መግቢያ » ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ/3

የትምህርቱ ርዕስ | የቤተ ክርስቲያን ታሪክ/3

የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በዘመን ሲከፈል
የቤተ ክርስቲያን ታሪክ የሚጀምረው በዘፍ. 3፡15 ላይ ለአዳም በተሰጠው የተስፋ ቃል ላይ ነው ። ቤተ ክርስቲያን ከአብርሃም እስከ መጥምቁ ዮሐንስ ዘመን በጠራ ዝግጅት ውስጥ ነበረች ። የቤተ ክርስቲያን መደበኛ ታሪክ የሚጀምረው ከጌታችን መወለድና በሥጋ መገለጥ አንሥቶ ነው ። ቤተ ክርስቲያን በበዓለ ሃምሳ ልደቷን አክብራ በዓለም ሁሉ ተሰራጭታለች ። የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ከቤተ ልሔም እስከ ቀራንዮ ፣ ከካታኮምብ እስካለንበት ዘመን ድረስ ያለውን የምናይበት መጽሔት ነው ። ክርስትና የበቀለው በምድረ እስራኤል ጌታችን በተሰቀለበት በቀራንዮ ሳለ ለዘመናት እንደ ክርስትና መዲና ስትታይ የኖረችው ሮም ናት ። ይህም ቤተ ክርስቲያን ምን ያህል በሮማ መንግሥታት የፖለቲካ ተጽእኖ ውስጥ መውደቋን ያሳየናል ። ስለዚህ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ከኢየሩሳሌም እስከ ሮም ያለውን የምንዳስስበትም ነው ። ቤተ ክርስቲያን በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች በዘመን ትከፈላለች፡-

1-  በተስፋ ዘመን የነበረች ቤተ ክርስቲያን ፤
2-  በፍጻሜ ዘመን ያለች ቤተ ክርስቲያን ።
በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በዋናነት የምናየው ቤተ ክርስቲያን የተከፋፈለችበትን ዘመንና ምክንያት ነው ። አንዲቷ ቤተ ክርስቲያን የተከፈለችበት ዘመን፡-
   1-  በ451 ዓ.ም በኬልቄዶን ጉባዔ ቤተ ክርስቲያን ለሁለት ተከፈለች ። በዚህም የምዕራቡ ራሱን ካቶሊክ ወይም ኩላዊ – የሁሉም ብሎ ሰየመ ። የምሥራቁም ኦርቶዶክስ የሚለውን የኒቅያ ስያሜ ያዘ ።
   2-  በ1054 ዓ.ም. ቤተ ክርስቲያን ለሦስት ተከፈለች ። በዚህም ካቶሊክና የምሥራቅ ኦርቶዶክሶች የተለያዩበት ነው ። የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ዋና የማዕዘን ድንጋይ የሆነውን “መንፈስ ቅዱስ ከአብ ይሠርጻል” የሚለውን የቀና ትምህርት “መንፈስ ቅዱስ ከአብና ከወልድ ይሠርጻል” በሚል አስተምህሮ በመለወጧ የግሪክና የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ተለያይተዋል ።
ማስታወሻ፡- ኦርቶዶክስ የሚለውን ስም የሚጋሩ ለሁለት ይከፈላሉ፡- የምሥራቅ ኦርቶዶክስና የኦሬንታል ኦርቶዶክስ ይባላሉ ። የምሥራቅ ኦርቶዶክስ የሚባሉት ግሪክ ፣ ሩሲያ ፣ ሰርቢያ ፣ ዩጎዝላቪያ ናቸው ። የኦሬንታል ኦርቶዶክስ የሚባሉት ደግሞ የኢትዮጵያ ፣ የግብጽ/ኮፕት/ ፣ የሶሪያ፣ የአርመን ፣ የሕንድ ፣ የኤርትራ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ናቸው።
   3-  በ1517 ዓ.ም. በፕሮቴስታንት እንቅስቃሴ ቤተ ክርስቲያን ለአራት ተከፍላለች ። ከካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ተቃውሞ አድርገው የወጡ ሉተርና ተከታዮቹ ራሳቸውን ፕሮቴስታንት ብለው ሰይመዋል ። ፕሮቴስታንት ማለት ተቃዋሚ ማለት ነው ።
የቤተ ክርስቲያን ታሪክ አከፋፈል
ቤተ ክርስቲያን ሦስት ዓይነት የታሪክ አከፋፈሎች አሏት፡-
1-  የጥንት ቤተ ክርስቲያን ታሪክ
2-  የመካከለኛው ዘመን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ
3-  የኋለኛው ዘመን ወይም አዲሱ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ
የጥንት ቤተ ክርስቲያን ታሪክ
የጥንት ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የተለያየ አከፋፈል አለው ። ታሪካዊ ክስተቶች ልባቸውን እንደ ገዛው መጠን ዘመኑን በተለያየ መንገድ ይከፋፍሉታል።
1-  ከ33 ዓ.ም. እስከ 313 ዓ.ም ይህ ዘመን ከጌታችን ሞትና ትንሣኤ እስከ ቆስጠንጢኖስ መንገሥ ወይም ቤተ ክርስቲያን ነጻነት እስካገኘችበት ድረስ ያለው ነው ። ይህ ዘመን የግሪካውያንና የሮማውያን ሥልጣኔ ተቀላቅሎ ዓለምን የሚገዛበት ጊዜ ነው ።  ግሪካውያን የኃይል በትራቸው ከእስክንድር በኋላ ሲያበቃ ጥበባቸው ግን ዓለምን መግዛት ጀመረ ። ይህም አካልን ከመግዛት የሰውን መንፈስ ወደ መግዛት የተሻገሩበት ነው ። በዚህ ዘመን ሮማውያን በሥልጣን ፣ ግሪኮች በጥበብ ዓለምን ይገዙ ነበር።
2-  ከ33-451 ዓ.ም. ይህም ከጌታችን ሞትና ትንሣኤ እስከ ኬልቄዶን ጉባዔ ያለው ጊዜ ነው ። የጥንቷን ቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንዲህ የሚከፍሉ አሉ ። 451 ዓ.ም ቤተ ክርስቲያን ለሁለት የተከፈለችበት ትልቅ ታሪካዊ ሁነት ያለበት ነው ።
ምዕራባውያን ለጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የራሳቸው አከፋፈል አላቸው።
1- ከ33 ዓ.ም. እስከ 590 ዓ.ም ። ይህም ከጌታችን ሞትና ትንሣኤ ትልቁ ጎርጎርዮስ ጳጳስ እስከሆነበት ያለው ዘመን ነው ።
     2- ከ33 ዓ.ም. እስከ 476 ዓ.ም ። ይህ ጊዜ ከጌታችን ሞትና ትንሣኤ የሮም መንግሥት እስከ ወደቀበት ያለውን የሚከልል ነው ። ከሰሜን አውሮፓ የፈለሱ አረመኔዎች የሮምን መንግሥት የጣሉበት “የሮም አወዳደቅ” ተብሎ የተጠራበት ዘመን ነው ። ይህ ዘመን የሮማና የግሪኮች የዘመናት አገዛዝ ስፍራ የለቀቀበት በመሆኑ ለጥንቷ ቤተ ክርስቲያን እንደ መክፈያ ያዩታል ። እንግዲህ ምዕራባውያን የጥንቷን ቤተ ክርስቲያን ዘመን በሁለት እይታ እንደሚያዩት ልብ በሉ ።
ማስታወሻ፡- ዓለምን ይገዛ የነበረው የቄሣሩ መንግሥት ፣ የሮሙ ኃያል ለዚህ ዓለም አቀፍ ግዛቱ የሰጠው ስያሜ “ፓክሳ ሮማና” የሚል ነው ። ትርጉሙም፡- “ሮም ለዓለም ያመጣችው ሰላም” የሚል ነው ። ይህ ከአምስት መቶ ዓመታት በላይ የሰለጠነው የሮማ ግዛት በመስከረም 4 / 476 ዓ.ም. በድንገት ፈራረሰ ። ይህ የታፈረና የተፈራ መንግሥት እዚህ ግባ በማይባሉ ወራሪዎች ፈርሷል ። ምክንያቱ ምን እንደሆነ ቢጠና በዋናነት የሮማ መንግሥት ውስጥ ሥር የሰደደው የሞራል ውድቀት ነው ። ከዚያ ጊዜ አንሥቶ ለግለሰቦች ፣ ለማኅበራትና ለአገር ውድቀት ማሳያ ጥቅስ የሆነው “የሮም አወዳደቅ” የሚል ነው ።
በሁሉም አከፋፈል ውስጥ የጥንቷ ቤተ ቤተ ክርስቲያን በውስጡ ሦስት ዘመኖች አሉት፡-
1-  ዘመነ ሐዋርያት
2-  ዘመነ ሰማዕታት
3-  ዘመነ አበው
ዘመነ ሐዋርያት
ይህም ከ33-100 ዓ.ም ያለውን ጊዜ የሚከልል ነው ። የመጨረሻው ሐዋርያ ወንጌላዊው ዮሐንስ ዕረፍት በ97 ዓ.ም ገደማ ነውና ይህ ዘመን ዘመነ ሐዋርያት ይባላል ።
ዘመነ ሰማዕታት
ከ100 – 313 ዓ.ም ያለው ጊዜ ነው ። 313 ዓ.ም. ቆስጠንጢኖስ የሃይማኖት ነጻነት ያወጀበት ዘመን ነው ።
ዘመነ አበው
ከ313-451 ዓ.ም ያለው ነው ። ይህ ዘመን ታላላቅ አባቶች የተነሡበት  በፍልስፍና ፣ በሕግ ፣ በተፈጥሮ ሳይንስ ፣ በመጽሐፍ ቅዱስ እውቀት ፣ በንግግር ችሎታ በጣም የመጠቁ መምህራን የተነሡበት ዘመን ነው ።
የመካከለኛው ዘመን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ
 የምዕራባውያን አከፋፈል ከ590-1517 ዓ.ም ያለው ነው ። ይህም ታላቁ ጎርጎርዮስ ጳጳስ ከሆነበት ፕሮቴስታንት እስከ ተነሡበት ጊዜ ነው ። የሌሎች አከፋፈል ከ313-1453 ዓ.ም. ድረስ ያለው ነው ። ይህም ቆስጠንጢኖስ የሃይማኖት ነጻነት ካወጀበት እስከ ቊስጥንጥንያ በቱርኮች መውደቅ ያለውን ጊዜ የሚከልል ነው ይላሉ ።
ማስታወሻ- ቊስጥንጥንያ ዛሬ ቱርክ ተብላ የምትጠራዋ ናት ። ትልቅ የሃይማኖት መዲና ነበረች ። የሮማ መንግሥት ዓለምን በሚያስተዳድርበት ዘመን ሁለተኛዋ መናገሻ ከተማ ነበረች ። ቁስጥንጥንያ የቢዛንታየን ነገሥታት የነበሩባት የሮም መንግሥት መናገሻ ያደረጋት በመጨረሻ በቱርኮች በመወረር የሃይማኖት ደብዛዋ የጠፋች አገር ናት ። ቢዛንታየን መንደር ሲሆን የነገሥታት ዘር የሚወጡበት ስፍራ ስለነበር የቢዛንታየን ነገሥታት በሚል ሲጠራ ኑሯል ።
በቊስጥንጥንያ የነበረው በስድስተኛው ክፍለ ዘመን በቅድስት ሶፊያ ሃጊያ የተሠራ ትልቅ ቤተ ክርስቲያን የእስላም መስጊድ በመሆን እስከ 1935 ዓ.ም. ቢቆይም ከዚህ ጊዜ በኋላ ግን ሙዝየም ሁኗል ። ክርስትና በዚህ ቦታ ላይ ክፉኛ የተጎዳበት ስለሆነ በ1453 ዓ.ም የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ሁለተኛው የዘመን ምዕራፍ ሊሆን ችሏል ። 476-1453 ዓ.ም. ያለው የመካከለኛው ዘመን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ የጨለማው ዘመን በማለት ይጠሩታል ። ይህ ዘመን የሮማ መንግሥት የወደቀበት ፣ ሁከት የበዛበት ፣ ቤተ ክርስቲያን የተከፋፈለችበት ዘመን በመሆኑ የጨለማ ዘመን የሚል ስያሜ ሊያገኝ ችሏል።
ማስታወሻ፡- ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በ1957 ዓ.ም. ከእንግሊዟ ንግሥት ከኤልሳቤጥ ጋር ሁነው የመረቁት የአክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን የተሠራው በሃጊያ ሶፊያ ቤተ ክርስቲያን ቅርጽ ነው ። የቅድስት ሶፊያ ቤተ ክርስቲያን በስድስተኛው ክፍለ ዘመን በንጉሥ ዮስጢንያኖስ የተሠራ ነው ።
የኋለኛው/ አዲሱ/ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ
ከ16ኛው ክፍለ ዘመን እስካለንበት ዘመን ድረስ ያለውን የሚጠቀልል ነው ። ይህም ዘመን ቤተ ክርስቲያን ከሦስት ወደ አራት የተከፈለችበት ዘመን ነው ። ከዚያ በኋላ ግን ቊጥር ወደሌለው የፕሮቴስታንት መከፋፈል ፣ ልክ የሌላቸው አብያተ ክርስቲያናት ፣ ዶክትሪኖችና ዶግማዎች የተነሡበት ነው ።
ይቀጥላል
አንብቡ ፣ አንብቡ ፣ አንብቡ ኧረ እባካችሁ አንብቡ !!!
ዲአመ 
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም