መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (41)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (41)

የውሸት ኑሮ አቁም – ክፍል 2

ብዙ ኑሮአችን በውሸት የተሞላ ነው ። ውሸት ከእውነት በላይ ዋጋ ያስከፍላል ። “እውነቱን ተናግሮ የመሸበት ማደር” እንዲሉ እውነት ለጊዜው መራራ ቆይቶ ጣፋጭ ናት ። ውሸት ለጊዜው የሚጣፍጥ እስከ መጨረሻው ግን የሚመርር ነው ። ስንዋሽ ያንን ግለሰብና ያንን ተቋም በእውቀት በለጥኩት የሚል ስሜት ያሳድርብናል ። ቆይቶ ግን ነገሮችን ጨለማ ያደርግብናል ። የውሸት ጋብቻዎች ብዙ ዋጋ ያስከፍላሉ ። ከአገር ለመውጣት የሚገባባቸው የውሸት ጋብቻዎች ብዙ መቀያየም ያመጣሉ ፣ የጋብቻንም ክብር ይጥላሉ ። የመጣው ውጤትና የተከፈለው ዋጋ አልመጣጠን እያለ ደስታን ይነሣል ። ለዚህ ነው ወይ ይህን ሁሉ ዋጋ የከፈልኩት  ያሰኛል ። የትም ቢሄዱ ሰማይና አፈር አንድ ነው ። ይኸው ሰማይ ፣ ይኸው አፈር ነው ያለው ። ሁሉም ቤት የራሱ የሆነ ልቅሶ አለው ። እዚህ የእንጀራ ጥያቄ እዚያ ያለመርካት ጥማት አለ ። ድሀ ቸገረኝ ይላል ፣ ሀብታም ጨነቀኝ ይላል ። ችግር በዕለት ጉርስ ጸጥ ይላል ። የጨነቀው ግን አገር ካገር ቢንከራተት ፣ ቤቱን ትቶ ጭፈራ ቤት ቢያድር አይታገሥለትም ። ቸገረኝ ከሚል ጨነቀኝ የሚል ያሳዝናል ። የቸገረውን ድሀ ሁሉ ያዝንለታል ፣ የጨነቀውን ባለጠጋ ግን የሚያዝንለት የለም ። በትልልቅ ቤት ትልልቅ ጥያቄ አለ ። በትልልቅ ቤት ትልቅ ጉድ አለ ።

ውሸት በልምምድ እንኳ ትክክለኛውን መልክ መምሰል ይሳናታል ። ረጅም ጊዜ መተወን አይቻልም ። ለአንድ ሰዓት ተውኔት አንድ ዓመት ተለማምደው ያውም አይሳካላቸውም ። እውነት ወጪዋ ትንሽ ነው ። የሐሰት በጀት ግን ብዙ ነው ። ሰው ከውሸት አገኘዋለው የሚለውን ለእውነት ቢኖር ያገኘው ነበር ። እውነትን በእንቅልፍ ልባችንም ልንናገረው የምንችለው ነው ። ውሸት ስንናገር የልባችን ትርታ ይጨምራል ። ስጋታችን ከፍተኛ ይሆናል ። በቆራጥነትና በመታገል የምንደርስበትን ስኬት በውሸት ማግኘት አስፈላጊ አይደለም ። ዛሬ ዓለምን በአእምሮ ቅኝ የሚገዙት በኳስና በፊልም አብዮት ነው ። የኳሱ ደጋፊ ሁልጊዜ ተዝናንቶ የሚኖር አይደለም ፣ በሰለጠነው ዓለም ያለው ደጋፊ ጭንቀቱን የሚያስተነፍስበት ስፍራ ነው ። ፊልሙ ሐሰተኛና ብዙ ወጣቶችን የሚያሳስት ነው ፣ የሆሊውድ አባላት በዓለም ላይ በጭንቀት በመማቀቅ ቀዳሚ ናቸው። በፊልም እንደ ሠሩት ዝሙት ያንን ያህል ረጅም ደስታ የለውም ። የፊልሙን ቅንብር በእውነተኛው ኑሮ ውስጥ ፈልገው ያጡ ወጣቶች ለጭንቀት ይዳረጋሉ ። እንደ ሌሎች ለመልበስ ፀጉርን ለመቆረጥ መሞከር ራስን የማጥፋት ወንጀል ነው ። የምንኖረው የራሳችንን ኑሮ ሊሆን ይገባዋል ። የውሸት ቤት ሳይፈርስ አይቀርም ።

ከራስ ፀጉር እስከ እግር ጥፍር የራሳቸው ባልሆነ ነገር የሚብለጨለጩ አሉ ። ለዚህ ከፍተኛ ወጪ ያወጣሉ ። አገራት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የሚያወጡት ለመዋቢያ ነገሮችም ነው ። ተፈጥሮአቸውን ሳይጠቀሙ የሌሎችን የጌጥ ገበያ የሚያደምቁ ወጣቶች ያሳዝናሉ ። ፀጉር እያላቸው ፀጉር ይገዛሉ ። የልጅነት አፍላ መልክ እያለ ሜካፕ ይሸምታሉ ። የጌጣጌጥ ትልቁ ችግር ያንን ጌጥ ካላደረጉና ያንን ሽቱ ካልተቀቡ የመቆም ድፍረት የሚያሳጣ ነው ። ሰው ሠራሽ ነገር ሁሉ የራሱ ችግር አለው ። እነ ማይክል ጃክሰን ቆንጆ ጥቁር ነበሩ ፣ መልካቸውን ወደ ነጭ ሲቀይሩ የመኖር አቅምና ዕድሜ አላገኙም ። ራስን መሆን ውሸትን ድል መንሣት ነው ። እንደ እነ እገሌ ማውራት የሚፈልጉ ሰዎች ከላይም ከታችም ብዙ ናቸው ። በርግጥ የማረኩን ሰዎች በውስጣችን ይገዙናል ። የሌሎችን ስንይዝ የራሳችንን ጥለን መሆን የለበትም ።

ሰርግ መልካም ነው ። አዳምና ሔዋን ግን እንደ ተጋቡ እንጂ እንደ ተሰረጉ ብዙ አናውቅም ። እግዚአብሔር ያቀደላቸው ለሰርግ ሳይሆን ለጋብቻ ነው ። በእውነት ባንተ ሰርግ ከልቡ የሚደሰት ሃያ ሰው ካገኘህ በጣም ሀብታም ነህ ። ታዲያ ሺህ ሰው መጋበዝ አስፈላጊህ አይደለም ። አንዳንዱ ከሥራው ውጥረት የተነሣ ሰርግህ ላይ የመጣው እንዳትቀየመው ነው ። ከዚህ ሁሉ በላይ የኪራይ ቤት ልትገባ የሚሊየን ብር ሰርግ መሰረግ ይህ የውሸት ኑሮህ ውጤት ነው ። ሰርግህን የንጉሥ አድርገህ የችግረኛ ኑሮ ከመኖር ፣ ሰርግህን ቀልጠፍ አድርገህ የሰርግ ያህል መኖር የተሻለ ነው ። በልቶ ለማያመሰግንና አቃቂር ለሚያወጣ ሰው ብዙ መድከም አስፈላጊ አይደለም ። ዝክር ቢሆን በረከት ታገኝበታለህ ፣ እግዚአብሔርም ዋጋ ይከፍልሃል ። አጉል ወጪህ ግን አንተኑ አራቁቶ ይቀራል ።

ቤትህን እያስራብህ በደጅ ብዙ ገንዘብ ለጥጋበኛ ትበትናለህ ። ይህ የውሸት ኑሮ ነው ። በደጅ የጋበዝካቸው የወደቀውን ቤትህን ሲያዩ ለእኛ ብሎ ነው አይሉህም ፣ ይልቁንም ይታዘቡሃል ። ስትታመም የምትጠራው ያችው ሚስትህ ናት ። የጋበዝካቸው ቀብርህ ላይ እንኳ ላይገኙ ይችላሉ ። የጉራ ኑሮህን ተጸየፈው ። ከልብህ ሳትወዳቸው እነ እገሌን እንደ ወደድህ አድርገህ አታስመስል ። መውደድ በራሱ መፍቀድ የሚል ትርጉም ያለው ነው ። መቼም መሣሪያ ተደግኖበት የሚወድድ ማንም የለም ። ዛሬ ንግግራችን ራሱ ግራ የገባው ነው ። እወድሃለሁ ግን ላፈቅርህ አልቻልኩምና ተለያይተናል የሚሉ ሰዎችን እንሰማለን ። መውደድና ማፍቀር የአማርኛና የግእዝ ጉዳይ ካልሆነ ሁለቱም ተመሳሳይ ነው ። አዎ ከእውነቱ ስሜቱን የሚያምን ትውልድ ለውሸት ኑሮ ተላልፎ ይሰጣል ። በትክክልም ሰውን ላንወድ እንችላለን ። የምንወደው ስሜታችንን ነው ። ያንን ስሜታችንን ያጋጋለ ሰው እርሱን ካልያዝሁ እንላለን ። ከአቅም በላይ ልጆችህን አታሳድግ ። ያጣህ ቀን ጠላት ይሆኑሃል ። በልክ መኖር ከጭንቀት ያድናል ። ከመሬት ብዙም ያልራቁ ለመውደቅ አይሰጉም ። ትንሽ ስታገኝ ሀብታም ሰፈር ለመከራየት አትቸኩል ፣ ማግኘትህን በትክክል አረጋግጥ ።

ከሌሎች ጋር ቁመት እየተለካካህ አትኑር ። ሽንገላን ተጸየፈው ። የዝሙት አዳሪዎች እንጂ ጨዋ ሰዎች ሸንጋይ አይደሉም ። ልጅህን በአቅምህ አሳድገው ። የልኩን እንጂ የትላንት አስተዳደግህን ለመካስ ብለህ ከመጠን በላይ አትመግበው ። የማትኖረውን ኑሮ በፎቶ ላይ እያስዋብህ አትልቀቅ ። ዘመኑ ያልኖረ መልክ እየሰጠህ ያታልልሃል ። ማድያቱም ፣ ጥቁረቱም የመኖርህ ትርፍ ነውና ውደደው ። በዚህ ዓለም ላይ እንኳን ሰው ድንጋይም ይጠቁራል ፣ ድንጋይም ይከሳል ። ውሸት ፕራንክ ተብሎ በመጣበትና በሚያዝናናው ዘመን ስለ ውሸት መጻፍ በራሱ ተጠዪ ያደርጋል ። የሰውን ሥራ እየሰረቁ አዋቂ ፣ ደራሲ የሚባሉ ባሉበት ዘመን ውሸት ኃጢአት ነው ማለት ብዙ ጠላት የሚያስነሣ ነው ። ፖለቲካው ከጅማሬ እስከ ፍጻሜ ውሸትን ጌጥ ባደረገበት ዘመን ለእውነት መኖር ባንዳ የሚያሰኝ ነው ። ቢሆንም ለእውነት ኑር ። ሞት አይቀርምና ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 18 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም