መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የምንከተለው ማንን ነው ?

የትምህርቱ ርዕስ | የምንከተለው ማንን ነው ?

“እንግዲህ እንደ ተወደዱ ልጆች እግዚአብሔርን የምትከተሉ ሁኑ”

ኤፌ. 5 ፡ 1 ።

ሥልጠና እንኳን ሰውን እንስሳትን ሳይቀር ይለውጣል ። ከመመርመሪያ ማሽኖች ይልቅ መርማሪ ውሾች ውጤታማ እየሆኑ ነው ። ወደዚህ ብቃት የደረሱት ግን በሥልጠና ነው ። ሥልጠና የሰውን ሀኬተኛነት በመውሰድ ትጋትን ይሰጣል ። ትላንት የማይችለውን ነገር እንዲችል ያደርገዋል ። ሥልጠና ዘላንነትን ወደ ሥነ ሥርዓት ፣ የተለምዶ ነዋሪነትን በዓላማ ወደ መኖር ይቀይራል ። ዛሬ አሉን የምንላቸው በጎ ነገሮች የሥልጠና ውጤት ናቸው ። ሥልጠና ሌሎች ለእኛ ይሰጡናል ፣ ራሳችን ለራሳችንም የምናስለምደው የሕይወት መርህ ነው ። ሥልጠና በመጀመሪያው አለማወቅንና አለመቻልን ያሳያል ፣ ቀጥሎ ማወቅና መቻልን ያመጣል ። ሥልጠና ራስን ማስለመድ ነው ። ራሳችንን ስፖርት ካስለመድነው ራሱ አምጡ ይለናል ። ሥልጠና ወደ መልካም ሱስ ይከተናል ። መልመድ ሳይሆን መለማመድ በመሆኑ ሥልጠና ዋጋ የሚያስከፍል ነገር ነው ። ክርስትና በዚህ ዘመን ቅመሙን አጥቶ አልጫ የሆነው ፣ በአረመኔነት ተቀምሞ የሰውን ሕይወት የሚቀጨው ሥልጠና ወይም ራስን ማስለመድ በመጥፋቱ ነው ። ክርስትና መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ፣ አለቃ ፣ መርህና የሚኖሩለት ዓላማ ያለው ነው ። ዛሬ ክርስቲያኑ ለራሱ አባት ፣ ለራሱ ልጅ እየሆነ ሲመጣ ፣ ራሱ መርህና ራሱ ግብ እየሆነ መጣ ። በዚህ ምክንያት  የሚታየው በቀዳዳ ስልቻ የመሙላት ትግል ውስጥ ገባን  ። ዛሬ ከምናያቸው የጭካኔና የዘረኝነት ፉጨት ጀርባ ክርስቲያን ነን የሚሉ አሉበት ። መነቃቃት አገኙ የተባሉ ከተሞች ሳይቀር አንገት የሚቀላባቸው የጭካኔ ካምፕ ሁነዋል ። ድንቄም መነቃቃት !! የአገሬ ሰው፡- “ጽድቁ ቀርቶ በቅጡ በኰነነኝ” የሚለው ለዚህ ነው ። ክርስትና ራስን ማስለመድና መለማመድ የሚፈልግ ነው ። መንፈሳዊ ዕድገት ማለት ተአምራዊ ዕድገት አይደለም ። በተአምራት እንፈወሳለን እንጂ አንለወጥም ። መንፈሳዊ ዕድገት ደግሞ ራስን የማስለመድ ውጤት ነው ።

“ተመልከት ዓላማህን ፣ ተከተል አለቃህ” ይባላል ። የወታደር ቤትን ልዩ የሚያደርገው የሚመለከተው ዓላማና የሚከተለው አለቃ ያለበት መሆኑ ነው ። ወታደር ከሀ እስከ ፐ በሥነ ሥርዓት የታነጸ ነው ።  ወታደር የሚያሰኘው ልብሱ ሳይሆን ዲሲፕሊኑ ነው ። ራሱ ጸንቶ በመቆም አገሩን ለማቆም የሚጥር ነው ። የወታደር ዓላማው አገሩንና ሕዝቡን መጠበቅ ነው ። ወታደር ዘርና ጎሣ አለኝ ብሎ ለዚያ ካደረ ወታደርነቱ እያበቃ ይመጣል ። ከፍ ብሎ የተሰቀለ ፣ የሚኖርለትና የሚሞትለት ዓላማ ያስፈልገዋል ። በዓላማው መሠረትም አለቃውን መከተል ያሻዋል ። ክርስቲያንም ልክ እንደ ወታደር ዓላማውን ፍቅር ፣ አለቃውን ክርስቶስ መከተል አለበት ። ፍቅርን የጣለ ፣ ክርስቶስን ከመከተል የተመለሰ ክርስቲያን ሊሆን አይችልም ። ክፋትን ካልተጠየፈ ፣ ወንጀልን ካላወገዘ ክርስቶስን እንደ ገና በታሪኩ የሚሰቅል ይሆናል ።

ራስን ማስለመድና መለማመድ ያለበት ሥልጠና አንዱ መገለጫው መከተል ነው ። እንስሳት መጀመሪያ የሚሰለጥኑት የሚያሰለጥናቸውን በመከተል ነው ። በስልጠና ውስጥ መቀመጥ ፣ መቆም ፣ ሰላምታ መስጠት ፣ መከተል ወሳኝ ናቸው ። የሚከተሉት በአለቃው እርምጃ መጠን ነው ። የሚመራቸውን ማወቅና መንገዳቸውን ይዘው መሄድ ይገባቸዋል ። ሰውም ከፍ ያለ ፍጡር ቢሆንም መሪ ያስፈልገዋል ። ሰው በዋናነት የሚከተለው እግዚአብሔርን ነው ። ልጆቻችንን ማሰልጠን አለብን ። ሳንናገር እንድንግባባ አድርገን ፣ ሁሉን እንዲወዱና ሁሉን እንዲያፈቅሩ አድርገን ማለማመድ ያስፈልገናል ። ቤተ ክርስቲያንንና አገራቸውን እንዲያፈቅሩ ፣ ድሆችን በፍቅርና በርኅራኄ እንዲመለከቱ ተግተን ማስተማር ይገባናል ። ማሰልጠን እስኪይዙት ድረስ በጣዕም ማስተማር ፣ በተግባር አርአያ መሆንና ማለማመድ ያለበት ነው ።

ተወዳጅ ልጆች የሚባሉት ወላጆቻቸውን የሚከተሉ ሲሆኑ ተወዳጅ ክርስቲያኖችም እግዚአብሔርን የሚከተሉ ናቸው ። እግዚአብሔርን የሚከተሉትም ውስጣዊ ጥላቻን በማራቅ ፣ የተበዳይነት ስሜትን በመጣል ፣ ግልፍተኛነትን በመተው ፣ አስደንጋጭ ቍጣን በማራቅ ፣ በጩኸት አሳምናለሁ ብሎ መነሣትን በማቆም ፣ የሰውን እንከን እየፈለጉ ማዋረድን በመጠየፍ ፣ ሰውን ጠልፎ መጣልን እንደ ቆሻሻ በመመልከት ነው ። ኤፌ. 4 ፡ 31 ።

እየተከተልን ያለነው ማንን ነው ብለን ራሳችንን መጠየቅ አለብን ። አንድ ሰው በጣም በኦርቶዶክሳዊነቱ አትንኩኝ ባይ ነው ። በቅርብ ሰሞን ግን ዘሩና ጎሣው እያንገበገበው ይሳደባል ። “ከክርስትናህና ከጎሣህ ?” ብለው ቢጠይቁት “ጎሣዬ ይበልጥብኛል” አለ ። አንዳንድ ሰው ሃይማኖቱን የያዘው ጎሣው እስኪመጣ መጠበቂያ አድርጎ ነው ። እየተከተልን ያለነው ወቅታዊ ዘፈኖችን ፣ ጊዜ የሰጣቸው ወሬዎችን ፣ የፖለቲከኞችን የተስፋ ዳቦ ሊሆን ይችላል ። እግዚአብሔርን መከተል ግን ወደ ዘላለም ደጃፍ ያደርሳል ።

መከተል መሰልጠን ነው ። ትውልዳችንን በዘረኝነት ሳይሆን በፍቅር ማሰልጠን ያስፈልገናል ። ገና ጨዋታ ሳይጠግቡ ቂምን እያስታጠቅን የዕድሜ ልክ ታማሚ ማድረግ የሚበጅ አይደለም ። ልጆቻችንን በቁም መግደል ነው ። ወጣቱ እያጠፋ ነው ፣ እያየንም ነው ። የሚለውጠው ግን ትምህርት ነው ። በቂ እውቀትና ሀብት ያላቸው ትውልድን ለመቅረጽ ፣ በፈሪሀ እግዚአብሔር ለማነጽ መነሣት አለባቸው ። በማውገዝ ብቻ ሰው አይለወጥም ፣ እኛም አናርፍም ።  እግዚአብሔርን ስለ መከተል ማስተማር ይዋል ይደር የማንለው ተግባራችን ሊሆን ይገባል ። ያለን ብቸኛ መፍትሔ ትውልድን ማስተማር ፣ በፈሪሀ እግዚአብሔር ማነጽ ብቻ ነው ። የተለወጠ ትውልድ ያልተለወጠን አገር ይለውጣል ፣ ያልተለወጠ ትውልድ ግን የተለወጠን አገር ያፈርሳል ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 18 ቀን 2012 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም