መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት 5

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት 5

…. ንጽሕናን መጠበቅ

ነጻነትን ከሚሰጠን ነገር አንዱ ንጽሕናን መጠበቅ ነው ። ገላችን ከቆሸሸ ፣ ልብሳችን ንጹሕ ካልሆነ ራሳችንን እንኳ መውደድ እንቸገራለን ። አንድ የተሟላ ሰው ላዩም ውስጡም ፣ ሥጋውም ነፍሱም ንጹሕ ሲሆኑ ነው ። ቤተ መቅደስ ንጹሕ መሆን አለበት ። በየትኛውም ሃይማኖት በየትኛው አገር ያለ መቅደስ ንጽሕና ቀዳሚ መገለጫው ነው ። ሰው የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ነው ። በወርቅና በብር የተገዛ ሳይሆን በእግዚአብሔር ልጅ ክቡር ደም የተገዛ ሕንፃ ሥላሴ ፣ ታቦተ መንፈስ ቅዱስ ፣ ማኅደረ መለኮት ነው ። ስለዚህ ንጹሕ መሆን አለበት ። ይልቁንም የሃይማኖት አባቶች የንጽሕና ምሳሌ ናቸው ። ሕዝቡንም ስለ ንጽሕና ሊያስተምሩት ይገባል ። እግዚአብሔርን የሚወድድ እግዚአብሔር የፈጠረውን ይወድዳል ። ተፈጥሮ የእግዚአብሔር የፍቅሩ ውጤት ነው ። በንጽሕና ጉድለት ተፈጥሮ እየተጎዳ ነው ። ወንዞች ይበከላሉ ። ውቅያኖሶች በተለያዩ ዝቃጮች ምክንያት በውስጣቸው የያዙትን ፍጥረት እያጡ ነው ። ንጽሕና የፍጥረት ሕይወት ነው ። እግዚአብሔርን የሚወድ ሰው ፍጥረትን ይወዳል ። የምድሪቱ ትልቅ ፍጡርና ባለ አደራ የሆነው ሰውም ተፈጥሮን የመጠበቅና የመንከባከብ ግዳጅ አለበት ።

ንጽሕናን ለመጠበቅ የተሻለ አስተሳሰብና የሞራል ግንባታ እንዳለን የሚጠበቅ ነው ። ነገር ግን መልእክትን ማስተላለፍ ስለሚገባ ስለንጽሕና ማስተማር ይገባናል ። በተለያዩ ትልልቅ ተቋማት ሠራተኞች ከመቀጠራቸው በፊት ይህ ትምህርት ይሰጣል ። የተከበሩ ሰዎች ሾፌር የሚሆኑ በታላቅ ጥንቃቄ ስለንጽሕና ትምህርት ይሰጣቸዋል ። ሕዝብን በማገልገል ላይ ያሉና ዓለም አቀፍ ተቋማት ትኩረት ሰጥተው ስለንጽሕና ያስተምራሉ ። እኛ ግን የእግዚአብሔር ቃል ስለ ሁሉም የሕይወት ክፍል የሚናገር ነውና መጽሐፉን መሠረት አድርገን እንናገራለን ። የቀደሙ አባቶችም ብሉያትና ሐዲሳትን ብቻ ሳይሆን ንጽሕናን መሠረት አድርገው ያስተምሩ እንደነበር እናውቃለን ።

አንተ ብርቱ የእግዚአብሔር ልጅ ሆይ በምድር ላይ እንደ ተራ ሰው ፣ እንደ መንገደኛ ፣ እንደ ዘዋሪ ሳይሆን እንደ ልዑል የተቀመጥህ ነህ ። ኑሮ ከርታታ ቢያደርግህ እንኳ ግብህ ሰማይ ነው ። የንጉሥ ልጅ ነህና ራስህን መጠበቅ አለብህ ።

መኝታህ ንጹሕ ይሁን ። በዚህ ዓለም ላይ በትክክል የምትጠቀመው አልጋህንና መኪናህን ነው ። ስለዚህ መኝታህ ንጹሕ መሆን አለበት ። አልጋ ላይኖርህ ይችላል ። ባለጠጋ ስትሆን መሬት ተኛ ተብለህ ትታዘዛለህ ። ስላለህ ትጠቀማለህ ማለት አይደለም ። ብዙ ሰው የገንዘቡ ተመጋቢ ሳይሆን ተመልካች ነው ። ብቻ መኝታህ ንጹሕ ይሁን ። በየሳምንቱ አንሶላህን ቀይር ። የትራስ ጨርቅህ ውኃ ፣ ውኃ ብቻ መሽተት አለበት ። ከመኝታህ እንደ ተነሣህ ወዲያው አልጋህን አታንጥፍ ። ገልጠህ ቢያንስ ለአንድ ሰዓት ነፋስ እንዲያገኝ አድርግ ።

የራስህን ንጽሕና ጠብቅ ። ከመኝታህ እንደ ተነሣህ ታጠብ ። ጥርስህን አጽዳ ። የምንበላው ምግብ ቀለም ስላለው ያንን በመፋቂያ ፣ በጥርስ ክፍተት መሐል የሚጠቀጠቀውን ደግሞ በብሩሽ አጽዳ። ከመኝታ ስትነሣና ወደ መኝታ ስትሄድ ጥርስህን ማጽዳት አስፈላጊ ነው ። ማንኛውንም ምግብ ከበላህ በኋላ አፍህን በውኃ ተጉመጥመጥ ። እግዚአብሔር የማሽተት ጸጋን የሰጠን ራሳችንን እንድንቆጣጠር ነው ። ስለዚህ ገላህን ፣ ልብስህን በማሽተት ንጽሕናውን አረጋግጥ ። ሰዎች ቢታዘቡህ እንጂ አይነግሩህምና ራስህን አዳምጥ ። በየዕለቱ የጫማ ወይም የእግር ሹራብህን/ካልሲህን/ ቀይር ። በየዕለቱ እግርህን ታጠብ ። በቁም እያለህ እግርህ ሞቶ መሽተት የለበትም ። ንጽሕናን ለመጠበቅ እጮኛ መያዝ ፣ ስብሰባ መሄድ አያስፈልግህም ። ለራስህ ክብር ንጹሕ ሁን ።

እንደ ሥራህ ጠባይ መታጠብ አለብህ ። ቆሻሻ ለመንካት ቅርብ የሆነ ሥራ ከሆነ በየዕለቱ መታጠብ ግድ ይላል ። ሽቱም የሚጣፍጠው ንጹሕ ገላ ላይ ሲያርከፈክፉት ነው ። በቆሸሸ ገላ ላይ ሽቱ ቢቀቡ ይከፋል እንጂ አይሻልም ። አካባቢያችን ሲቆሽሽ ዝንቦች ተዋጊ ሆነው ይመጣሉ ። አጽዱ ማለታቸው ነው ። ጅቦች ቤታችን ድረስ አንኳኩተው የሚመጡት ቆሻሻ ካላነሣን ነው ። በደመ ነፍስ ያሉት ፍጥረታት ሳይቀር ስለ ንጽሕና እንድንተጋ ያደርጉናል ። ከሁሉ በላይ ጤናችንን ፣ ክብራችንን ፣ ተወዳጅነታችንን ለመጠበቅ ንጽሕና አስፈላጊ ነው ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 17 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም