የትምህርቱ ርዕስ | የምሕረቱ አደባባይ ነኝ

“ስለዚህ ግን ፥ የዘላለምን ሕይወት ለማግኘት በእርሱ ያምኑ ዘንድ ላላቸው ሰዎች ምሳሌ እንድሆን ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ዋና በምሆን በእኔ ላይ ትዕግሥቱን ሁሉ ያሳይ ዘንድ ፥ ምሕረትን አገኘሁ ።” 1ጢሞ. 1፡16
ደብተራ ኦሪት የተባለችው የመጀመሪያይቱ መቅደስ ሦስት ክፍሎች ነበሩአት ። የመጀመሪያው አደባባይ ሲባል ፣ ሁለተኛው ቅድስት ፣ ሦስተኛው ቅድስተ ቅዱሳን ይባላል ። አደባባዩ ዐውደ ምሕረት ነው ። ሁሉ የሚያየው ነው ። አደባባዩ ሁሉም ማለት ምእመኑና ካህኑ የሚረግጡት ነው ። አደባባዩ ወደ ቅድስትና ቅድስተ ቅዱሳን ለመግባት ማለፊያና መዘጋጃው ነው ። በአደባባዩ ላይ ሁለት ንዋያተ ቅድሳት አሉ ። የመጀመሪያው የናሱ መሠዊያ ሲሆን ሁለተኛው የመታጠቢያው ሰን ነው ። የናሱ መሠዊያ የኃጢአትና የምስጋና መሥዋዕት የሚቀርብበት ነው ። የናሱ መሠዊያ ላይ ያለው ፍም በቅድስት ውስጥ ያለው የዕጣኑ መሠዊያ ላይ የሚቀርበው ዕጣን የሚጤስበት ነው ። በመሠዊያው በኩል የማያልፍ እንደሌለ በክርስቶስ ቤዛነት በኩል ካላለፈ ማንም ወደ ሕይወት መቅረብ አይችልም ። ምእመኑም ካህኑም በመሠዊያው በኩል ያልፋሉ ። ንጹሕ ኅሊና ለማግኘት በመሠዊያው በኩል ማለፍ ግድ ይላል ። የክርስቶስ ደም የቆሸሸ ኅሊናን የሚያነጻ ፣ የደፈረሰ ሰላምን የሚመልስ ነው ። በደሙ በኩል ካልሆነ ማንም ሰው ወደ መንግሥተ ሰማያት አይገባም ። መሠዊያው ጋ ሲደርስ ሁሉም ሰው ኃጢአቱና የእግዚአብሔር ምሕረት ትዝ ይለዋል ። እንዲሁም የክርስቶስ መስቀል ፊት ስንቆም ማንነታችን በልኩ ይታየናል ። ወዲያውም ልባችን ለንስሐ ዘንበል ይላል ፣ የፈሰሰው የክርስቶስ ደምም ስርየትን ይሰጠናል ። በቅድስት ውስጥ ያለው የዕጣኑ መሠዊያ በጠዋትና በማታ ዕጣን ይጤስበት ነበር ። ይህም የጸሎት ምሳሌ ነው ። ዕጣኑ ግን የሚጤሰው በመንደር እሳት ሳይሆን በናሱ መሠዊያ ላይ መሥዋዕትን ባሳረገው ፍም ነው ። ጸሎትም አምልኮትም ሊቀርብ የሚገባው በቀራንዮ ፍቅር ነው ። በመንደር እሳት በዘመናዊ አምልኮ እግዚአብሔር አይከብርም ። የናሱ መሠዊያ ላይ የኃጢአትና የምስጋና መሥዋዕቶች ይቀርቡ ነበር ። መሠዊያው ስርየትና ምስጋናን ያውጃል ። የክርስቶስ መስቀልም ስርየትና ምስጋናን ያሳስባል ።

ዐውደ ምሕረቱ ወይም የምሕረት አደባባዩ ላይ የምናገኘው ሁለተኛው ንዋየ ቅዱስ የመታጠቢያው ሰን ነው ። የመታጠቢያው ሰን መስታወትና ውኃ ነበረው ። በመስታወቱ ቆሻሻውን ያየው ካህን በውኃው በመታጠብ ለአገልግሎቱ ብቁ ይሆናል ። አንድ አገልጋይ ራሱን በቃሉ ማየትና በመንፈስ ቅዱስ ንጹሕ ልቡናን ገንዘብ ማድረግ ይኖርበታል ። ዐውደ ምሕረቱ ይህን ሁሉ ይናገራል ። ዐውደ ምሕረቱ ሽፍንፍን የሌለው ሁሉ የሚያየው ነው ።
የደብተራ ኦሪት ዐውደ ምሕረት ዛሬ የለም ። ሐዋርያው ጳውሎስ የእኔ ሕይወት ዐውደ ምሕረት ነው ። የእግዚአብሔርን ምሕረት የሚያውጅ ነው ይላል ። እግዚአብሔር አሳዳጁን ተሰዳጅ ፣ ገዳዩን አዛኝ ፣ ሽፍታውን ባሕታዊ ፣ ሌባውን መጽዋች ፣ አመንዝራውን ንጹሕ ሲያደርገው ፣ የተለወጠው ሕይወት ዐውደ ምሕረት ነው ። ሰዎች ጳውሎስን ሲያዩ የእግዚአብሔር ምሕረት እንደገና ዕድል እንደሚሰጥ ይገነዘባሉ ። ከትላንት በደላቸው የዛሬ መመለሳቸው ዋጋ እንዳለው ያውቃሉ ። ካፈርሁ አይመልሰኝ ብሎ ለጥፋት ታማኝ መሆን ሞኝነት መሆኑን ይገነዘባሉ ። እውነትን በተረዱበት ሰዓት መኖር የባከነውን ዘመን መካስ መሆኑን ያውቃሉ ። ጳውሎስ የመሰለው ነገር ክርስቶስ የኦሪት ተቃዋሚ ሁኖ ነበር ፣ እውነቱ ግን የኦሪት ፈጻሚ ነው ። በመሰለንና በእውነቱ መካከል ሰፊ ልዩነት እንዳለ የጳውሎስ ሕይወት አደባባይ ሁኖ ያሳየናል ። በዐውደ ምሕረቱ ላይ የመታጠቢያው ሰን አለ ብለናል ። የጳውሎስ ሕይወትም መስታወት ሁኖ አጉል ቀናተኝነታችንን ያሳየናል ። ጳውሎስ ለእግዚአብሔር ቀንቶ የእግዚአብሔርን ወንጌል አሳደደ ። ሐዋርያው ጳውሎስ የጥንቱን ከአዲሱ ኪዳን ለማስታረቅ በዐረብ ምድር ለሦስት ዓመት ጊዜ ሰጥቶ አጥንቷል ። የሰማውን ቶሎ የሚናገር ሳይሆን የሚያሰላስል ነበር ። ለአገልግሎት ብቁ ለመሆንም የሰሙትን ከማወጅ በፊት በቅጡ ማየት አስፈላጊ ነው ። ይህን ሁሉ የሚነግረን የጳውሎስ ሕይወት ዐውደ ምሕረት ስለሆነ ነው ።
“የዘላለምን ሕይወት ለማግኘት በእርሱ ያምኑ ዘንድ ላላቸው ሰዎች ምሳሌ እንድሆን” ይላል። የዘላለም ሕይወት ለማግኘት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን ያስፈልጋል ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በታሪክ ውስጥ የተከሰተ ድንቅ መምህር ነው ብለው የሚያምኑ አሉ ። የሞራል አብዮትን ያመጣ የፍቅር ሰው እንደሆነም የሚናገሩ አሉ ። እርሱ ግን አምላክ በመሆኑ አዳኝ ፣ ቤዛ በመሆኑም ሕይወትን ከጥፋት የሚጋርድ ነው ። ብዙ ኦሪታውያን ለሕጋቸው ቀንተው ክርስቶስን ሰቅለውታል ። ሐዋርያው ጳውሎስም ምናልባት በዚያ ሸንጎ ላይ ሳይኖር አይቀርም ። በዓይኑ አይቶ የገፋውን ክርስቶስ በራእይ ቢያየው በደማስቆ መንገድ ላይ ተማረከለት ። ጌታችን ካረገ ከስምንት ዓመት በኋላ ሐዋርያው ወደ ክርስትና ተመለሰ ። ሕይወቱን እያዩ ብዙዎች ወደ ወንጌል ቢመለሱ ሐዋርያው ናፍቆቱ ነው ። ምሳሌ እንድሆን ይላል ። ሰው ምሳሌ የሚሆነው ባደረገው መልካም ነገር ነው ። ሐዋርያው ግን በተቀበለው ምሕረት ምሳሌ እንድሆን ይላል ። እግዚአብሔር የሐዋርያውን ሕይወት የምሕረት ማስተማሪያ አደረገው ።
“ኢየሱስ ክርስቶስ ዋና በምሆን በእኔ ላይ ትዕግሥቱን ሁሉ ያሳይ ዘንድ ፥ ምሕረትን አገኘሁ” ይላል የኃጢአተኞች ዋና ነኝ ማለት ትልቅ ትሕትና ነው ። የሚያጸድቅ እግዚአብሔር ነውና ሐዋርያው ራሱን ለማጽደቅም አልፈለገም ። ዝቅተኛውን ቦታ መርጧልና የጋበዘው ጌታ ትልቁን ወንበር ሰጥቶታል ። አይገባኝም ብሏልና ይገባሃል ተብሎ ተሹሟል ። ትዕግሥቱን በእኔ አሳየ ይላል ። እስኪመለስና እስኪያውቀው ድረስ በተስፋ ጠብቆታልና ትዕግሥቱን ያደንቃል ። ከተመለሰ በኋላ የተቀበለውን ምሕረቱን ሊያመሰግን ይነሣሣል ። ሐዋርያው ይህን ሁሉ የሚናገረው የሕግ አስተማሪዎች ሊሆኑ ወድደው ምሕረቱ ለሰብአ ዓለም ነው ፣ እኛን ግን በሥራችን ዋጋ ይክፈለን ለሚሉ ተግሣጽ እንዲሆን ነው ።
ብዙዎቻችን ክርስትናን የምንኖረው በታላቅ ደስታ አይደለም ። ልንተወው ሲገባን ያልተውነው ክፉ ነገር አለ ። ልናደርገው ሲገባን ያላደረግነው መልካም ነገር አለ ። በዚህ ምክንያት ሕይወታችን ለሌሎች ምሳሌ አይደለምና በእግዚአብሔር ደስ ቢለንም በራሳችን እናዝናለን ። ይህ ተገቢ ኀዘን ነው ። ባደረግነው ምሳሌ ባንሆንም በተደረገልን ነገር ምሳሌ ሆነናልና እግዚአብሔር ይመስገን ። እገሌ እንኳ ፣ እገሊት እንኳ የእግዚአብሔር ሰዎች ሆኑ ብለው ሰዎች እኛን በማየት የእግዚአብሔርን ምሕረት ያደንቃሉ ። ሕይወታችን የምሕረቱ አደባባይ ሁኖ ለማመን ድፍረት ያጡትን ኃጢአተኞች ያደፋፍራል ። አዲስ መድኃኒትን መውሰድ ሰው ሁሉ ይፈራል ። ብዙዎች ሲሞክሩት ግን ለመውሰድ ይደፍራል ። ጳውሎስን ያዳነው መድኃኒት እኔንም ያድነኝ እስኪሉ የሐዋርያው ሕይወት ምሳሌ ሁኗል ።
ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንሄድ ለመታየት ባንፈልግም ፣ አስቀድሰን በቶሎ ውልቅ ብንልም ፣ ሰዋራ ቦታ ሂደን ብንቆርብም ፣ በድብቅ ምጽዋት ብንሰጥም ፣ ሰው ሳያየን ብንጸልይም ፣ ምንም ምልክት ሳይታይብን መጽሐፍ ቅዱስን ብናጠናም ያለነው በእይታ ውስጥ ነው ። ጌታችን የክርስቲያንን ሕይወት ተራራ ይለዋል ። መደበቅ አይችልም ።   በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሰወር አይቻላትም” ብሏል ። /ማቴ. 5፡14/ ። ሰዎች ሲያዩን ለእግዚአብሔር ከመሥራታችን በፊት እግዚአብሔር የሠራልንን ያያሉ ። እኔም ተስፋ አለኝ ብለው ለመዳን ይከጅላሉ ። እያንዳንዱ ክርስቲያን ዐውደ ምሕረት ወይም የምሕረቱ አደባባይ ነው ።
ገቢና ወጪያችን ሳይመጣጠን ስንኖር ይህን ያደረገው ምሕረቱ ነው ። ድጋፎቻችን ተሰብረው ያልወደቅነው በምሕረቱ ነው ። የሚዝቱብን በዝተው ያልጠፋነው በምሕረቱ ነው ። አለቀላቸው ስንባል እንደገና አዲስ ሰው የሆነው ከምሕረቱ የተነሣ ነው ። የነደደው እሳት ወላፈኑ አጠገባችን ያሉትን ሲገድል ፍሙ ግን ልብሳችንን እንኳ ያላጠቆረው ከምሕረቱ ተነሣ ነው ። “የምጣዱ ሳለ የእንቅቡ ተንጣጣ” እንዲሉ እሳቱ የሚነድብን እኛ ታግሠን ፣ በሩቅ ያሉት የሚጮኹት ምሕረቱ ስላስቻለን ነው ። ያለ ቀልባችን ሁነን ስንበርር አደጋውን ያለፍነው በምሕረቱ ነው ። በረሀብ ዘመን የጠገብነው ፣ በሚቻልበት ዘመን ያጣነውን በማይቻልበት ዘመን ያገኘነው በምሕረቱ ነው ። ዘመድ ያላቸው ሲሸበሩ ምልምል ዛፍ የተባልነው እኛ የተረጋጋነው በምሕረቱ ነው ። ያገር ልጅ ጠላት ሁኖን ባዕድ የተዛመደን በምሕረቱ ነው ። ሕይወታችንና ኑሮአችን የምሕረቱ አደባባይ ነው ። እግዚአብሔር ማን እንደሆነ ለማወቅ እኔን ተመልከቱ እስክንል ድንቅ የተደረገልን ፣ በጥበቡ የኖርን ነን ።
እነዚያ የባቢሎን ምርኮኞች ፣ አገር አልባ የሆኑት ፣ መጽናኛ መቅደሳቸው የፈረሰባቸው ፣ ንጉሥና ካህና የራባቸው ፣ ሽማግሌ አጥተው የትላንቱ መስተዋት የተሰበረባቸው እንዲህ ብለው ዘመሩ፡- ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ምሕረት የተነሣ ነው ርኅራኄው አያልቅምና ።” /ሰቆቃወ ኤር. 3፡22/

በምሕረትህ ባለጠጋ የሆንኸው ፣ ዛሬም እኔን ለመሸከም ያልሰለቸኸው ውድ አምላኬ ተመስገን!
1ጢሞቴዎስ /18/
ኅዳር 29 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም