መግቢያ » ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ/2

የትምህርቱ ርዕስ | የቤተ ክርስቲያን ታሪክ/2

የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ ማወቅ ምን ይጠቅማል ?
ሊቀ ነቢያት ሙሴ፡- “የዱሮውን ዘመን አስብ ፣ የብዙ ትውልድንም ዓመታት አስተውል ፤ አባትህን ጠይቅ፣ ያስታውቅህማል፤ ሽማግሌዎችንም ጠይቅ ፣ ይነግሩህማል” ብሏል ። ዘዳ. 32፡7። የሺህ ዓመታትን ታሪክ መጠየቅ እንደሚያስፈልግ ሊቀ ነቢያት ሙሴ በመጨረሻው ቡራኬና ምክሩ ተናግሯል ። ታሪክን መመርመር የእግዚአብሔር ሕዝብ የተጣለበት አደራና ግዴታ ነው ። ሊቀ ነቢያት ሙሴ በአማራጭ ሳይሆን በትእዛዝ አንቀጽ መናገሩን ማስተዋል ያስፈልገናል። የታሪክ ምንጭ ከሆኑት ውስጥ በመኖር የሚቀድሙ አባቶችና ሽማግሌዎችን ይጠቁማል።

ሁላችንም የታሪክ ውጤቶች ነን ። ብዙ ሰዎች ታሪክን ማጥናት ትርፍ ነገር እንደሆነ ያስባሉ። የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ራሱ እግዚአብሔር ሥጋ ለብሶ የሠራውና በቅዱሳን አባቶች አድሮ መንፈስ ቅዱስ ያከናወነው ተግባር የሚጠናበት ነው። የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያለፈውን ለማወቅ ፣ ያለውን ለማስተዋል ፣ የሚመጣውን ገምቶ የራስን ድርሻ ለማስቀመጥ የሚረዳ ነው። ሁለት ዓይነት ታሪክ አለ ፤ አምላካዊና ሰብአዊ።ታሪክን ከክርስትና ውጭ ማድረግ ተገቢ አይደለም ። ዋናው ክርስትና ነው ቢባልም ክርስትና እኛ ጋ የደረሰው በታሪክ ውስጥ አልፎ ነው ። ታሪክን አለመጠየቅና አለመማር ትእዛዘ እግዚአብሔርን መተላለፍ መሆኑን በነቢዩ ሙሴ የተነገረው ያሳየናል ። በዚህ ክፍል ላይም የታሪክ ምንጮች ሽማግሌዎች ናቸው ። የቀዳሚ ሰማዕት እስጢፋኖስና የንዋየ ኅሩይ የጳውሎስን ትረካ ያጣፈጠው ታሪክን ጠቅሰው በመናገራቸው ነው ። /የሐዋ. 7፡2-53፤ 22፡2-21/ ። ታሪክን ማወቅ የሰሚዎችን ጆሮ ይከፍታል ። አንድ ፈረንጅ መጥቶ ስለ አክሱምና ስለ ላሊበላ ቢነግረን ታሪኩን ብናውቀው እንኳ ውስጣችን ደስ ይለዋል ። ያንንም ሰው እንደ ባዕድ ከማየት ቤተኛ አድርገን እንመለከተዋለን ። ታሪክን ማወቅ ቤተሰብ ይፈጥራል ።
የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ምንድነው ?
የቤተ ክርስቲያን ታሪክ የእግዚአብሔር መንግሥት ታሪክ ነው ። በሚታየው የምድር መንግሥታት ጉዞ ውስጥ የማይታይ አንድ መንግሥት አለ ፣ እርሱም የእግዚአብሔር መንግሥት ነው ። ቤተ ክርስቲያን የዚህ ሰማያዊ መንግሥት ቋሚና ተጠሪ ናት ። የቤተ ክርስቲያን ታሪክ መሠረትም የወልደ እግዚአብሔር ሰው መሆን ነው ። የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ስፋትም ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ ወንጌልን ለፍጥረት ስበኩ የሚለው ታላቅ ተልእኮ ነው ። የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፡-
1-  ስለ ክርስትና የሚያጠና የትምህርት ዘርፍ ነው ።
2-  ቤተ ክርስቲያን ያደገችበትን ሁኔታ ያጠናል ።
የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ ማጥናት፡-
1-  እግዚአብሔር ለአባቶቻችን ያደረገውን ለማድነቅ ፣
2-  የወደቅንበትን ቦታ እያየን ከማዘን ለማስተካከል ይረዳል ።
የቤተ ክርስቲያን ታሪክ የተጠናቀቀ ሳይሆን ክርስቶስ ዳግመኛ እስኪመጣ ድረስ የሚቀጥል ነው ። እኛም የቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደሆንን ማወቅ ያስፈልጋል ። የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ ማወቅ አለመፈለግ ስለራሳችን ማወቅ አለመፈለግ ነው ። የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ከቤተ ልሔም እስከ ቀራንዮ ፣ ከሰማዕታት ዋሻ /ካታኮምብ/ ፣ እስካለንበት ዘመን ድረስ ያለውን የምናይበት ነው ። የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ ለምን እናጠናለን ካልን፡-
1-  የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ ማወቅ ለእምነታችን ምቹ ሁኔታ ይፈጥርልናል ። ስለምናምነው እምነት በታሪክ ውስጥ ያለውን የመረጃ ክምችት እናውቃለን ።
2-  ለመጽናት በጣም ይጠቅመናል ። ሐዋርያው በዕብራውያን 11 ላይ ገድለ ቅዱሳንን ተረከና እነዚህ ሁሉ ለእምነት ጽናታችን ጠቃሚ እንደሆኑ ሲገልጽ እንዲህ አለ፡- እንግዲህ እነዚህን የሚያህሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን…ዕብ. 12፡1
3-  ቤተ ክርስቲያን የምታምንባቸው የነገረ መለኮት ትምህርቶች በቅርጽ የተቀመጡት በታሪክ ውስጥ በተነሣ ግጭት ነው ። አንዳንድ የሃይማኖት አንቀጾች ታሪክን ካላወቅን የምንረዳቸው አይደሉም ።
4-  የቤተ ክርስቲያን ታሪክ መጽሐፍ ቅዱስን ለመተርጎም በጣም አስፈላጊ ነው ። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር አሳብ ቢሆንም በሰው ቋንቋ ፣ ባሕልና ታሪክ ውስጥ የተገለጠ ነው ።
5-  የእግዚአብሔርን ሥራ ያሳያል ። ቤተ ክርስቲያን ስትደክም እንድትበረታ ያደርጋል ። እግዚአብሔር በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሠራው ሥራ አለና ።
     
ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ሦስት ነገሮችን ማወቅ አስፈላጊ ነው ። የመጀመሪያው መሠረተ እምነቷን ማወቅ ነው ። ሁለተኛው ታሪኳን ማወቅ ነው ። ሦስተኛው ፈተናዋን ማወቅ ነው ። ታሪክን የማያውቅ ሰው ሁሉም ነገር ዛሬ የጀመረ እየመሰለው ይደነግጣል ። በመደነቅም ጉልበቱን ይጨርሳል ። የሚሆነው ሲሆን የነበረ መሆኑን የምንገነዘበው ታሪክን ስናውቅ ብቻ ነው ። ታሪክ ያለፈውን ሃይማኖታዊ ፣ ፖለቲካዊና ባሕላዊ ክስተቶችን የምናጠናበት ዐውድ ነው ። ሰው በጊዜ የተወሰነ ፍጡር ነውና ያልፋል ፣ ያለፈውን አውቆ የራሱን ጨምሮ ለመሄድ ታሪክን ማወቅ አስፈላጊው ነው ። ትውልድ የዛሬ ክስተት ሳይሆን ሰንሰለታዊ መስመር ነው ። ሕይወት ወደፊት እልፍ የምናደርገው ጋራ ሥዕል ሲሆን ይህ ሥዕል የሚጠናቀቀው በመጨረሻው ቀን ነው ። የድርሻችንን የምንፈጽመው እንጂ እኛ ጀምረን የምንጨርሰው ተግባር ፣ ወይም በሙሉነት የምንቀርፈው ችግር የለም ። ችግርን ለመቀነስ እንጂ ለመጨረስ የምንሠራ አይደለንም ። ታሪክን ጣዕም ያለው ያደረገው ደረቅ ሁነት ሳይሆን ዛሬም የሚሠራ ሐቅ መሆኑ ነው ።
ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ወሎ ተርቦ ለልደት ቀናቸው ኬክ ከእንግሊዝ አገር አዝዘው አስመጡ የሚል የተጋነነ ፕሮፓጋንዳ ሲወራ ነበር ። የ1966ቱን አብዮት በዚህና በሌላም ነገር ያደመቁት ወገኖች በ1977 ዓ.ም. ሰው በታላቅ ረሀብ እየረገፈ ዐሥረኛውን የአብዮት በዓል ለማክበር ውስኪ በመርከብ አስጭነው አስመጥተው ነበር ። ታሪክ ካልተጠነቀቁት ይደገማል ። ታሪክ በጥንቃቄ ካጠኑትና ካስተዋሉት መንገድ የመምራት አቅሙ ከፍተኛ ነው ።
የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ብለን ስንናገር የዓለም ግማሽ ታሪክ ብለን መናገራችን ነው ። በዓለም ላይ የታየው ሥነ ጽሑፍ ፣ ኪነ ጥበብ ፣ ኪነ ሕንፃ ፣ የተፈጥሮ ጥበቃ ፣ የነገሥታት በቤተ ክርስቲያን አደባባይ መንገሥ ፣ የነጻነት ታሪክ … ከቤተ ክርስቲያን ውጭ የተከናወነ አይደለም ። ቤተ ክርስቲያን ያልነበረችበትን ክስተት ለይቶ ለማውጣት አስቸጋሪ እስኪሆን ድረስ ያለፉት ሁለት ሺህ ዓመታት የዓለም ግማሽ ታሪክ ሁናለች ። በአገራችን እንኳ አክሱምን ፣ ላሊበላን ፣ ፋሲለደስን ፣ ገዳማተ ጣናን ፣ … ስናስብ ቤተ ክርስቲያን ለአገርና ለዓለም ያበረከተችውን አስተዋፅዖ መረዳት እንችላለን ። ቤተ ክርስቲያን ለአገር እንኳ በቱሪስት መስህቧ እንጀራ ናት ።በእንጀራነቷ እንኳ መከበር አለመቻሏ ፣ በግራና በቀኝ እርስዋን ለማፍረስ በጠላት መከበቧ እያደር የሚገርም ሁኗል ። ይልቁንም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከሌለች ኢትዮጵያ ታሪክ የሌላት አገር ትሆናለች ። ፊደልን ቀርጻ የሰጠች ፣ የአገር ፍቅርን ፣ የባንዲራ ክብርን ያስተማረች ቤተ ክርስቲያን ናት ። ከአፍሪካ ብቸኛ የምንሆንበት የራሳችን ፊደል ያለን ሕዝቦች የሆንነው በቤተ ክርስቲያን ነው ።
በዓለማችን ላይ የሚታዩት ትልልቅና ጥንታዊ የትምህርት ተቋማት አስቀድመው ገዳማት እንደነበሩ ይታወቃል ። ቤተ ክርስቲያን የእውቀት ምንጭ ናትና ። ገዳማውያኑ ያስተማሯቸውን ተማሪዎች ለማስመረቅ ሲያስቡ ምን አልብሰን እናስመርቃቸው ሲሉ የራሳቸውን የምንኩስና ልብስ አልብሰው ስላስመረቋቸው ዛሬ የምናየው የተማሪዎች የመመረቂያ ልብስ ተገኝቷል ። በአጭር ቋንቋ በመነኮሳት ልብስ የሚመረቁ አዋቂዎች ቤተ ክርስቲያንን ማወቅና ማክበር ይገባቸዋል ።
የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ ስናጠና ሁለት ነገሮችን መጠንቀቅ አስፈላጊ ነው ።የመጀመሪያው ፍጹምነትን መፈለግና ሁለተኛው ታሪክ አያስፈልገንም ብሎ ማሰብ ነው ።
ቤተ ክርስቲያን በምድር ላይ ያለች የእግዚአብሔር መንግሥት ናት ። ተልእኮዋንም በጊዜና በቦታ ስለምታከናውን የራሷ ታሪክ አላት ። የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ምንጮች ምንድናቸው፡-
1-  ብሉይ ኪዳንና አዲስ ኪዳን
2-  መጻሕፍተ ሊቃውንትና ዓለም አቀፍ ጉባዔያት
3-  የነገሥታት አዋጅ
4-  ትውፊቶች
5- የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ፀሐፊዎች ፣ /አውሳብዮስ፣ ሶቅራጥስ፣ ሩፊኖስ፣…ይጠቀሳሉ/ 
6- በየጊዜው እየተገኙ ያሉ መቃብሮች ፣ ሥዕሎች ፣ ገንዘቦች ፣ መቅደሶች በአጠቃላይ የሥነ ምድር ቁፋሮ ወይም የአርኪዎሎጂ ግኝቶች
7-  የተለያዩ ቅርሶች የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ምንጭ ናቸው ።
ይቀጥላል
እባካችሁ ሰዎች እንዲያውቁ የበኩላችሁን ተወጡ
ዲአመ 
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም