መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት 7

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት 7

አጉል ልማዶችን ተዉ

አጉል ልማዶችን ከሥር ጀምሮ ወላጆች ያስጥሉናል ። ቀጥሎ መምህራን ያስተዉናል ። መጻሕፍትም እንደ ሸለፈት የሆነውን ፣ ውበትና ጤንነትን የሚጎዳውን ክፉ ልማድ እንድንተው ያግዙናል ። የሰው ልጅ በሕይወት እስካለ ድረስ ለማወቅና ለንስሐ ጊዜው አይረፍድበትም ። አጉል ልማድ ባለማወቅ ምክንያት ፣ ሥነ ሥርዓትን ባለመማር ፣ ልቅ በሆነ ባሕል ውስጥ በማደግ ፣ ሥልጣኔ በሚመስል ዘላንነት በመያዝ ሊመጣ ይችላል ። አጉል ልማዶች እጅግ ብዙ ሲሆኑ ሁሉንም መንቀስ አይቻለንም ። አጉል ልማዶች ትንሽ የሚመስሉ ትልቅ ጥፋት የሚያስከትሉ ናቸው ። አጉል ልማድ ውስጥ ካለን ከሰዎች ጋር እንጋጫለን ። ሰዎች ባይጋጩንም ለእኛ ያላቸው ክብር ይቀንሳል ። አንዳንድ ሰዎች ሊነግሩን ይችላሉ ። የሚበዙት ግን እየታዘቡ ዝም ይሉናል ። በአፍ መፍረድ ፣ በልብ መታዘብ ሁለቱም አንድ ዓይነት ኃጢአት ቢሆንም ሰዎች ታዝበው ዝም ይሉናል ። መመከርን መቋቋም የማንችል ፣ ግን ብዙ ግድፈት ያለብን ሰዎች ልንሆን እንችላለን ። በዚህ ምክንያት የበለጠ እኛን ላለማጣት ዝም የሚሉን ይበዛሉ ።

መኝታ አታብዛ ። ገንዘብ እየፈለግህ መኝታ እያበዛህ አይሆንም ። አንተ እንድትተኛ የተጉልህ ሰዎች ይኖራሉ ። ነገር ግን እነርሱ ጊዜያዊ እንጂ ዘላለማዊ በረከቶችህ አይደሉምና እልፍ ይላሉ ። ያን ቀን በራስህ መቆም ያቅትሃል ። የራስህ ሕይወት ስለሌለህ የእነርሱ ህልውና ሲያበቃ ያንተም ያበቃል ። ወረተኛ አትሁን ። ሸሚዝ እንጂ ሰው አይቀያየርም ። ቶሎ ስልቹ ሆነህ መልሰህ እገሌን አታሳዩኝ ፣ አታሰሙኝ አትበል ። ሰው ብዙ ነው ፣ ሰው ጥቂት ነው ። ካከበርከው ሰው ብዙ ነው ። ከናቅኸው ግን ሰው ጥቂት ነውና አንድ ሰውም ታጣለህ ። ወሬ አታጣጥም ። “ፐ ፣ ይገርማል ፣ እስኪ ንገኝ” እያልህ የወሬ ሱስህን አትወጣ ። አንዳንዱን ነገር ባትሰማው የተሻለ ነው ። ፊት ለፊት ልትነግረው የፈራኸውን ሰው ከኋላው አትማው ። ስታወራ ከንፈርህን እየመጠጥህ ፣ ግንባርህን እያሸህ አታውራ ። ስትሰብክ አትወራጭ ፣ ከቦታ ቦታ አትፍለስ ። እጅህን አታወናጭፍ ። ሰዎች በግልህ የነገሩህን ራሳቸው ያውሩ እንጂ ስማቸውን ጠርተህ በአደባባይ አታውራ።

ምግብ ስትመገብ በመጠኑ ጥቅልል እንጂ ሰሐኑን እንደሚወስዱበት ሰው ከልክ በላይ አትጠቅልል ። ጥቂት በጥቂት መጉረስ ክብር ነው ። ስትበላም አፍህን ገጥመህ ብላ እንጂ ስታላምጥ አጠገብህ ያለ ሰው መስማት የለበትም ። በትልቅ ማዕረግ ላይ ያለህ ከሆንህ በአደባባይ ምግብ አትብላ ። ጳጳሳት በአደባባይ ባይመገቡ ይመከራል ። ወደ ድግስ ስትጠራ በልተህ ሂድ ። በምንም መንገድ የሚያሰክር መጠጥ አትጠጣ ። ጠላት ያለበት ሰው በሴት ፣ በሆዱና በአልኮል መጠጥ ያጠምዱታልና ተጠንቀቅ ። ሰዎችን ስታወራና ስታናገር ፊት ለፊት እያየሃቸው ተነጋገር ። አፍረህ አንገትህን መቅበር ፣ እንደ ተንኮለኛም ግንባርህን አቀርቅረህ በዓይንህ ግልባጭ ሰውን ማየት በጣም ነውር ነው ። ሰው አፍ ውስጥ የምትገባ እስክትመስልም አፍጥጠህ አታነጋግር ። ሰዎቹን ራሳቸውን ተመልከት እንጂ የለበሱት ልብስ ፣ ያደረጉት ጫማ ላይ ዓይንህን አትላከው ። እንደ ውሻም እግር እግር አትመልከት ። ዜማ ስታዜም ፣ መዝሙር ስትዘምር የላይኛውንም የሥረኛውንም ጥርስህን አታሳይ ። ጥርሱን የሚያሳይ የሞተና የረገፈ አጽም ብቻ ነው ። እቤትህ ሳትጨርስ ደጅ ላይ ወጥተህ ቀበቶህን መፍታትና መዝጋት ነውር ነው ። በሰው ላይ ማዛጋት ፣ ሰው ፊት መሐረብ ሳይሸፍኑ ማሳልና ማስነጠስ ተገቢ አይደለም ። ቀጠሮ አክብር ። ሁለት ጊዜ ደውለህ ስልክ ያላነሣልህ ሰው ጋ መደወል አቁም ።

ሰዎችን ሰላም ብለህ ከሸኘህ በኋላ ዞር ብለህ አትመልከታቸው ። ጀርባን የሚያይ ጠላት ነውና ። ከሰዎች ጋር ሆነህ ስልክህን አትጎርጉር ። ከተከበረ ሰው ፊት እግርህን አጣምረህ አትቀመጥ ። ታላቅህ ሲመጣ ከመቀመጫህ ተነሥተህ ተቀበለው ። ሲደወልልህ ስልክህን አንሣ ። ማንሣት የማትፈልግ ከሆነ ጉዳዩን ገልጸህ እንዳይደውሉ አድርግ ። ሰዎችን በገዛ ስህተታቸው ይቅርታ አትጠይቅ ። ይህ እውነትን የሚቀብር ፣ መለማመጥን የሚያሰፍን ነው ። ደግሞም ስህተታቸውን እንዳያዩ አስተዋጽኦ ታደርጋለህ ። ካልተገራ ሰው ጋር ቀልድ አትቀልድ ። ባለጌ ሥራውን አይረሳምና ለመደ ብለህ በርህን አትክፈትለት ። ለሰዎች ቀጠሮ ስትሰጥ ጉዳዩንም አብረህ ንገራቸው ። “እፈልግሃለሁ ብርቱ ጉዳይ አለ ፣ አሁን አልነግርህም” እያልህ የሰውን ሰላም አትንሣ ። የማትጨርሰውን ወሬ አትጀምር ። “ይህ ለምን ሆነ ?” አትበል ፤ እንዲህ እንዲሆን እኔ ምን አጥፍቻለሁ ? ብለህ ታረም ። የማምሸት ልማድህን ተው ። በጊዜ መተኛትን ልመድ ። ሰዎች ሲናገሩ አታቋርጣቸው ። እኔ ብቻ ልናገር አትበል ። ሁሉን እንደምታውቅ ከተሰማህ ታመሃልና እርዳታ ያስፈልግሃል ። ምንም ብትቀራረብ ባለሥልጣንን በአደባባይ አንተ ብለህ አትጥራ ። የጎሣና የቋንቋ ትችት ያለበት ወሬ አትጀምር ። ያየኸውን የሰው ገመና ለሌላው አትናገር ። ይህ የጸሎት እንጂ የወሬ ርእስ አይደለምና ። መጓዝ ያለብህ ሰዎች እስከፈቀዱልህ ድረስ ብቻ ነው ። ያልተፈቀደልህን መስመር ስታልፍ የተፈቀደውንም ታጣለህ ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 24 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም