መግቢያ » ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ » የቤተ ክርስቲያን ታሪክ/7

የትምህርቱ ርዕስ | የቤተ ክርስቲያን ታሪክ/7

አሥራ ሁለቱ ሐዋርያት
ደቀ መዝሙር የተማሪነት ስም ሲሆን ሐዋርያ ደግሞ የተልእኮ ስም ነው ። ደቀ መዝሙር አዳሪ ተማሪ ፣ የመምህሩን ሕይወትና እውቀት የሚካፈል ፣ እንደ ልጅ የሚያገለግል ፣ እንደ ሕፃን የሚጠይቅ ፣ “ተናገር በከንፈሬ ፣ ተቀመጥ በወንበሬ” ተብሎ የሚሾም ፣ ተተኪ ፣ እጩ መምህር ፣ ከመምህሬ በፊት ያድርገኝ ብሎ የሚዋጋ ወታደር ፣ የእገሌ ተማሪ ነኝ ብሎ የእውቀት አባቱን ስም የሚያስጠራ ፣ በመከራና በጭንቅ ጎዳና ነፍሱን የሚያጠግብ ፣ የዲያቆን የጳጳስ መነሻ ማለት ነው ። ሐዋርያ የሚለው ቃል ደግሞ ሒያጅ ፣ መንገደኛ ፣ ገስጋሽ ፣ መልእክተኛ ማለት ነው ። በምሥጢራዊ ትርጉሙ ደግሞ የክርስቶስ አፍ ፣ ባለ አደራ ፣ ባለሥልጣን ፣ ክርስቶስን በዓይኑ አይቶ በጆሮው ሰምቶ ሊመሰክርለት የወጣ ማለት ነው ። እስራኤል በ12 የነገድ አለቆች እንደ ተመሠረተች ቤተ ክርስቲያንም በአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ተመሥርታለች ።

አሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ዝርዝራቸው በአራት ስፍራ ላይ ተቀምጦል ። /ማቴ. 10፡2-4 ፤ ማር.3፡16-19፤ ሉቃ. 6፡13-16 ፤ የሐዋ. 1፡13/ ። አሥራ ሁለቱ ሐዋርያት አብዛኛዎቹ የተጠሩት ከገሊላ አውራጃ ነው ። የተጠሩበት ነገድም ጴጥሮስና እንድርያስ በአባታቸው ከነገደ ሮቤል በእናታቸው ከነገደ ስምዖን ናቸው ። ያዕቆብና ዮሐንስም በአባታቸው ከነገደ ይሁዳ በእናታቸው ከነገደ ሌዊ ናቸው ። ፊልጶስ ከነገደ ዛብሎን ፣ በርተሎሜዎስ ከነገደ ንፍታሌም ፣ ቶማስ ከነገደ አሴር ፣ ማቴዎስ ከነገደ ይሳኮር ፣ ያዕቆብ ወልደ እልፍዮስ ከነገደ ጋድ ፣ ስምዖን ቀነናዊ ወይም ናትናኤል ከነገደ ብንያም ፣ ታዴዎስ የተባለው ልብድዮስ ከነገደ ዮሴፍ ፣ በይሁዳ ምትክ የገባው ማትያስ ከነገደ ዳን ናቸው ። የአስቆሮቱ ይሁዳም ከነገደ ዳን ነበር።
በዚህ አገላለጽ መሠረት አሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ከአሥራ ሁለቱ ነገደ እስራኤል ተጠርተዋል ። ተደራራቢ ስም ያላቸው አሉ ። ይህም በአይሁዳውያን የተለመደ ነው ። አይሁዳውያን ብዙ አገዛዞችን ስላስተናገዱና በብዙ አገሮች ተበትነው ስለኖሩ አንዱን ሰው በዕብራይስጥና በግሪክ ስም መሰየም የተለመደ ነው ። ለምሳሌ፡-
1-  ጴጥሮስ፡- ስምዖን ኬፋ ይባላል ። ስምዖን ወላጆቹ ያወጡለት ሲሆን ከነገደ ስምዖን ስለተወለደ የወጣለት ስም ይመስላል ። ጴጥሮስና ኬፋ ተመሳሳይ ትርጉም ሲኖራቸው ጴጥሮስ በግሪኩ ፣ ኬፋ በአራማይክ ሲሆን ትርጉሙ ዓለት ማለት ነው ። ይህን ስም ያወጣለት ጌታችን ነው ።

2-  ዲዲሞስ ወይም ቶማስ ። ቶማስ በአራማይክ ሲሆን ዲዲሞስ በግሪክ ነው ። የሁለቱም ትርጉም መንታ ማለት ነው ።

3-  ማቴዎስ፡- ሌዊ የሚል ስም አለው ። ቀራጩ የሚል የስም ቅጥያም አለው ። ማቴዎስ መጠሪያው ሲሆን ሌዊ የቤተሰብ ስም ነው ።
ሐዋርያት የተለያየ ስያሜ አግኝተዋል ። “የምሥጢር ደቀ መዛሙርት” የሚባሉ ጴጥሮስ ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ ናቸው ። ማር. 5፡37 ፤ ሉቃ. 8፡51 ፤ ማቴ. 17፡1 ። “አእማድ” ወይም ምሰሶዎች ተብለው እነዚህ ሦስት ደቀ መዛሙርት ተጠርተዋል ። /ገላ. 2፡9 /። ደቀ መዛሙርቱ የአብዛኛዎቹ ሙያ ተመሳሳይ ነው ። ጴጥሮስና እንድርያስ ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ ፣ ፊልጶስና ናትናኤል ዓሣ አጥማጅ ሲሆኑ ፤ ትንሹ ያዕቆብና ይሁዳ እንጨት ጠራቢ ናቸው ። ማቴዎስ ቀራጭ ነው ። በሐዋርያት ወንድማማቾች የሆኑ ሦስት ጥንዶች አሉ፡- ጴጥሮስና እንድርያስ ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ ፣ ትንሹ ያዕቆብና ይሁዳ ናቸው ። ይሁዳ ያልነው ጌታን የሸጠው አይደለም ።
በአዲስ ኪዳን በብዛት ስሙ የተጠቀሰው ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ሲሆን በፈጣንነቱና በተቀበለው አደራ እንደ ሊቀ ሐዋርያት ይታያል ። ከሐዋርያትም በቶሎ የሞተው ትልቁ ያዕቆብ ወይም የዘብዴዎስ ልጅ ነው ።በሄሮድስ አግሪጳ ዘመን በ44 ዓ.ም. ነው ። /የሐዋ. 12፡2 /። ሁሉም ሐዋርያት ዓለምን በዕጣ ተከፋፍለው ወንጌልን ሰብከዋል ። በሰማዕትነትም ተጋድሎአቸውን ፈጽመዋል ። ቅዱስ ጴጥሮስ በ67 ዓ.ም. በሮም የቁልቁሊት ተሰቅሎ ተጋድሎውን ፈጽሞአል ። ይህም ሐምሌ አምስት ቀን ይታሰባል ። ቅዱስ ጳውሎስም በዚሁ ቀን ከጴጥሮስ ጋር የሞተ ሲሆን አሟሟቱም አንገቱን በሰይፍ ተቀልቶ ነው ። ጴጥሮስ በቫቲካን ኮረብታ ፣ ጳውሎስ በኦስቲያ መንገድ መቀበራቸውን በሁለተኛው ክፍለ ዘመን የነበረው ጋይዮስ መስክሯል ። እንድርያስ በፍልስጤም ፣ በእስኪስያ ፣ በስራኪ ፣ በመቄዶንያ ፣ በትንሽዋ እስያ ፣ በግሪክ አስተምሮ የቊስጥንጥንያን ቤተ ክርስቲያን መሠረተ ። ፓትራ በምትባል አገር ሲያስተምር በመስቀል ላይ ተሰቅሎ በደንጊያ ተወግሮ ሞቷል ። የራስ ቅሉም በ1208 ዓ.ም. በመስቀል ጦረኞች ወደ ሮም ተወስዶ የነበረ ሲሆን በ1964 ዓ.ም ለግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተመልሷል ። ቶማስ በፋርስ በህንድ አስተማረ ። ማቴዎስ በፍልስጤም ፣ በኢትዮጵያና በፋርስ እንዲሁም በመቄዶንያ አስተማረ ። ፊልጶስ በትንሽ እስያ በፍርግያ አስተማረ ። በርተሎሜዎስ በሕንድና በአርመን አስተማረ ። ናትናኤል በመስጴጦምያ ፣ በግብጽ ፣ በሰሜን አፍሪካ ሰበከ ። ትንሹ ያዕቆብ ወይም ወልደ እልፍዮስ በፋርስና በግብጽ አስተማረ ። ማትያስ በግብጽ ፣ በቀጰዶቅያ ፣ በኑብያ ሰበከ ።
ይቀጥላል
አንብቡ ፣ አንብቡ ፣ አንብቡ ፣ ኧረ እባካችሁ አንብቡ !!!
ዲአመ 
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም