መግቢያ » ከመጻሕፍት » ወዳጄ ሆይ » የቀኑ ወለላ

የትምህርቱ ርዕስ | የቀኑ ወለላ

 

ወዳጄ ሆይ !

አንተ ላጣኸው የሚሸሽህ ሲበዛ አትገረም ፤ ፀሐይ ስትጠልቅ እንኳን ሰው የገዛ ጥላህም ይሰወራልና ። እግዚአብሔር የዘገየ የመሰለህ አንተ ስለቸኮልህ ነው ። የእግዚአብሔር ቀን በድንገት ትመጣለችና ተዘጋጅተህ ኑር ። ትልቅ ጅማሬ ከፈለግህ ፍጻሜህ ትንሽ ነው ፤ ትንሽ ጅማሬም ፍጻሜው ትልቅ ነው ። ጥርስና ምላስ ቢነካከሱም ፣ ጥርስና ምላስ ባይመሳሰሉም አብረው ይኖራሉ ። ብንጣላም ሳንጠላላ መኖር ግድ ነው ። አንድን ነገር ስታገኝ ሌላውን እንዳጣህ እወቅ ። በጅምርህ ሰዎች ሲንቁህ በአቅምህ ሳይሆን በራሳቸው አቅም ለክተውህ ነው ። ራስህን ካላበረታኸው የሚያዳክምህ ብዙ ነው ። ያለ አስታዋሽ ቁርስ እየበላህ ለጸሎትና ለቃለ እግዚአብሔር አስታዋሽ አትሻ ። 

ወዳጄ ሆይ !

በክፉ ሥራህ የሰው ዓይን ባያይህ ሕሊና አይቶሃልና መሰደድን አታቆምም ። ድንጋይ በውኃ ውስጥ ቢኖርም አይርስም ፣ እንዲሁም ቃሉን እየተማሩ የሚደነድኑ አሉ ። ድንጋይ መኖሪያው ውኃ ውስጥ ቢሆንም ዋና አይችልም ይባላል ፣ ሰዎችም እረኛ ተብለው ስለተሾሙና በቤተ ክርስቲያን ስላሉ ብቻ መምራት ይችላሉ ማለት አይደለም ። የሰማኸውን ስብከት እየረሳህ የሰማኸውን ስድብ ማስታወስ ተገቢ አይደለም ። አንተ እንድትፋፋ የከሱልህን አትርሳ ። አገርህን ቀብረህ ቀና ብትልም የሚያይህ የለም ። አገርህን አፍርሰህ ሰው አገር ብትቀመጥም አንድ ቀን መግቢያ ታጣለህ ። ብዙ ወዳጅ እንዳለህ ብታስብ እውነቱን የሚነግርህ የመከራ ቀን ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

ሰውን በልብሱና በቤቱ ትልቅ ነው ብለህ አትለካው ። የሰዎችን ምሥጢር ለማወቅ አትጓጓ ። የተሸከመህን መሸከም ክብር ነው ። ሰውን በደንብ እስክታየው የእንስሳት ፍቅር አይገባህም ። ና ብሎ ዕዳ እንዲሉ መለወጡን ሳታይ የቀድሞ ባለጌን አትጥራ ። ወደ ኋላ ለምስጋና ፣ ወደፊት ለግብ ተመልከት ። በዓለም ላይ ሦስት ርካሽ ሰዎች አሉ ። አራተኛውን ግን መሬት አይችለውም ። ተሰጥቶአቸው የማያውቁበት ፣ የነበሩበትን የረሱ ፣ በሰው ውድቀት የሚስቁ ርካሾች ሲሆኑ አራተኛው ግን አምላኩን የካደ ነው ። ሰዓቱ አለፈ ብለህ ከንስሐ አትዘግይ ፤ በሕይወት እስካለህ የንስሐ ዕድል መሆኑን ተረዳ ። እግዚአብሔር ሲደርስ የባከኑ ዘመኖችን ይክሳል ። ሰይጣን የሚፈትንህ ትዕግሥት እንድታጣ ነው ፤ ከዚያ በኋላ የምትወድቀው አንተ ነህ ። አዳም አንድ ጊዜ በሰይጣን ተፈተነ ፣ ውድቀቱ ግን ውድቀት እየወለደ ሲንከባለል ኖረ ። እንደ ጠበቅከው አለመሆኑ ሰው የመሆንህ መገለጫ ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

በሞላ ውኃ አለመታጠብ ፣ በበዛ ቃለ እግዚአብሔር አለመማር ትልቅ ክስረት ነው ። እንደ ማግኔት ተቃራኒህን ካልሳብህ የክርስቶስ ፍቅር ባንተ ላይ የለም ። በየቀኑ እንዳታዝን ስሜትህን ሳይሆን እውነትን ተከተል ። ሌሎችን ማክበር ያለብህ አንተ የሌለህን ስለያዙ ነው ። እያንዳንዱ ትምህርት ሕመም አለው ፤ እያንዳንዱ ሕመምም ትምህርት አለው ። ሕይወትን ዘወትር አዲስ የሚያደርጋት ክፉዎች ቆመው ደጎች ሲወድቁባት ነው ። እንደ ጤና ጣፋጭ ፣ እንደ ፍቅር ማዕረግ ፣ እንደ ይቅርታ ድል ፣ እሰው ፊት እንደ መቆም መራራ የለም ። የገዛኸው እህል አንዱ ፍሬም ሲንጠባጠብ ይቆጭሃል ፣ እግዚአብሔርም በአምሳሉ የፈጠረው ፣ በደሙ የገዛው አንድ ሰው ሲሞት ያዝናል ። ለመፍረድ አቅም ያገኘኸው ለማፍቀር ጉልበት ስላጣህ ነው ። ሌሎችን መጥቀም ትልቅነት ነው ፣ ካልሆነልህ ግን አለመጉዳትም ጨዋነት ነው ። እውነተኛ አስታራቂ ቢኖር ብዙ እሳቶች በበረዱ ነበር ። 

ዲያቆን አሸናፊ መኮንን

ኅዳር 11 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም