የእውነት አገሯ ፣ የፍቅር ድንበሯ፣ የፍትሕ ምንጯ ፣ የረድኤት መገኛዋ ፣ የኑሮ ዋልታዋ ፣ የሰላም አለቃዋ ፣ የኅብረት ማሰሪያዋ ፣ የቸርነት ነቅዕዋ ፣ የፍለጋ ማብቂያዋ ፣ የንባብ ትርጓሜዋ ፣ የትንቢት ፍጻሜዋ ፣ የዘመድ አውራዋ ፣ የወዳጅነት መለኪያዋ አንተ አይደለህም ወይ? የነገደ የሚያተርፈው ፣ የዘራ የሚለቅመው ፣ የወለደ የሚስመው ፣ የወጣ የሚገባው፣ በባሕር የሚሄደው ከማዕበል የሚተርፈው ፣ በአየር የሚበረው በሰላም የሚያርፈው ክርስቶስ ሆይ ባንተ አይደለም ወይ? የመሪው መሪ፣ የዓይናማው ብርሃን፣ የመንገድ መድረሻ፣ የእንባ ማበሻ ፣ የቀትር ጥላ፣ የሌሊት መጠጊያ ኢየሱስ ሆይ አንተ አይደለህም ወይ? እኔማ ምን አገር አለኝ ፣ አገሬ አንተ አይደለህም ወይ? ሁሉ ወገኑን ሲጠራ እኔ ግን የምጠራው ያላንተ የለም።
ሁሉን ማወቅ ብስጩ ፣ ሁሉን ማየት ስልቹ ያደርጋል። ባለጠጎች ንብረት ይዘው ራሳቸውን ከስረዋል ። ከነ መልኩ የሚሞት ፣ ከሃይማኖቱ ጋር የሚቀበር ይታጣል። ያዩት መከራ ተመልሶ ሲመጣ አዲስ ይሆናል። ዕድሜ ቁጠኛ ሲያደርግ የዋህ ሰው ሲያበርድ ደስ ይላል። የመልካሞችን መልካም አንተን ያገኘ ግን ከሁሉ ይድናል።
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጳጉሜን 1 ቀን 2017 ዓ.ም .