መግቢያ » ከመጻሕፍት » ወዳጄ ሆይ » የማታ ጀምበር

የትምህርቱ ርዕስ | የማታ ጀምበር

 

አቤቱ በዋጋ የገዛኸው የሰው ልጅ በነጻ ሲሞት ዝም አትበል ! መርጦ ሳይወለድ ተመርጦ ለተገደለው ጌታ ሆይ እዘን !

ወዳጄ ሆይ !

ደስታ የሰላም ውጤት ነው ፤ ሰላምም የሚገኘው በእውነተኛ ፍቅር ውስጥ ነው ። ካዘኑት ጋር ካላዘንህ የስብራትህ ቀን ሲመጣ አጽናኝ አታገኝም ። ጭፍን ፍቅርህ ጭፍን ፍርድ እንድትሰጥ ያደርግሃል ። እኔን ካልነካኝ ብለህ ስትቀልድ ሩቅ ያየኸው ቅርብ ይሆናል ። ሰው ሲወድቅ ሰው የሆነ ያዝናል ። በገንዘብ ቁማር የሚጫወትን ስታወግዝ ነፍስ አሲይዞ የሚቆምርን ዝም ካልህ እውነት ትፈርድብሃለች ። 

ወዳጄ ሆይ !

ሙሴ ቀድሞ ያስከተለ መሪ ነው ። በረሃውን አርባ ዓመት ኖሮበት አርባ ዓመት ሕዝቡን በምድረ በዳ መራ ። መሪ ካልቀደመ አለቃ ይሆናል ። የማያስከትል ይነዳል ። ለበጎ ነገር ጎንህን ሳታይ ስትነሣ እግዚአብሔር ይባርክሃል ። መከራን ቀድሞ የሚያሳይህ በዚያ መንገድ እየመጡ ያሉትን እንድትረዳቸው ነው ። ስለምትሄድበት መንገድ የሚነግሩህ አብረውህ የሚጓዙ ሳይሆኑ የሚመለሱት ናቸው ። አዲስ መከራ ያስለፈልፋል ፣ ክለሳው ግን ያስገርማል ፤ ሥለሳው ግን ያስቃል ። አንዳንድ የድሀ ልጅና አንዳንድ የሀብታም ልጅ አይራሩም ። የድሀ ልጅ የማይራራው የሰማውን መከራ ከራሱ የችግር ዘመን ጋር እያነጻጸረ “ይሄማ ቀላል ነው” በማለት ነው ። የሀብታም ልጅ የማይራራው ችግሩ ምን እንደሆነ ስላልገባው ነው ። አንዳንድ ድሀ ይራራል ፣ የእርሱ የጉዳት ዘመኑ ትዝ ይለዋልና ። አንዳንድ የሀብታም ልጅ ይራራል ፣ እርሱ ጋ ትርፍ የሆነው እዚያ ጋ ዋና ሆኗልና ። 

ወዳጄ ሆይ !

አስታርቃለሁ ብለህ ስትሸመግል እንዳትሸነግል ተጠንቀቅ ። እውነት በሌለበት ህርቅ የለም ። ህርቅ የፍቅር ፍርድ ይፈልጋልና ። እግዚአብሔር ችሎን ነበር ፣ እኛ ግን መቻቻል አቃተን ። እግዚአብሔር ከቀሰፈን ራሳችንን የቀሰፍነው ይበዛል ። እግዚአብሔር የሰጠንን እኛ ካልያዝነው እርሱ አይጠብቀውም ። መዛል የጨበጥከውን ያስጥላል ፣ መሰልቸትም ሞተህ እንድትኖር ያደርግሃል ። ዓለም ሰፊ መቃብር የምትሆነው ተስፋ ለቆረጡት ነው ። ተስፋ መቍረጥ ተንቀሳቃሽ ሬሳ ያደርጋል ። ተስፋ የሚደረጉ ነገሮች ስላሉ ሳይሆን እግዚአብሔርን አይቶ ተስፋ ማድረግ እርሱ ትክክለኛው ተስፋ ነው ። ተስፋ አይቶ መናገር ሳይሆን አምኖ መደሰት ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

ግትር ሰው መሆን እውነተኛነት ሳይሆን እኔ ብቻ አውቃለሁ ባይነት ነው ። የሰማኸውን አትካድ ፣ አንድ ቀን ይህ ጆሮህ መስማት ያቆማልና ። ያየኸውን አትካድ ፣ አንድ ቀን ይህ ዓይን ይፈስሳልና ። አባት ሆነህ ሩኅሩኅ ካልሆንህ ልጅ አለኝ ብለህ አትናገር ። የምታስተምረው ሳይኖርህ አስተማሪ ፣ የምትሰጠው ሳይኖርህ አባት አትሁን ። በጉባዔ ቅዱስ የተባለ መልሶ ርኩስ ይባላል ። በሰማይ ቅዱስ የተባለ ግን እውነተኛ ቅዱስ ሆኖ ይኖራል ። የድጋፍ ድምፅ ቢኖርህም መሞትህ አይቀርም ። የታመመ እንጂ የሞተ አይጠየቅም  ። 

ወዳጄ ሆይ !

ተቀምጠህ ካየኸው ሁሉም ሰው ትልቅ ፣ አንተ ግን ትንሽ የሆንህ ይመስልሃል ። ስትቆም አንተም ትልቅ መሆንህን ትረዳለህ ። ስትራመድም ሰዎች ከደረሱበት ትደርሳለህ ። የተስፋ ቃል ያሻግራልና በክፉ ቀን ለራስህ ንገረው ፣ ቀን ለከፋባቸውም ንገራቸው ። ማጽናናት መጽናናት ነው ። የሰማይ ደጅ ማለት የድሆች ሆድ ነው ። የልዑሎች ልዑል የሆነውን አምላክ ይዘህ አትፍራ ። እግዚአብሔርን አምነው የሰጡህን አደራ መካድ በምድር በሰማይ ስደተኛ መሆን ነው ። እጅግ የተጠየፉ ሰባት ሰዎች አሉ  ። እነርሱም፡- ትዳራቸውን ለገንዘብ የሚለውጡ ፣ ጉቦ በልተው ፍርድ የሚያጣምሙ ፣ ወልደው የሚረሱ ፣ በሐሰት የሚመሰክሩ ፣ በሰው ደም የሚቀልዱ ፣ በጽድቅ ጀምረው በኃጢአት የሚፈጽሙ ፣ ተቀብለው የማያመሰግኑ ናቸው ። 

ወዳጄ ሆይ !

ጥልቁን ያላየ ምጥቀት ላይ ቢወጣ እንደ ቀላል ይቆጥረዋል ። የሁሉም ነገር መነሻም ያ እየመሰለው አያመሰግንም ። መጨረስ ያልቻሉትን አትውቀስ ፣ አንተ ገና አልጀመርህምና ። የሸመገሉትን አትሳደብ ፣ ትደርስበታለህና ። ልጅነትህን አትውቀስ አትመለስበትምና ። በጥቁር ፀጉርህ ትዝታ አትኑር ፣ ሽበቱን አታጌጥበትምና ። በሚያዝኑት አትሳለቅ ፣ አንተ ትንሹ ቢደርስብህ ትወድቃለህና ። በሚሰደዱት አትፍረድ ፣ አንዳንዴ አገር ከሲኦል ይከፋልና ። በባዕድ አትቀየም ፣ ወገንህ እየገደለህ ነውና ። ወጣቶችን ኰናኝ አትሁን የሰጠሃቸው የለምና ። 

ወዳጄ ሆይ !

ሕግን እንዲያስከብር የተቀመጠ ድርሻው ሕግ ማስከበር እንጂ መታገሥ አይደለም ። የሚታገሥ የተበደለ ሲሆን የሚፈርድ መንግሥት ነው ። የሙሴ መሪነትን የአሮን ክህነት ይረዳዋል ። የአሮን ክህነት በሙሴ መሪነት ቅርጽ ይይዛል ። ሙሴ የሌላቸው አሮኖች ወርቅ አምላኪዎች ናቸው ፤ አሮን የሌላቸው ሙሴዎች የተስፋይቱን ምድር ተመኝተው የማያዩአት ናቸው ። ትላንት በሠራኸው መልካም ሥራ ብቻ ከኮራህ ወደፊት መራመድህ ይቀራል ። ሙሴ ስለፈርዖን አንድም ቀን አላወራም ። ፈርዖን ሞቶ እግዚአብሔር ሕያው አምላክ ሆኖለታልና ። 

ወዳጄ ሆይ !

እያንዳንዱ ቀንን የሚኖሩ በሽተኛና ንጉሥ ናቸው ። እነዚህ በዓመት ሳይሆን በየዕለቱ ልደታቸውን ያከብራሉ ። ቀኑ ዋጋ ያለው ጦርነት ላለበት ሰው ነው ። ዓመፅ እንዳይነሣ አድርገህ ሥራ እንጂ ዓመፅን ለማብረድ አትሥራ ። ጦርነትን የምታስቀረው ሁልጊዜ ጦርነት እንዳለ ሆነህ ስትኖር ነው ። 

አቤቱ በዋጋ የገዛኸው የሰው ልጅ በነጻ ሲሞት ዝም አትበል ! መርጦ ሳይወለድ ተመርጦ ለተገደለው ጌታ ሆይ እዘን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም