የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

የሚጮኹ ማረሻ አይስቡም

“እንቍራሪቶች ከበሬ የበለጠ ሊጮኹ ይችላሉ ። ነገር ግን እርሻ መሬት ላይ ማረሻ መሳብ ወይም መጥመቂያ መሣሪያ ማሽከርከር አይችሉም ። ቆዳቸውም ጫማ ለመሥራት አያገለግልም ።” /ካህሊል ጂብራን/

ሰው የሚሠራን አይወድም ። ከበሬ ይልቅ አንበሳን ያከብራል ፣ ከአህያ ይልቅ የሜዳ አህያን ፎቶ ያነሣል ። በሬ ክብሩን ያጣው በማገልገሉ ፣ አህያም የቆሸሸችው በሰው ሸክም መሆኑን ማንም አይገነዘብም ። ይቅር ባዩን ሰው በሬ ፣ ቻዩን አህያ ብሎ መስደብ የተለመደ ነው ። በሬ ብለው ከሰደቡን ትልቅ ምርቃት ነው ። በሕይወትም በሞትም የምናገለግል ነን ማለት ነው ። በሬ በቁሙ ያርሳል ፣ መጓጓዣ ይሆናል ፣ ዘር ይሰጣል ፣ በተዘዋዋሪ ወተት ያስገኛል ። ሙቶ ሥጋው ይበላል ፣ ቆዳው ልብስና ጫማ ይሆናል ። ኩሱ እንኳ ማገዶ ይሆናል ። አህያ ተብሎ ቢሰደብ የሚከፋው ካለ አላዋቂ ነው ። አህያ ትዕግሥተኛ ፣ ሽቶ ለመሸከም ብላ የቆሸሸች ፣ እህል ለማድረስ ብላ ዱቄት የመሰለች ፣ እየሄደች ስትደበደብ ፣ እየሠራች ስትሰደብ የቻለች ፣ ለውለታዋ ሌላ ጭነት ሲጫንባት የማትከፋ ፣ ትንሽ ተቀብላ ብዙ የምትሰጥ ፣ ሥልጣኔዎች ሳይመጡ የሰውን ድካም ያገዘች ናት ። ከሁሉ በላይ አህያ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የተሸከመች ፣ የሰላም ማብሰሪያ ፣ የጥንት ነገሥታት የምሥራች መንገሪያ ናት ። ለሚሠራ ሰው ክብር ስለሌለን ወረኞችን እየፈለፈልን ነው ። መዋሸትን እንደ ሥልጣኔ ስለቆጠርን ቀጣፊዎችን እያበዛን ነው ። የወደድነውን ሰው እጅ እግሩን አጣምሮ ቢኖርም መቀለብ አይሰለቸንም ፤ ከጠላነው ደግሞ ተራራ አቀበት ቢወጣ ፣ ሸለቆ ቁልቁለት ወርዶ ቢሠራ አንፈልገውም ። ሚዛናችን ሐሰተኛ ፣ ፍርዳችንም የተዋረደ እየሆነ ነው ። እግዚአብሔር ሁሉን ቢፈጥርም ሰዎች ካልሠሩ ሁሉም ነገር እየራቃቸው ይመጣል ። ለስንፍና ሁሉም ነገር ጠረፍ ፣ ለሥራ ግን ዳሩ መሐል ነው ። ሥራን የሚያከብር ፣ ሠራተኞችን የሚሸልም አገር ከፍታው አይደረስበትም ። ጠላቱም አሻቅቦ እያየው ሲታክት ይኖራል ። የማይሠራ ሕዝብ ዘረፋን ፣ እየገደለ የማክሰኞ ገዳይ ፣ የሐሙስ ገዳይ ተብሎ ሲወደስ መኖር የሚፈልግ ነው ። የዱር አራዊትን የጨረሰ ሰነፍ ሰው ነው ። የዱር ዛፎችን የጨረሰ ታካች ሰው ነው ። ቁጭ ብሎ መመገብን የሚወድ ፣ በሌላው ደም ወተት የሚጠጣ ገብር ሀካይ የተባለው ሰው ነው ።

በሬ ከሁሉ በላይ የሚያሳዝነው ወደ ማረጃው ስፍራ ሲወስዱት እየተቻኮለ የሚሄድ ነው ። ይህ ሁሉ ታታሪነቱ እውቀት ያንሰዋል ። ሥራ እንጂ ሴራ አያውቅም ። በሬ ካራጁ ይውላል እንዲሉ ።

አያ በሬ ሆይ ፣
ሞኙ በሬ ሆይ ፣
ሣሩን አየህና ገደሉን ሳታይ ፣
እልም ካለው ገደል ወደቅህብን ወይ ?

አንዳንድ ቀና ሰዎች ፣ ሥራ ሥራ የሚሉ ታታሪዎች ፣ እኔ ደግሞ ምን ጠላት አለብኝ የሚሉ ሁሉ ወዳጄ ነው ባዮች ፣ በእጃቸው ቅቤውን እያንጠባጠቡ ካላጎረሱ የሚከፋቸው ደጎች ፣ ወድቀው ለመማር የሚኖሩ ዘመን አባካኞች የክፉዎች ዒላማ ይሆናሉ ። በቁማቸው ጉልበታቸውን ይጠቀሙባቸዋል ። ወደ መታረጃቸውም ቄራ ፣ ወደ መውደቂያቸው ገደል ይነዱአቸዋል ። ከሞቱ በኋላም እነዚህ ጠላቶቻቸው አይተኙላቸውም ። ብዙ ክፉ አማካሪዎች ፣ ወዳጅ መስለው ወዳጅ የሚያሳጡ ምጽዋተኞች ፣ የዘላለሙን ክደው ለዕለት ያደሩ ምንደኞች ፣ ቀን ከሌሊት ላበላቸው ሳይቀር ጉድጓድ የሚቆፍሩ የማይለምዱ አውሬዎች ፣ እሳት ለኩሰው ሌላው ሲቃጠል ለመሞቅ የሚከጅሉ ሕሊና ቢሶች የአገር መሪዎችን ፣ የቀረቡአቸውን ወዳጆች ፣ ማኅበራዊ ኑሮን ያተራምሳሉ ። ታታሪነትን እንደ በሬ መያዝ ብቻ ሳይሆን እንደ እባብም ብልህነትን መያዝ ይገባል ። ፍጥረታት እግዚአብሔር እኛን የሚያስተምርበት ክፍሉም ፣ የማስተማሪያ ቁሳቁሱም ናቸው ።

መጮህ የሚችሉ መሥራት የሚችሉ አይደሉም ። ብዙ ኃይል የሚባክነው በአፋችን በኩል ነው ። ብዙ አቅም የሚዳብረውም በጆሮዎቻችን ነው ። ተፈጥሮአችንም አንድ አፍ ፣ ሁለት ጆሮዎች ያሉት ነው ። እንቍራሪቶች ይጮኻሉ ። ድምፃቸው ግን እለቁ ፣ እለቁ የሚል ፣ ሰላም የሚነሣ ነው ። የሚጮኹትም አደባባይ ወጥተው ፣ አትሮኖስ ተደግፈው አይደለም ። በውኃ ውስጥ ሰጥመው ፣ በጭቃ ውስጥ ላቁጠው ፣ በጢሻ ውስጥ ተሸሽገው ነው ። ሲጮኹ የሚውሉ ሰዎች ድምፃቸው ሰላማዊ አይደለም ። የሚረብሽ ወሬ ከሌለ ሥራ ያጣሉ ። ሥራ ሲያጡም የገዛ ወዳጃቸውን ቀደው ይሰፋሉ ። ልፋተኞች እነዚህን ወረኞች እየቀለቡ ቁጭ ብለው እንዲበሉ ያደርጓቸዋል ። የሚጮኹ ሰዎች በኢንተርኔት ጫካ ውስጥ ተሸሽገው እንጂ ገሀድ ወጥተው አይደለም ። ሠርተው ማሳየት አይችሉም ። ለሚሠራ ሰው ግን እንደ ቅንቅን ሆነው ዕረፍት ያሳጣሉ ። በጓዳ ተቀምጠው ስንቱን በረሃ ይሰዳሉ ፣ ከልጆቻቸው ጋር እየተጫወቱ ወላድን መሐን ያደርጋሉ ። ቀዝቃዛ ትኩስ እየተጎነጩ ሌላውን በረሀብ ያስጨርሳሉ ።

እየሠራን ከሆነ ብዙ አንጮኽም ። ምክንያቱም ሥራው ከሚናገረው በላይ መናገር አንችልምና ። የሚጮኽ ሰው መሥራት የማይችል ነው ። በሬ ዝም ብሎ ያርሳል ። እንቍራሪት ግን ብትጮህም ምንም ጥቅም አትሰጥም ። በሬ ሙቶም ቆዳው ጫማና ልብስ ይሆናል ፣ እንቍራሪት ግን ምንም ጥቅም አትሰጥም ። ለፍትሕ የሚጮኹ የተከበሩ ናቸው ። ራሳቸውንም መሥዋዕት የሚያደርጉ ናቸው ። ለሥራ የሚያነቃቁ የተከበሩ ናቸው ። ከፊት ቀድመው የሚያስከትሉን ናቸው ። መልእክት የሌለው ጩኸት የሚጮኹ ፣ የመናገር ግዴታ ያለባቸው እየመሰላቸው በማይመለከታቸው አስተያየት ሲሰጡ የሚውሉ ሰነፎች ናቸው ። አገር በተግባር እንጂ በወሬ አትነሣም።

የብርሃን ጠብታ 18
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥቅምት 21 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ