የትምህርቱ ርዕስ | የማይጨቃጨቅ

 “እንግዲህ ኤጲስ ቆጶስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል፤… የማይጨቃጨቅ ነገር ግን ገር የሆነ” 1ጢሞ. 3፡2-3
ሙግት የሚወድና ፍርድ ቤትን እንደ ቤተ ክርስቲያን ካልተሳለመ ደስ የማይለው አንድ ሰው ዳኛው “አግብተሃል ?” ብለው ሲጠይቁት “አዎ ትዳር አለኝ ፣ ያገባሁት ሴት ልጅ ነው” ብሎ መለሰ ። ዳኛው በመገረምና በቊጣ “ታዲያ ልታገባ የምትችለው ሴት መሆኑ የታወቀ ነው ፣ ለምን እንዲህ ያለ መልስ ትሰጣለህ ?” ቢሉት “አይ የእኔ እኅት ያገባችው ወንድ ነው” አለ ይባላል ። ነጋ ለነገር ፣ ጠባ ለጭቅጭቅ የሚሰለፉ ፣ ካልተጨቃጨቁ የኖሩ የማይመስላቸው ፣ ዝም ያሉ ቀን የሞቱ የሚመስላቸው ብዙ ሰዎች አሉ ። ሴትየዋ ሰፈሩን በነገር ቀጥ አድርገው ያቆሙት ፣ ዕረፍት አጥተው ዕረፍት ያሳጡ ነበሩ ። የአዲስ አበባ መንደሮች እየፈረሱ ወደ አዲሱ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ከተወሰዱ መካከል እኚህ ሴት አንዷ ናቸው ። እዚያ ፎቅ ላይ በመስኮት የሚያዩት በዚህ በኩል መንገደኛ ሲያልፍ በግቢው በኩል ዘበኛው ሲንጎራደድ ብቻ ነው ። ጎረቤታቸው ማን መሆኑን አያውቁም ። ወደ ቀድሞ ሰፈራቸው በንዴት መጡ ። ከሩቅ እየተሳደቡ ሲመጡ “ደሞ መጣሽ” ቢሏቸው “ይቅር በሉኝ እዚያ ፎቅ ላይ ተሰቅዬ እንኳን የምሰድበው የሚሰድበኝ አጣሁ” አሉ ይባላል ። የሚያጣላ ነገር ቢያጡ በሰላምታ የሚጣሉ ፣ “እንደምን አደራችሁ ?” ሲባሉ “ባድር ባላድር ምን አገባችሁ ?” የሚሉ አያሌ ናቸው ።

የሚጨቃጨቁ ሰዎች ብዙ ጊዜ ለቤቱ አንድ ልጅ ይሆኑና የሁሉ ዓይን እነርሱ ላይ ያርፋል ። የሚፈልጉትን ነገር ሳይጠይቁ ያገኙታል ። ቆንጆና ጎበዝ ተብለው ይወደሳሉ ። አትንኩት ተብለው በሁለት ፊት ያድጋሉ ። በዚህ ጊዜ ሁሉም ነገር የማይጥማቸው ተሳዳቢና ደፋር እየሆኑ ይመጣሉ ። ሁለተኛ ልጅ ቢወለድም ራሳቸውን የሚያስቡት እንደ ብቸኛ ነው ። ሁለተኛውን ልጅ ወንድማቸው መሆኑን ከመቀበል ልጃቸው አድርገው መቀበል ይቀላቸዋል ። ተጨቃጫቂነት ያለ እኔ አይሆንላቸውም ብሎ ከማሰብ የሚመጣ ነው ። የእኔን ድርሻ ሌሎች ይሥሩልኝ ብሎ ሸክም የመሆን ዝንባሌ ነው ። ተጨቃጫቂዎች ስድባቸውን እንደ ትልቅ መሣሪያ ያዩታል ። እንግዳ ሲመጣ እየገነኑ ይመጣሉ ። ብቻቸውን መኖርና መብላት ይፈልጋሉ ። ዕድሜአቸው ቢገፋም ገና ሕፃን ነኝ ብለው ያስባሉ ።
ተጨቃጫቂነት በተለያየ መንገድ ይመጣል ። ማዘዝ የሚወዱ መሥራት ግን የማይችሉ ሰዎች ተጨቃጫቂ ናቸው ። ለመሥራት ሙያና የልብ ቆራጥነት የላቸውም ፣ የማዘዝ ግን ብቃት አላቸው ። የሚጨቃጨቁት ስንፍናቸውንና ሙያ ቢስነታቸውን ሰው እንዳያውቅባቸው ነው ። ጭቅጭቅ ሽፋን መስጫ ነው ። በሱስ የተያዙ ፣ በትዳራቸው ላይ የሚማግጡ ሰዎች ጭቅጭቅ ሊያበዙ ይችላሉ ። ሁልጊዜ በስህተታቸው ፊት ስለሚኖሩ ታወቀብኝ የሚል ስጋት ውስጥ ይገባሉ ። በዚህ ምክንያት መጨቃጨቅ ይወዳሉ ። የበታችነት ስሜት የሚሰማቸው ሰዎችም መጨቃጨቅን እንደ አትኩሮት ማግኛ ይጠቀሙበታል ። የተረሱ ስለሚመስላቸው አለሁ የሚሉት በመጨቃጨቅ ነው ። የማይረኩ ሰዎችም በጭቅጭቅ የታወቁ ናቸው ። እነርሱ ብቻ ጎበዞችና አሳቢዎች እንደሆኑ ያስባሉ ። ሌላውን ሰው ሰነፍና ሞራል የሌለው እድርገው ይስላሉ ። ጭቅጭቃቸው ሌሎችን በእነርሱ አለመርካት ውስጥ ለመክተትና ጓደኛ ለማግኘት ነው ። አለመርካት ትልቅ የጭቅጭቅ ርእስ ነው ።
ሙያ ከእኔ ወዲያ ለሐሳር ብለው የሚያስቡ ሰዎችም ተጨቃጫቂዎች ናቸው ። ሌሎች የሠሩት ነገር አይጥማቸውም ፣ ሲቀመጡ ደግሞ ለምን ? ይላሉ ። በጣም ጎበዝ መሆንም ተጨቃጫቂ ያደርጋል ። አሳባቸው በዝቶ አቅማቸው ያነሰባቸው ሰዎችም በጭቅጭቅ የታወቁ ናቸው ። ተጨቃጫቂዎች አንድን ነገር ደጋግመው የሚናገሩ ናቸው ። እነዚህ ሰዎች እግዚአብሔር ጸሎትን የሚሰማው በመጨቃጨቅ ይመስላቸዋል ። ሳይታክቱ በትዕግሥት መጸለይና መጨቃጨቅ ልዩነት አለው ። የሚፈልጉትን የማያውቁ ሰዎችም ይጨቃጨቃሉ ። የብዙ ሰው ችግር የሚፈልገውን ነገር በትክክል አለማወቁ ነው ። ትምህርት እያለ ያስብ ነበር ተማረ ፤ ነገር ግን አሁንም እርካታን አላገኘም ። ትዳር ይሻ ነበረ ፣ አገኘ ፤ አሁንም ደስተኛ አይደለም ። ይህ ሰው የሚያስደስቱ ነገሮችን እንጂ ራሱን ደስታን እየፈለገ አይደለም ። የሚያስደስቱ ነገሮችን መፈለግ ደስታን አያስገኝም ። ደስታ ራሱ ግን የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ ነው ። ካላስደነበሩአቸው የአገሬ ሰዎች አይሠሩም ብለው የሚያምኑም ሰዎች ይጨቃጨቃሉ ። የአለቅነት ስሜት የሚሰማቸው ሰዎች መሪ እስኪሆኑ ድረስ መጨቃጨቅን አይተዉም ።
ሆዳቸውን የሚወዱ ሰዎች ጨቅጫቃ ናቸው ። የቤት ወጪ በቅጡ የማያወጡ ነገር ግን ወጥን በማጣጣም የታወቁ ናቸው ። ስጡ ሲባሉ አይሰጡም ፣ ትችት ግን ጎበዝ ናቸው ። ሆድን መውደድ አንድ ቀን ገደል ይከታል ። በትዳራቸው ላይ ሌላ ትዳር መሳይ የሚይዙ ሰዎች የሚታለሉት በሆዳቸውና በሱስ ነው ። እንደ ዔሣው ሆዳቸውን የሚያመልኩ ፣ ወጥ አሳዳጆች ጨቅጫቃ ናቸው ።በርግጥ ሁሉም ሚስት ባለሙያ ላይሆን ይችላል ። ይህ ሰው ራሱ መሥራት ቢለምድ ወይም ይሥሩ የሚላቸውን ሰዎች ሙያ ትምህርት ቤት ልኮ ቢያስተምር በቀጣይ ዘመን ከመጨቃጨቅ ይድናል ።
አዲስ ፍቅር የያዛቸው ሰዎች ጨቅጫቃ ናቸው ። ሰው በሃምሳ ዓመቱ ከተቃራኒ ጾታ ጋር ፍቅር ቢጀምር የሃምሳ ዓመት ልምዱ ለዚህኛው ሕይወት አይረዳውም ። መልሶ እንደ ወጣት ይሆናል ። ቅናት በውስጣቸው ያደረ ሰዎች እገሌ እግርሽን አየ እያሉ ይጨቃጨቃሉ ። ሚስቴን ተመኝተሃታል ብለውም ከሰው ይጣላሉ ። ልምድ ማጣትና ቅናት የጭቅጭቅ መነሻ ናቸው ።
የነሐሴ ዝናብ እኝኝ ብላ ይባላል ። ተጨቃጫቂ ሰውም እኝኝ ብላ ነው ። እኝኝ ብላ ከጠዋት እስከ ማታ እስከ ሦስት ቀንም የሚቀጥል የማያስወጣ የማያስገባ ዝናብ ነው ። ጨቅጫቃ ሰው ይሰለቻል ። ሁሉም ሰው አመሉ ነው እያለ የሚናገረውን ነገር ያፈስሰዋል ። ወዳጅነቱና ትዳሩም ይፈርሳል ። እርሱም በራሱ ሰላም የሌለው ይሆናል ። ምን መሆን እንዳለበት የማያውቅ ፣ ሰዎች እንዴት እንዲሆኑ እንደሚፈልግ የማይገነዘብ ሰው ነው ። ጨቅጫቃ ሰው ነዝናዛ ሰውም ይባላል ። የሚነዘንዝ የሌሊትና የክረምት ቊስል ነው ። ጨቅጫቃ ሰው ጤና አጥቶ ጤና የሚያሳጣ  ነው ። አንዳንዶቹ ነዝናዛዎች ሱሰኞች ስለሆኑ ጤና አያጡም ። ሲነዛነዙ ደስ ይላቸዋል ።
ጨቅጫቃ ሰዎችን መሾም ሥራን መበደል ነው ። ጨቅጫቃ ሰዎችን ልናተርፋቸው የምንችለው የሚጠሉትን ነገር በመለየት ፣ ጠባያቸው መጥፎ መሆኑን በመንገር ፣ ይልቁንም ትዕግሥትን እንዲሰጣቸው በመጸለይ ነው ። ምንም ሳይሆኑ ብዙ እንደሆኑ እየተሰማቸው ባልተጨበጠ ነገር የተጨበጠ ሁከት ውስጥ የሚገቡ አያሌ ናቸው ። ልናዝንላቸው ይገባል ። እኛም በመሰልቸት እንዳንርቃቸው ትዕግሥትን መለማመድ አለብን ።
ኤጲስ ቆጶስ የማይጨቃጨቅ ሊሆን ይገባዋል ። ነገር አፍቃሪ ሁኖ ፍርድ ቤት ሥራው እንዳይሆን ፣ አንድን ነገር በቃልና በተግባር ከማስተማር በመጨቃጨቅ አስጨብጣለሁ እንዳይል መጠንቀቅ አለበት ። ቀድሞውኑ የሚጨቃጨቅ ሰው ኤጲስ ቆጶስ ሊሆን አይገባውም ። በመጨቃጨቅ እየተሰለቸ ይመጣል ። አብረውት የሚሠሩትን አገልጋዮች ያሰድዳል ። ሰዎች ያለ ጥፋታቸው ራሳቸውን እንዲጠራጠሩ ያደርጋል ። ደግሞም በእግዚአብሔር ረድኤት እንጂ በእርሱ ቊጣ ሰዎች አይለወጡም ። ጨቅጫቃ ከሆነ ግን ሰውን በቊጣዬ እለውጣለሁ ብሎ የመንፈስ ቅዱስን ድርሻ ይወስዳል ። የሰዎችን ነጻ ፈቃድ ይጋፋል ። ይህ ደክሞ ማድከም ነው ።
ምስክርነትን ጭቅጭቅ የሚያደርጉ ሰዎች አሉ ። ያማረውን ቃለ ወንጌል ሰዎች እንዲጠሉ ያደርጋሉ ። ስብከትን ጭቅጭቅ ፣ ምክርን ንዝንዝ ማድረግ አይገባም ። ብዙ ልጆች ከቤት የሚወጡት በዚህ ምክንያት ነው ። አንድን ነገር ደጋግሞ ማውራት ፣ አዲስ አሳብ ማምጣት አለመቻል ጭቅጭቅ ነው ።ዘወትር አንድ አዲስ ነገር ለማወቅ መጣር ከጭቅጭቅ ያድናል ።
አቤቱ ሆይ ፈውሰን ።
1ጢሞቴዎስ 41
ጥር 20 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም