መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የማትረሳ

የትምህርቱ ርዕስ | የማትረሳ

 ተስፋ ያደረግሁት ከእኔ ቢርቅም አንተ ግን በአማኑኤል ስምህ ከእኔ ጋር ሁን ። ያከበርኩት ቢያዋርደኝ አንተ ግን በወርቀ ደምህ መገዛቴን ንገረኝ ። አለኝታ ያልኩት ደጁን ቢዘጋብኝም አንተ ግን የጠፋው ልጅ አባት ሁነኝ ። አስታዋሼ ያልኩት ፍጹም ቢረሳኝም አንተ ግን የማትረሳ እምዬ ነህ ። የእኔ ያልኩት እንደ በረዶ ቢሟሟም አንተ ግን የማታልቅ ሀብቴ ነህ ። ይጠግነኛል ያልኩት ቢሰብረኝም አንተ ግን ሐኪሜ ነህ ። ያድነኛል ያልኩት ቍስሌን ቢያድሰውም አንተ ግን አዲስ ራእይ የምትሰጠኝ ነህ ። ይመጣል ያልኩት ቢቀርም አንተ ግን ቀጥረህ የማትቀር ነህ ። ያልታየውን አየሁልህ የሚል  ሸንጋይ ቢገጥመኝም አንተ ግን ዓይኔ ነህ ። ላይደርስልኝ ቆይ መጣሁ እያለ ቢያዘናጋኝ አንተ ግን ደመናን ጠቅሰህ ፣ ባሕር ተራምደህ ትመጣለህ ። ለካባ ያሰብኩት ቀሚሴን ቢወስደውም አንተ ግን የጽድቅ ሸማዬ ነህ ። ይሰውረኛል ያልኩት ቢያጋልጠኝ አንተ ግን የመማጸኛ ከተማዬ ነህ ። ይደርስልኛል ያልኩት እልም ቢልም አንተ ግን በረከቴ ነህ ። ለትርፍ ክፍያ ስጠብቅ ደመወዜን ባጣም አንተ ግን መኖሪያዬ ነህ ። በግራዬ ሰዎች ቢከዱኝ አንተ ግን በቀኜ ወዳጆች ታመጣልኛለህ ። ቀኑን ሳልገምት ቢደርስብኝም አንተ ግን ቀድመህ አዘጋጅተህልኛል ። ጉልበቴ የከዳኝ ቀን አንተ ግን ተነጥፈህልኛል ። ልነሣ ስል አልጋ ላይ ስቀር አንተ ግን አስታመኸኛል ። የተንተራስኩት ክንድ ሲዝል አንተ ግን ችለኸኛል ።
ይወደኛል ያልሁት ቢጠላኝም አንተ ግን ውዴ ሆነህልኛል ። ያድነኛል ያልኩት ገዳይ ቢሆንም አንተ ግን መርዙን አርክሰህልኛል ። መኖሬን ስጠራጠር አንተ ግን ብዙ ቀን ጨምረህልኛል ። ይሾመኛል ያልኩት ቢያዋርደኝም አንተ ክርስቶስ አክብረኸኛል ። ናልኝ ያልኩት ቢቀርም አንተ ግን ሳትለየኝ ፈጥነህ ደርሰህልኛል ። የከበቡኝ ሲበተኑ አንተ ግን መላእክትን አዝዘህልኛል ። ይለምኑልኛል ያልኋቸው ቢዘርፉኝ አንተ ግን ቅዱሳንን ሰጥተኸኛል ። ያዝንልኛል ብዬ ቍስሌን ያሳየሁት ጥዝጣዜ ቢጨምርብኝ አንተ ግን ዳሰኸኛል ። አለቀ ያልኩት ገና እንጭጭ ቢሆንም አንተ ግን የዳርቻዬ አዛዥ ነህ ።
ተስፋዬ ሆይ በእኔ አቆጣጠር ዘገየህ ። ወይ ቶሎ ና  ወይ ልቤን ትዕግሥት ሙላ ። ውስጤን ሳስበው ገና በዓለም ለመኖር እከጅላለሁ ። በአፌ ማራናታ ፣ በልቤ ቆይ ጌታ እላለሁ ። ገልብጠህ ስማኝ ፣ እንደ ልቤ ሳይሆን እንደ አፌ አድርግልኝ ። እንደ እኔ ሳይሆን እንደ አንተ ይቅር በለኝ ። አለው ያሉኝን ደግ ነገር እባክህ ጨምረህ ስጠኝ ። አላመኑኝም ብዬ በሰው ከማዝን አምንሃለሁ ብዬ ባንተ መደሰት አብዛልኝ ።
ወዳጅ ሆይ በቃልህ ያልተማርን በሬሳ አንማርም ። እኛን ለማስተማር ዘመኑን ብታስጨንቅም ፣ ስትለቀን ያው ነን ። እባክህ ዝም ብለህ ወዳንተ መልሰን ። አሳዳጁን ጳውሎስን ገንዘብ ያደረግህ እኛንም ለክብርህ ለመኖር አብቃን ። እናቱን እንደ ናፈቀ ልጅ መምጫ መምጫህን እያየን እንኑር ። ቀኑ ሳያልቅብኝ ምስጋናዬን ላቅርብልህ ።
ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ክብርና ምስጋና ይገባል ። ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና 23
ሚያዝያ 3 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም