የትምህርቱ ርዕስ | የበዛ እውቀት

“ጸጋውንም በጥበብና በአእምሮ ሁሉ አበዛልን ።”

ክርስቲያናዊ ሕይወት ከእውቀት ጋር የተሳሰረ ነው ። በእውቀት አይዳንም ፣ ያለ እውቀትም አይዳንም ። ከነገረ ድኅነት ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያለው ቅዱስ ቍርባን የሚወስደው ሰው የክርስቶስን ሞትና ትንሣኤ መናገር አለበት ። አሊያ ዕዳ ይሆንበታል ። “ይህን እንጀራ በበላችሁ ጊዜ ሁሉ፥ ይህንም ጽዋ በጠጣችሁ ጊዜ ሁሉ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ሞቱን ትናገራላችሁና” ይላል ። 1ቆሮ. 11፡20 ። ክርስትና በማወቅ የሚጀመር ጉዞ ሲሆን ታውቆ የማይፈጸመውን ነገረ እግዚአብሔር ሲረዱ መኖር ነው ። የክርስቲያናዊ እውቀት መሠረቱ አስተርእዮ ወይም አምላካዊ መገለጥ ነው ። እግዚአብሔር ራሱን በፍጥረት ፣ በተአምራት ፣ በመጻሕፍት ፣ በነቢያት ገልጧል። እግዚአብሔር መታወቅ የሚፈልግ አምላክ ነው ። እግዚአብሔር መታወቅ የሚፈልግ አምላክ ስለሆነ በፍጥረት ላይ የኃያልነቱና የጥበበኛነቱ አሻራ ጎልቶ ይነበባል ። ዓይንን ግንባር ላይ ማድረጉ እግር ላይ አለመሰካቱ ጥበበኛነቱ ነው ። ሁሉንም በቦታና በዘመኑ ማስቀመጡ የጥበቡ መገለጫ ነው ። ግዙፉ ሰማይ ፣ በመለኪያ የማይታወቀው ባሕር ፣ ከሚዛን በላይ የሆኑ ተራሮች የኃያልነቱ አስረጂ ናቸው ። ፍጥረት በዘፈቀደ እንዳልመጣና ወደ ታላቅ ግብ እየተጓዘ እንደሆነ የሚካድ አይደለም ። ሁሉንም በመልክ በመልክ ያስቀመጠ ጉዞውን ያስጀመረና እስካሁንም እየመራ ያለው እግዚአብሔር ነው ። ዓለም እንዲህ ሰክራ እንኳ ያልወደቀችው የእግዚአብሔር እጅ ከለላ ስለሆነላት ነው ።

የዚህችን አገር መሪ ስሙን ለመጥራት ባንወድ እንኳ ገዥነቱን ልባችን ይቀበለዋል ። እንዲሁም አንድ ኃይል አለ የሚሉ እግዚአብሔር ብለው ግን ለመጥራት የማይፈልጉ ቢኖሩም እግዚአብሔር ግን ይገዛቸዋል ። እርሱ ሳይሰጋ ይኖራል ። እርሱ ለፍጥረቱ እውቅና ይሰጣል እንጂ ፍጥረቱ ለእርሱ እውቅና አይሰጠውም ። ለአባቱ እውቅና የሰጠ ልጅ ፣ ሠሪውን የቀደመ ሸክላ የለም ። ያልካደንን እግዚአብሔር መካድ በእውነት ነውር ነው ።

አምልኮት ሙሉ የሚሆነው በእምነትና በመንፈሳዊ ዓይን በማየት ብቻ ሳይሆን በእውቀትም ነው ። እግዚአብሔር በስሙ የሚለመን አምላክ ነውና ስሙን ካላወቅን መለመን አንችልም ። ሰው በአእምሮውና በመንፈስ ቅዱስ መጸለይ አለበት ። አሊያ አምልኮቱ ሙሉ አይሆንም ። አምልኮ አብሾ እንደ ጠጣ ለፋፍ ፣ እንደ ሰከረ ጥጋበኛ ፣ አቅሉን እንደ ሳተ ሰው መዘላበድና መጮኽ ያለበት ሳይሆን በአእምሮና በመንፈስ የሚከናወን ነው ። ሰው አሜን ብሎ የሚለምነውን ነገር አውቆ ካልተባበረ አሜን ባለማለቱ መልሱ ይቀራል ። በረከቱ ይዘገያል ። አእምሮ ማለት እውቀት ማለት ነው ።

እውቀት ብቻውን ወደ ክርስቶስ ባያቀርብም ያለ እውቀት ወደ እምነት መምጣት አይቻልም ። ጻፎችን ፈሪሳውያም ክርስቶስ የት እንደሚወለድ በቂ እውቀት ነበራቸው ። ተወለደ ሲባል ግን ልባቸው አልደነገጠም ። ለሄሮድስም የነገሩት እንዲሰግድለት ሳይሆን እንዲገድለው ነው ። /ማቴ. 2፡5/ እውቀት ብቻና ያለ እውቀት መሆን ሁለቱም አደጋ አለው ። ከሁሉ የከፋው ግን ሳያውቁ የሚያውቁ የሚመስላቸው ፣ በተቦጨቀ ጥቅስ ዶግማ ሲቀርጹ የሚውሉ ፣ ስተው የሚያስቱ ሰዎች ናቸው ።

ነገረ ድኅነት እውቀትን አብዝቷል ። ስለ ቅድስት ሥላሴ ያወቅነው ፣ ነገረ ሥጋዌን በልካችን የመረመርነው በዳነ አእምሮ ነው ። አልማርም የሚል ሰው ለቤተ ክርስቲያን አደጋ ነው ። የበዛልን እውቀትም ምሥጢረ ሥላሴና ምሥጢረ ሥጋዌ ነው ። ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን መሠረታቸው ነገረ ሥጋዌ ፣ የሥጋዌ መሠረትም ምሥጢረ ሥላሴ ነው ። በማይናወጥ መሠረት ላይ ለመቆምና ለሌሎችም የመዳን ምክንያት ለመሆን ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን የምታስተምረውን ነገረ ሃይማኖት ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል ።

እውቀት ያሳስታል የሚሉ ሰነፎች ሲሆኑ መዳን በእውቀት ነው የሚሉም ግኖስቲካውያን ሁለቱም በቤተ ክርስቲያን የተወገዙ ናቸው ። “እኔ እንደሚመስለኝ ፣ ለእኔ እንደ በራልኝ” እያሉ መጽሐፍ ቅዱስን የሚተረጉሙ ወጣቶች ኢትዮጵያውያን ናቸውና እንደ ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ፡- “የሚመራኝ ሳይኖር ይህ እንዴት ይቻለኛል?” ማለት ይገባቸዋል ። የሐዋ. 8፡31። ይህን ጥያቄ የተቀበለው ወንጌላዊው ፊልጶስ ተርጓሚ አያሻም እንዳሻህ ተርጉመው አላለውም ፣ ተረጎመለት እንጂ ። ከዚያም አምናለሁ ብሎ ለመጠመቅ አስቀድሞ አሳብ አቀረበ ። እስከ ምሥጢረ ጥምቀት ድረስ ባይማር ኖሮ ልጠመቅ ብሎ አይጠይቅም ነበር ። መማር ማወቅ ለዳኑ ሕዝቦች የተሰጠ ትልቅ በረከት ነው ። እውቀትን ከሚጠላ መንፈስ አድነን ።

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /17

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 30 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም