የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

የተረፈ ሰው ምስጋና

እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ 2016 ዓ.ም. ወደ ዘመነ ማቴዎስ 2017 ዓ.ም. በሰላምና በጤና አሸጋገራችሁ!

“ኖኅም ለእግዚአብሔር መሠውያውን ሠራ፥ ከንጹሕም እንስሳ ሁሉ ከንጹሐን ወፎችም ሁሉ ወሰደ፥ በመሠውያውም ላይ መሥዋዕትን አቀረበ።” (ዘፍ. 8 ፡ 20 ) ።

ዛሬ ላይ ያለው መላው የዓለም ሕዝብ ተደምስሶ ፣ እንስሳቱ ከዝርያ በቀር ሁሉም አልቀው ፣ እጽዋቱ ተጎሳቁለው የእኛ ቤተሰብ ብቻውን ቢተርፍ ፣ የቤተሰቡም ብዛት ስምንት ብቻ ቢሆን ምን ይሰማናል ? ኖኅ የገጠመው ስሜት እንዲህ ያለ ነበር ። የቅርብ ዘመዶቹ ፣ ጎረቤቶቹ ፣ የአገር ልጆች ፣ የዓለም ሕዝቦች የሉም ። ያለው ፣ የተረፈው ቤተሰብ የእርሱ ብቻ ነው ። ያለው የተረፈው የአገር ዜጋ የእርሱ ቤተሰብ ብቻ ነው ። ያለው የተረፈው የዓለም ሕዝብ የእርሱ ቤተሰብ ብቻ ነው ። ይህም ቤተሰብ የተረፈው በብልሃት ሳይሆን በእምነት ነው ። በብልጠት ሳይሆን በመታዘዝ ነው ። በማልመጥ ሳይሆን በደስታ ለእግዚአብሔር በመገዛት ነው ። በከተማው ላይ ይሰማ የነበረው የየቀኑ ጭፈራ ዛሬ የለም ። ጨፋሪዎቹም ፣ የጭፈራ ቦታዎቹም የሉም ። የትልልቅ ሰው ቤቶች ፣ ለመግባት ፈቃድ የሚጠየቅባቸው የተቀጠሩ ሰፈሮች ዛሬ የሉም ። እነዚያ የጌቶች ዘበኞች ራሳቸውንም አዛዦቻቸውንም ማትረፍ አልቻሉም ። እልቂቱ ከቃል በላይ ነው ። እልቂቱ የምጽአት ያህል ነው ። መትረፉም ከዚህ በላይ ያስደንቃል ። ኖኅ ሰባኪም ነበርና አስቀድሞ የንስሐ ስብከት አሰማ ፤ ሁሉም የሰውን መደሰት የማይወድ ምቀኛ አድርገው ሳሉት ። የተቃወሙት ግን ዛሬ የሉም ። ያሸነፉ የመሰላቸው ለዘላለም ተሸንፈዋል ። አርደው የሚበሉ ፣ ገድለው የሚዘርፉ እንኳን መኖሪያቸው የቀብር ስፍራቸው አልታወቀም ።

ከብዙ ስደትና ስጋት ውስጥ ተርፈው የሚመጡ ወገኖቻችን ገና ከአውሮፕላን ሲወርዱ በጉልበታቸው ወድቀው መሬቱን ይስማሉ ። ኖኅ ከመርከብ ሲወርድ ምን ተሰምቶት ይሆን ? እግዚአብሔርን ካላሰበ በቀር መጽናናት አይችልም ። ከወራት በፊት የነበረው ያ ሁሉ ጫጫታ ዘላለማዊ ጸጥታ ወርሮታል ። የሚያጋፉ መንገዶች ዛሬ ጭር ብለዋል ። መላው ዓለም በስምንት ቤተሰብ እጅ ወድቋል ። የሚገርመው ከዚህ መዓት ተርፎ ኖኅ በስካር ወደቀ ። የሚገርመው ጥቂት ሳሉ ካም አባቱን ለማዋረድ ተነሣሣ ። አይቶ እንዳላየ መኖር ከባድ ነው ። ያለፈው መከራ ፣ የደረሰው እልቂት ከመናገር በላይ ነው ። ከዚህ የተረፈ ይመንናል ፣ በጽድቅ ይኖራል እንጂ ይበድላል ተብሎ አይታሰብም ። ሰው ግን ከባድ ነው!

ኖኅ የእግዚአብሔርን ማዳን አየ ። ዳግማዊ አዳም ሁኖ በእርሱ ቤተሰብ የዓለም ሕዝብ እንደገና ጉዞ ሊጀምር ነው ። በእነዚያ ቀናት በመርከብ ውስጥ ሁኖ ከመርከቡ ውጭ ያለ ወገን ሲያልቅ እያየ ነው ። መርከቡን ለመያዝ ሲሞክሩ እየራቃቸው ያለቁት ሕዝቦች በዓይኑ ላይ አሉ ። በመርከቡ ውስጥ ዛሬ የምንፈራቸው አራዊት ሁሉ ነበሩ ። እያንዳንዱ ቀን የሺህ ዓመት ያህል ረጅም ነበረ ። ኖኅ ግን ልቡን በእግዚአብሔር አበረታ ። በዚያች መርከብ ካፒቴን ፣ አባወራ ፣ ካህን ፣ ንጉሥ ነበረ ። መርከብ ሁሉ መድረሻ ቦታ አለው ፣ የኖኅ መርከብ ግን ተጓዥ ሳትሆን ለማዳን ብቻ የምትንሳፈፍ ናት ። በመርከቡ ውስጥ ሕይወት አለ ፣ ከመርከቡ ውጭ ግን ሞት ነበረ። ሰማይ ጠቀስ ፎቅ የሠሩም አልተረፉም ። ዛሬ ላይ የሚረዳው የኖኅ እምነት ብቻ ነው ። ይህች መርከብ የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት ። “ከቤተ ክርስቲያን ውጭ ድኅነት የለም ።” “ቤተ ክርስቲያን እናት ያልሆነችው እግዚአብሔር አባቱ አይደለም” የሚባለው ጽኑ ምሥጢር ነው ። ኖኅ ከመርከቡ ሲወርድ ሬሳ ለመቍጠር ፣ ቤት መሥሪያ መሬት ለማስተካከል አልቸኮለም ። የወደመው የእርሱም የዘመናት ሀብት ነው ። ሕይወቱን አትርፏልና ለንብረት አልተጨነቀም ። ኖኅ ግን ለእግዚአብሔር የምስጋና መሥዋዕት ለማቅረብ መሠዊያ ሠራ ። ለንጹሑ እግዚአብሔር ንጹሕ መሥዋዕት ለማቅረብ ተጋ ።

ከብዙ ሞት አምልጠን ፣ ከማይታየው ስውር መጥመድ ተጋርደን ፣ ከሚንበለበለው ፍላጻ ተሰውረን ዛሬን ያየን ነን ። ይህች ቀን ኖኅ የሚታሰብባት ፣ ከመርከብ የወረደባት ቀን ናት ። ያለፈው ጊዜ አይደገም የሚባል ብዙ ሰቆቃ የታየበት ፣ ወገን እንደ ቅጠል የረገፈበት ፣ ራብ ቤተኛ ሁኖ አልወጣም ያለበት ፣ ወንድም በወንድሙ የጨከነበት ነው ። ብዙዎች አልፈው እኛ ተርፈናል ። ብዙዎች አልቀው እኛ ቆመናል ። ለእግዚአብሔር ንጹሕ መሥዋዕትን ልናቀርብ ይገባል ።

መርገጫ በታጣበት ፣ እናት የልጇን ጩኸት በማትሰማበት ፣ አንዱ አንዱን እንዳይረዳው ሁሉ በተቸገረበት ዘመን የምታሻግር የኖኅ አምላክ ስለዚህ ቀን ፣ ስለዚህ አዲስ ዘመን እናመሰግንሃለን ። ከብዙ ጥፋት ያመለጥን ነንና እናከብርህ ዘንድ እርዳን ! እነዚያ ለምን ሞቱ ? ሳይሆን እኛ ለምን ኖርን ? ብለን እንድንጠይቅ እርዳን ! ለሞቱት ዕረፍት ፣ ለእኛም ኅብረት ስጠን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መስከረም 1 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ