቆሸሽ መንፈሳዊነት ሳይሆን ስንፍና ነው ። ሁላችንም ብንሆን ንጹሕ ሰው ይማርከናል ። መልካም መዓዛ ያለውንም አንጠላም ። እኛም ተወዳጅ ሰዎች የምንሆነው ንጽሕናችንን በመጠበቅ ነው ። ልንሸት የሚገባው ቆሻሻ ሳይሆን ውኃ ፣ ውኃ ብቻ ነው ። ንጽሕናን አለመጠበቅ ድብርት ውስጥ ይከታል ። አጠገባችን ላለውም ሰው ፈተና መሆን ነው ። “ሰውን ሲወዱ ከነንፍጡ ነው” የሚባለው አይሠራም ። በዚህ ዘመን ሰውን መውደድ ንፍጡን ጠርጎ ነው ። እኛ ከነንፍጡ ልንስመው እንችላለን ። የሚበዛው ሰው ግን ይጸየፈዋል ። ይልቁንም ጓደኛ ሆኖ የጓደኛውን የንጽሕና ጉድለት የማይነግር ካለ ጓደኛ አይደለም ።

ዐፄ ቴዎድሮስ አንድ ባለጉዳይ በፊታቸው ቆሞ ንጽሕናውን በቅጡ ስላልጠበቀ ፣ “ጓደኛ አለህ ወይ?” ብለው ጠየቁት ። እርሱም ቢያዝኑልኝ ቢፈርዱልኝ ብሎ መልካም ጓደኛ አለኝ ብሎ ነገራቸው ። ያም ጓደኛ ተጠርቶ መጣ ። “እንዴት ጓደኛው ከሆንህ ንጽሕናውን እንዲጠብቅ አልመከርከውም ?” ብለው አርባ ጅራፍ ገረፉት ። ዛሬም ጓደኛው ራሱን ሲጥል ዝም ብሎ የሚመለከት ቅጣት ይገባዋል ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 12 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም