የትምህርቱ ርዕስ | የማይሰክር

 “እንግዲህ ኤጲስ ቆጶስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል ፤ የማይሰክር” 1ጢሞ. 3፡3
የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ ጥር 18 ቀን 2012 ዓ.ም.
www.ashenafimekonen.blogspot.com
ብዙ ሕይወት ፣ ብዙ ትዳር ፣ ብዙ ቤተሰብ ፣ ብዙ ፍቅር ፈርሷል ። የፈረሰውም በመጠጥ ነው ። በኖኅ ዘመን መላው ዓለም በውኃ እንደ ጠፋ ዛሬም መላው ዓለም በመጠጥ እየጠፋ ነው ። የሰው ልጆች ዕለቱን የሚውሉት በትክክል በማሰብ ሳይሆን በመደንዘዝ ነው ። ጤነኛ ሁኖ ወደ መጠጥ ቤት የገባው ሰው ሲወጣ እያበደ ነው ። በሰላምታ ገብቶ እየተሳደበ ይወጣል ። መጠጥ ቤት ገብቶ ራሴን እገዛለሁ ማለት ዘበት ነው ። ነገሮችን መጋፈጥ የማይፈልጉ ፣ አቋራጭ ደስታ የሚሹ እነርሱ በመጠጥ ይደነዝዛሉ ። በተለያዩ ቢሮዎች ጉዳይ ያላቸው እንዲያደፋፍራቸው ብለው ይጠጣሉ ። ሰዎች ወደ መጠጥ እንጂ ወደ ስካር በራሳቸው አይገቡም ። ወደ ስካር የሚወስዳቸው መጠጡ ነው ። ብርጭቆ መጀመሪያ እንጨብጠዋለን ፤ ቀጥሎ ይጨብጠናል ።
ሰዎች ወደ መጠጥ የሚገቡት በተለያየ ምክንያት ነው ። ስካር አላማጅ አለው ። አልጠጣም የሚለውን ሰው መጠጥ ለማስጀመር ብዙ በጀት የሚበጅቱ ሰዎች አሉ ። አብላኝ የሚላቸውን ያልፋሉ ፣ አጠጣኝ ለሚላቸው ግን ቸር ይሆናሉ ። ለጽድቅ የታሰረ እጅ ሰውን ለማስከር ግን ይፈታል ። ጠጪዎች ሌላውን ለማስጀመር የሚፈልጉት አንደኛ አጃቢ ፍለጋ ነው ። ሁለተኛ እነርሱ የቸገራቸው ቀን ያ ተማሪያቸው ከየትም ፈልጎ እንዲያጠጣቸው ነው ። ሦስተኛ ያንን ሰው እንደ ፈለጋቸው ለማዘዝ ነው ። ሱስ ረጅም ገመድ ነው ። እየሰደቡት እንኳ ሱሰኛ ከአስተማሪዎቹ ቤት አይርቅም ። ሱስ ሐሰተኛ ደግነት ያለው ሲሆን የገዛ ልጆቹንና ሚስቱን እያስራበ ሌሎችን ይጋብዛል ። በደጅ ጥሩ ሰው ፣ ተጫዋች ያደርገውና ወደ ቤቱ ሲገባ በጥባጭና ግልፍተኛ ያደርገዋል ።

መጠጥ እብደት ነው ። እብደትነቱ ልዩ የሆነው አንዱን ቀን ሁለት በማድረግ ጠዋት ጨዋ የነበረውን ሰው ከሰዓት እብድ ያደርገዋል ። አሁንም እብደትነቱን ልዩ የሚያደርገው በገንዘብ የሚገዛ መሆኑ ነው ። የመጠጥ መግቢያውና ማጠቃለያው ምንድነው ካልን መግቢያ ዘፈን ሲሆን ማጠቃለያው ዝሙት ነው ። ውጤቱ ጸጸትና በሽታ ነው ። ውኃ ሲወስድ እያሳሳቀ ነው ይባላል ። ውኃ የሚወስደው ሰው ሳቅ ያፍነዋል ። ሳቁም አቅም እያሳጣው ወደ ሞት ወደ መስጠም ይሄዳል ። መጠጥም ጨዋታ ፣ ደስታ ፣ ነጻነት ያለበት ይመስላል ። ሰዎች እየሳቁ የሚሞቱበት ስፍራ ቢኖር መጠጥ ቤት ነው ። የሚደንቀው መንግሥት በምሁርነትና በተቆርቋሪነት የሚገሥጸውን እስር ቤት ይከታል ። ሰካራም ሲሳደብ ግን ጥበቃ ይደረግለታል ። በአገራችን እውነት ለመናገር እብድ ፣ ዘመናይና ሰካራም መሆን ያስፈልጋል ። የስካር ዓለም ጨካኝ ነገሥታት እንኳ የናቁት በመሆኑ ሰዎች እየጠጡ ብሶታቸውን ይናገሩበታል ። መጠጥ አዋራጅ ነገር ነው ። በመጠጥ ስፍራ የተገኙ ባለጠጎች ፣ ባለሥልጣናትና ሽማግሌዎች እንደ ሕፃን ሊታዩ ፣ ሊናቁና ሊሰደቡ ይችላሉ ። ሰው ራሱን ጨፍልቆ መለኪያ ውስጥ ሲከትት መጠኑ አንድ ብርጭቆ ያህል ይሆናል ። ብዙ ተንኮለኛና ጠላት ያለባቸው ሰዎች በፍጹም መጠጥ  አይቀምሱም ። ሰው ተመርዞ የሚገደለው ብዙ ጊዜ በመጠጥ ነው ። ክፉዎች እንኳ መጠጥ የሚያራቁት እንደሆነ አውቀው ይጠነቀቃሉ ። በየአገራቱ ያሉ ዲፕሎማቶች የዚያን አገር ምሥጢር የሚያገኙት የዚያን አገር ባለሥልጣናት በማጠጣትና አብሮ በማምሸት ነው ። በመጠጥ ውስጥ ያሉ የደኅንነት ሠራተኞች የአገራቸውን ምሥጢር አሳልፈው ይሰጣሉ ። መጠጥ አገርን ጭምር ለጉዳት ይሰጣል ።
ሄሮድስ በዘፈን ተማረከ ፣ በመጠጥ ልብ ሁኖ መጥምቁ ዮሐንስ አንገቱ እንዲቆረጥ አዘዘ ። መጠጥ የቅዱሳንን አንገት የሚያስቆርጥ ነው ። መጽሐፍ ቅዱስ ጨርሶ አትጠጡ አይልም ፤ ጠጡም አይልም ። በሰው ልጆች ታሪክ ፣ በመንፈሳዊ ሕይወት ጉዞ እንደ ታየው ግን አለመጠጣት ክብር አለው ። ባለመጠጣት የምናጣው ነገር የለም ፤ በመጠጣት ግን ብዙ ነገሮችን እናጣለን ። መጠጥ ሰው ከቤቱ ውጭ እንዲያመሽና እንዲያድር ያደርገዋል ። ብዙ ሚስቶች ቤት ጠባቂ ዘበኛ ሁነው የቀሩት በመጠጥ ምክንያት ነው ። መጠጥ ለልጆች ክፉ አርአያ ነው ። መጠጥ ኢኮኖሚን የሚያናጋ ነው ። መጠጥ የሐሰተኛ ደስታ መገኛ ነው ። መጠጥ ማታ ንጉሥ የሚያደርግ ጠዋት የሚያኮስስ ነው  ። መጠጥ ጤናን የሚጎዳ ፣ ያለ ጊዜው የሚገድል ነው ። መጠጥ ክብርን ዝቅ የሚያደርግ ፣ ከምግባረ ብልሹዎች ጋር የሚያውል ነው ። መጠጥ ንቀትና አደራ በላነትን የሚያመጣ ነው ። ሰካራም ጋ የሚቀመጥ የዕድር ገንዘብ የለም ። ሰካራም ከትዳሩም ፣ በማኅበራዊ ሕይወቱም በላይ ስካሩ ይበልጥበታል ። ሰካራም ተንቀሳቃሽ ሬሳ ነው ። ከቆሙት በታች ፣ ከሞቱት በላይ ነው ። እብድ ቢጨምት እስከ እኩለ ቀን ነው ይባላል ። ሰካራም ጨዋ የሚሆነው እስከ እኩለ ቀን ነው ። እርሱም በማታ ድካሙ ስለሚተኛ ነው ። ሲነሣ መነጫነጭና መሳደብ ይጀምራል ። እብድና ብርድ በግድ ያስቃል ይባላል ። ሰካራምም በግድ የሚያስቅ ነው ። አሁን ዘፍኖ አሁን ያለቅሳል ።
ሰዎች ወደ መጠጥ የሚገቡት ጓደኛ ፍለጋም ነው ። በመጠጥ ቤት ሐሰተኛ ኅብረት አለ ። ዛሬ አንዱ ከከፈለ ነገ ደግሞ ሌላኛው ይከፍላል ። ሰካራም  ቤት አይሠራም ፣ ከሠራም ቶሎ አይገባም ፣ ከገባም ቶሎ አይተኛም ይባላል ። መጠጥ ከገዛ ቤት ስደተኛ ያደርጋል ። ጠጪ ማለዳው የተበላሸበት ነው ።ማቀዝቀዣ ሚሪንዳ ፣ ሽሮ ፍትፍት ፈላጊ ነው ። ጠጪ በገዛ ሚስቱ የተናቀ ነው ። ያለ ፍላጎቷ እርሱ በፈሳሽ የወሰደውን መጠጥ እርስዋ ደግሞ በትንፋሽ ትወስዳለች ። ብዙ ጠጪዎችና ሱሰኞች ሁለት ትዳር መሥርተው የሚኖሩ ናቸው ። የመጀመሪያው ቤታቸው ለክብራቸውና ለልጆች ማሳደጊያ ሲጠቀሙበት ሁለተኛውን ደግሞ ለዘላንነት ይጠቀሙበታል ። መጠጥና ሱስ የስንፍና መገኛ ነው ። መጠጥ የማሰብን ኃይል እየቀነሰ ይመጣል ። ጠጪዎች ትዕግሥት ስለሚያጥራቸው በሽሽት የሚኖሩ ናቸው ፤ ከጤነኛ ሰው ጋር ለመገናኘትም ነጻነት አይሰማቸውም ። በጸጸት ስለሚሰቃዩም ጠዋት አዝነው ማታ ይመለሳሉ ። ውሻ ወደ ትፋቱ ይመለሳል የሚባለውም ይፈጸምባቸዋል ። ሰዎች በብርቱ ኀዘን ምክንያትም ወደ መጠጥ ይገባሉ ። ሌሎችም በየመጠጥ ቤቱ ያለው ጭፈራ ደስታ እየመሰላቸው ይገባሉ ። ገንዘብ ለማግኘት የሚሹም ባለሥልጣኖቹ ያሉት መጠጥ ቤት ነውና የጨለማ ቢሮዎችን ሲያስሱ ያድራሉ ። ጨረታው ፣ ጉዳዩ ፣ ፍርዱ የሚያልቀው መጠጥ ቤት ነው ። አገር ጣር የያዛት በመጠጥ ነው ።
በመጠጥ መንፈስ ሁነው አንገት የቀሉ ፣ አሮጊት የደፈሩ ብዙዎች ናቸው ። መጠጥ ሰውን ከእንስሳ ያነሰ ያደርገዋል ። ስንቱን እናወራለን ። የስካር መዘዙ ብዙ ነው ። በጸጸት የሚሰቃዩ ሰዎችም ስካርን መደበቂያ ያደርጉታል ። ነገር ግን ጨለማ በጨለማ አይሸነፍም ፤ ጨለማ በትንሽ ብርሃን ግን ይሸነፋል ። ለጸጸት መድኃኒቱ ንስሐ መግባትና በክርስቶስ ደም መታጠብ ነው።
ኤጲስ ቆጶስ የማይሰክር ሊሆን ይገባዋል ። ሾፌር መጠጣት የለበትም ። የሕይወት ኃላፊነት በእጁ ነውና ። የነፍስ አደራ ያለበት ኤጲስ ቆጶስም ሊሰክር አይገባውም ። ይልቁንም በምንኩስና ያሉ አባቶች ፈጽመው ሊጠጡ አይገባቸውም ። መነኩሴ ምናኔው ከመጠጥ ጭምር ነው ። ብዙ ዘመን በመጠጥ ምክንያት ስንሰደብ ኑረናል ። ካህናት በመጠጥ ምክንያት የክህነትን ክብር አዋርደዋል ። ስካርም የኦርቶዶክሳዊነት መለያ እስኪመስለንም መጠጥ ያልጠጣ ሌላ ነው ብለናል ። ይህ አለማወቅ ነው ፤ በእውቀት እንጂ በመጠጥ መወዳደር ክብር አይደለም ፤ የትም አያደርስም ።
ኤጲስ ቆጶስ በመንፈሰ እግዚአብሔር የተመረጠ ነውና ሊሰክር ቀርቶ ሊጠጣ አይገባውም ። ቃሉ፡- መንፈስ ይሙላባችሁ እንጂ በወይን ጠጅ አትስከሩ ይህ ማባከን ነውና” ይላል ። ኤፌ. 4፡18 ። መንፈሰ እግዚአብሔር ያደረበት ሰው በመጠጥ ሊነዳ አይገባውም ። በመንፈስ ቅዱስ ቁጥጥር ሥር ያለም በመጠጥ ቁጥጥር ሥር መሆን አይገባውም ። ይህ ማባከን ነውና ። ስካር ኅሊናን ፣ እውቀትን ፣ ምሥጢርን ፣ ጤናን ፣ ገንዘብን ፣ ወዳጅነትን ፣ ትዕግሥትን … ማባከኛ ነው ። ብዙ ኃላፊነት ያለባቸው በትንሽ መጠጥ አቅላቸውን ይስታሉና መጠንቀቅ ያስፈልጋቸዋል ።
የእስራኤል አምላክ ሆይ እርዳን ።
1ጢሞቴዎስ 40
ጥር 18 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም