መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት 8

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት 8

መልካም ልማድን አዳብር

ዕለታዊ ማስታወሻ የመጻፍ ልማድ ፣ ውሎህ እንዴት እንደ ነበር የመመዝገብ ሥርዓት ይኑርህ ። የእጅና የእግር ጥፍርህን ተከታትለህ ቍረጠው ። ብዕር ወይም ጣትህን አፍህ ውስጥ አታስገባ ። ሁልጊዜ መስተዋት ተመልከት ። በዛሬ ጊዜ የገጽህን/የፊትህን ሁኔታ በትክክል የሚነግርህ መስተዋት ነው ። መስተዋት ላይ ብዙ አትቆይ ። ነገ አፈር መሆንህን እያሰብህም ሁልጊዜ ካልተሽቀረቀርኩ ብለህ አትጨነቅ ። ወዳጅህ የሞተ ቀን ባሕር አቋርጠህ ፣ አውሮፕላን ተሳፍረህ ከምትመጣ በቁሙ ብትጠይቀው የተሻለና እውነተኛነት ነው ። የመቃብር ላይ ድራማ መቆም አለበት ።

ከሌለህ ነገር ላይ አትቆጥብምና ካለህ ነገር ላይ አስቀምጥ ። መጽሐፍ ስጡ አለ እንጂ በትኑ አላለም ። ለልጆችህ ቤት ለመሥራት ፣ መኪና ለመግዛት ፣ ንብረት ለማስቀመጥ ፣ በስማቸው አክስዮን ለመግባት አትጨነቅ ። ልጆችህ የሚኖሩበትን መንገዱን አሳያቸው ። ልጆችህ በምትሰጣቸው የገንዘብ ብዛት የሚወዱህ እየመሰለህ ትታክታለህ ፣ ልትገዛቸው የፈለግህ ስለሚመስላቸው የበለጠ ይጠሉሃል ። ልጆችህን አስተምራቸው ፣ ሕይወትን እንዲጋፈጡ ጨክነህ ልቀቃቸው ።

ሕፃናትን አትጥላ ። በአሁን ጊዜ የማይበድሉን ምድራውያን መላእክት እነርሱ ናቸውና ። ዝም ብሎ የተቀመጠን ውሻ አትደብድብ ። አህያ ብዙ ዋጋ የከፈለች ፣ ነገር ግን ስሟና ሥራዋ ክብር ያላገኘ እንስሳ ናትና እርስዋንና እንስሳትን ስለማሳረፍ ሥራ ። አላዋቂ ሰው ቢበድልህ እንደ አዋቂ አድርገህ ግብግብ ውስጥ አትግባ ። ሰው የሚሰጥህ የልኩን ነውና አትደነቅ ። ቀጥሎ ምን ይሆን ብለህ አትጨነቅ ፤ ከዚህ በላይ የሚያስጨንቅ ነገር ቀጥሎ አይሆንም ። የታሸጉ ምግቦችን አታዘውትር ። ጣፋጭ ነገሮችን ቀንስ ። የተለያዩ ጥራጥሬዎችን በአንድነት ደባልቀህ አብስለህ ተመገብ ።

ለሰዎች ገንዘብ ስትሰጣቸው ከግንዛቤ ጋር ይሁን ። ከበርህ ስትወጣ ጀምሮ ላለው ድሀ ፣ ለሚጠብቀው ዘበኛ ትንሽ ትንሽ እየሰጠህ ሂድ ። ካላካፈልህ ነገ ተደራጅቶ ሙሉ ንብረትህን ያወድመዋል ። ስጡ ይሰጣችኋል የተባለው ጠላት ለመቀነስም ነው ። ስትሰጥ ሰላም ይሰጡሃል ። ስትራመድ ለየት ያለ ቄንጥ አትጠቀም ። ቀና ብለህም ሂድ ። አንገትህን መስበር ያለብህ ለአምልኮ ብቻ ነው ። ስትተኛ በግራ ጎንህ እግርህን ዘርግተህ መተኛትን አዘውትር ። በጾም ወራት መሬት ላይ መተኛት ትሕትናም ጤናም ነው ። ጾም ነው ብለህ አፍን ሳትታጠብ ፣ ጥርስህን ሳትቦርሽ እየሸተትህ አትውጣ ። ጾመኛ ይቀባባ ተብሎአልና (ማቴ. 6 ፡ 18) ።

ሌሊት ነቅተህ እንቅልፍ እንቢ ካለህ ቃለ እግዚአብሔር ከፍተህ ስማ ። አሳብህን ሰማያዊ አሳብ ይቆጣጠረዋል ። ሰላም ስለምታገኝ ትተኛለህ ። የምትበላውን ምግብ አስቀድመህ እየው ። ለመቆጣጠር ብቻ ሳይሆን ምግብ ቀለም አለውና የዓይን ጥጋብ ነው ። ቀጥሎ አሽትተው ። ምግብ መዓዛ አለው ። ተበላሽቶ እንደሆነም ትለየዋለህ ። በጥቂት ቅመሰው ። ከዚያ በኋላ ተመገበው ።

የሳምንት መርሐ ግብርህን አውጣ ። ከመርሐ ግብርህ አንድ መጽሐፍ ለመጨረስ እቅድ ይኑርህ ። አንድ ታማሚ ወይም እስረኛ ለመጠየቅም ለራስህ ግዳጅ ስጠው ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 25 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም