መግቢያ » ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ/4

የትምህርቱ ርዕስ | የቤተ ክርስቲያን ታሪክ/4

የቤተ ክርስቲያን ስያሜ
ቤተ ክርስቲያን ተብሎ በግእዝ የተተረጎመው ቃል በግሪኩ “አቅሌስያ” ይባላል ። አቅሌስያ ማለት “የተጠሩና የተመረጡ የመፍትሔ አፈላላጊዎች ሸንጎ” ማለት ነው ። የጥንት ግሪካውያን በአገር ፣ በመንደሩ አንድ ችግር ሲከሰት ያንን ለመፍታት የተጠሩና የተመረጡ ሰዎች ስብስብ “አቅሌስያ” በማለት ይጠሩት ነበር ። “አቅሌስያ” መንፈሳዊ ትርጉሙን ሲያገኝም ኅሩያነ እግዚአብሔርን ወይም የእግዚአብሔር ምርጦችን ለመግለጥ ውሏል ። ቤተ ክርስቲያን የሚለው ቃል መሠረቱ አቅሌስያ ከሆነ ለአቅሌስያም እንደ መነሻ የሚሆነው የዕብራይስጡ “ኤዳህ” እና “ካሃል” የሚሉት ስያሜ ናቸው ። “ኤዳህ” የሚለው ስያሜ ጥቅም ላይ የዋለው እግዚአብሔርን ለማምለክ የተሰበሰበን ሕዝብ ለመግለጽ ነው ። “ካሃል” የሚለው በብሉይ ኪዳን 123 ጊዜ በላይ የተጠቀሰ ሲሆን ጉባዔ /ማኅበር/ በሚል ትርጉም ይታወቃል ። “ካሃል” ሃይማኖታዊ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ለተፈለገ ዓላማ የተሰበሰበን ሕዝብ ለመግለጥ ተጠቅመውበታል ። 

ከክርስቶስ ልደት በፊት በ284 ዓመት ብሉይ ኪዳን ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሌላ ቋንቋ ተተረጎመ ። የተረጎሙትም በእስክንድርያ የተገኙት ሰባ የአይሁድ ሊቃውንት ናቸው ። የእነርሱም ትርጉም የሰባ ሊቃናት ትርጉም ተብሎ ይጠራል ። እነርሱም “ካሃል” የሚል ሲያገኙ አቅሌስያ በማለት ተርጉመውታል ። “አቅሌስያ” ከሁለት ጥምር ቃላት የተገኘ ግሪክኛ ሲሆን “ኤክ” እና ካልዮ ከሚሉት ቃላት በመውጣት ሲሰየም “ኤክ” ማለት የወጡ ሲሆን “ካልዮ” ደግሞ የተጠሩ ማለት ነው ። በአንድነትም ስናነብ ተጠርተው የወጡ ምርጦች ማለት ነው ። “አቅሌስያ” የሚለው የግሪክ ቃል በአዲስ ኪዳን 113 ጊዜ በላይ የተጻፈ ሲሆን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትም ሁለት ጊዜ ብቻ ተጠቅሷል ። ማቴ. 16፡16 ፤ 18፡19 ። ማኅበር በማለት የተጠቀሱት ሁሉ “አቅሌስያ” ተብለው እንደተተረጎሙ በደንብ ማየት ይቻላል ።
“ቤተ ክርስቲያን” ተብሎ ወደ ግእዝ የተተረጎመው አቅሌስያን የተካ ቃል ነው ። ቤተ ክርስቲያን ተብሎ ሲጠራም ሦስት ነገሮችን አመልካች ነው፡-
1-  ወገንን አመልካች ነው ። ቤተ እስራኤል ማለት የእስራኤል ወገን ፣ ቤተ አሮን ማለት የአሮን ወገን ማለት እንደሆነ ቤተ ክርስቲያን ማለትም የክርስቲያን ወገን ፣ የክርስቶስ ወገን ፣ ዘክርስቶስ እንደማለት ነው ። ይህም የተስፋውና የመንግሥቱ ወራሾች የሆኑትን ምእመናን የሚገልጥ ነው ። ክርስቲያን የሚለው ስያሜ የወጣው ለመጀመሪያ ጊዜ በአንጾኪያ ነው ። ክርስቲያን ማለትም የክርስቶስ ተከታይ ፣ የክርስቶስ ወገን ፣ በመንፈስ ቅዱስ የከበረ ፣ መሢሓዊ ፣ ክርስቶሳዊ ፣ ዘክርስቶስ ማለት ነው። ቅዱስ አውስጢኖስ፡- “ክርስቲያን ማለት ሌላው ክርስቶስ ማለት ነው” ያለው ለዚህ ነው ።
2-  የክርስቲያኖች ስብስብ ቤተ ክርስቲያን በመባል ተጠርቷል ። ከእናንተ ጋር ተመርጣ በባቢሎን ያለች ቤተ ክርስቲያን ልጄም ማርቆስ ሰላምታ ያቀርቡላችኋል።” 1ጴጥ. 5፡13 ። ሰላምታ የምታቀርበዋ ቤተ ክርስቲያን በባቢሎን ያለች ማኅበረ ምእመናን ናት ። በዚህም መሠረት ቤተ ክርስቲያን ዘኤፌሶን ፣ ቤተ ክርስቲያን ዘሎዶቅያ ፣ ቤተ ክርስቲያን ዘኢትዮጵያ ይባላል ።
3-  መሰብሰቢያ ቦታን አመልካች ነው ። “ቤተ ክርስቲያን እንሂድ” እንዲሉ ። ምእመናን የሚሰባሰቡባት ፣ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን የሚቀበሉበት ቦታ “ቤተ ክርስቲያን” ተብላ ትጠራለች ። በእንግሊዝኛው “ቸርች” የሚለው ቃል የተወሰደው ከላቲን ሲሆን ትርጉሙም “የጌታ ሀብት” ማለት ነው ። ይህም ቤተ ክርስቲያን የሰው አለመሆኗን ለመግለጥ የዋለ ቃል ነው ።
የቤተ ክርስቲያን ባሕርይዋ
ባሕርይ አይቀየርም ፣ ጠባይ ግን ይቀየራል ። ቤተ ክርስቲያን የማይቀየሩ አራት ባሕርያት አሏት ። ጸሎተ ሃይማኖት ብለን የምንጠራው የሁለቱ ታላላቅ ጉባዔያት ማለትም የኒቅያ /325 ዓ.ም/ እና የቊስጥንጥንያ /381 ዓ.ም/ ጉባዔ መግለጫ ነው ። “ወነአምን በመንፈስ ቅዱስ እግዚእ ማኅየዊ ዘሠረጸ እምአብ” ከሚለው ጀምሮ ያለው የቊስጥንጥንያ ጉባዔ መግለጫ ነው ። የቊስጥንጥንያ ጉባዔ መግለጫም የቤተ ክርስቲያንን ባሕርይ የሚገልጹ ውሳኔዎችን አስተላልፏል ። “ወነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላዕለ ኩሉ ጉባዔ ዘሐዋርያት” ማለትም “በአንዲት ፣ ቅድስትና በሁሉ ባለች ሐዋርያት በሰበሰቧት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን” የሚል ነው ። በዚህ መሠረት ቤተ ክርስቲያን አራት መገለጫዎች አሏት እንላለን፡-
1-  አንዲት፡- ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት ። አንድ ራስ ብዙ አካሎች የሉትምና የቤተ ክርስቲያን ራስ የሆነው አንዱ ክርስቶስ አንዲት ቤተ ክርስቲያን አለችው ። የኒቅያ ጉባዔ የቤተ ክርስቲያን አንድነት የታየበት ጉባዔ ስለነበር ዓለምና ነገሥታት አክብረውታል ። የኬልቄዶን ጉባዔ ደግሞ ቤተ ክርስቲያን የተለያየችበት ስለነበር ዓለም ንቀቱን ፣ ነገሥታቱ እነመርቅያል ድፍረታቸውን ያሳዩበት ኋላም ለመሐመዳውያን በር የከፈተ ሁኗል ። የኒቅያ ጉባዔ በዓለም ላይ አራት መንበሮችን ሰይሞ የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ለማጽናት ጥሯል ። ለምዕራቡ የሮምን ፣ ለሰሜን ኤፌሶንን ፣ ለምሥራቁ አንጾኪያን ፣ ለደቡቡ እስክንድርያን ሰይሟል ። በእነዚህ አቅራቢያ ያሉ በሚቀርባቸው መንበሩ ሥር በመሆን አንዲቷን ቤተ ክርስቲያን ይጠብቃሉ ።
 
2-  ቅድስት፡- የቅዱሱ የክርስቶስ አካል ናትና ቅድስት ናት ። ወደ እርስዋ የሚመጡ ታሪካቸውና ስማቸው ይለወጣልና ቅድስት ናት ።ከዓለም ስለመለየትና ክርስቶስን ስለመምሰል ታስተምራለችና ቅድስት ናት ።
3-  ዓለም አቀፋዊት /ኩላዊት/ ፡- ወደ ምዕራቡ የሄደችው ቤተ ክርስቲያን ራሷን “ካቶሊክ” ማለቷ የሁሉም ነኝ ለማለት ብቻ ሳይሆን ኩላዊት ነኝ በሁሉ ያለሁ ነኝ ለማለትም ነው ። “እንተ ላዕለ ኩሉ” የሚለው ስያሜ ግን የአንዲቱ ቤተ ክርስቲያን መጠሪያ ነው ። ቤተ ክርስቲያን በሁሉና ለሁሉ ያለች ናት ። የዘር ፣ የቀለም ፣ የቋንቋ ግርዶሽ የለባትም ።
4-  ሐዋርያዊት፡- በሐዋርያት ትምህርት ላይ የተመሠረተች ፣ በተመሠረተው ላይ የተካበች ፣ ዘላለማዊነትን እንጂ ዘመናዊነትን ያልተከተለች ናት ። ከጌታችን ለሐዋርያት ፣ ከሐዋርያት ለሊቃውንት ሲተላለፍ የኖረው የአንብሮተ ዕድ ወይም እጅ የመጫን ሰንሰለታማ ጉዞ ያለባት ናት ። ዛሬ የምናየው አንድ ሊቀ ጳጳስ በአንብሮተ ዕድ ቅብብሎሹ ከቅዱስ ጴጥሮስ ጋር ይገናኛል ። ከዚያም ከጌታ ጋር ይገናኛል ። ቤተ ክርስቲያን የወንጌል ስብከቷ ፣ የክህነት ቅብብሎሽዋ ያልተቋረጠ ሲሆን ብቻ ሐዋርያዊት ትባላለች።
ይቀጥላል
አንብቡ ፣ አንብቡ ፣ አንብቡ ኧረ እባካችሁ አንብቡ !!!
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም