መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የነቢያት ጉባዔ » የነቢያት ጉባዔ ክፍል 7

የትምህርቱ ርዕስ | የነቢያት ጉባዔ ክፍል 7

ነቢዩ ሙሴ፡- “የሰማዩ ሰማይ እግዚአብሔር ነው ፣ ሀገረ ሕይወት ፣ መንግሥተ ሰማያትም እርሱ ነው ።” በሚል ምስጋና ተሞላና ስለ አገልጋዮች መናገሩን ቀጠለ ። ዮሐንስ መጥምቅም በታላቅ ትሕትና ይሰማው ነበርና ወደ እርሱ አትኵሮ መናገሩ ጀመረ፡-

“እግዚአብሔር ያለፉት ለቆሙት እንዲናገሩ አድርጎ ሕይወትን አዋቅሯል ። እርሱ ትላንት ያላመለጠው ፣ ዛሬ ያልካደው ፣ ነገም ከእጁ የማይወጣ ሕይወተ ባሕርይ አምላክ ነው ። ቅዱሳን በኑሮአቸው በቃል ፣ በሞታቸው በዝምታ ሲናገሩ ይኖራሉ ። እኔ እግዚአብሔርን የተከተልሁት ስለ ከነዓን አልነበረም ። ከነዓንን የፈጠረውን ይዤ ስለ ተፈጠረ ነገር እንዴት አገለግላለሁ ? የተመኘሁት ቢቀርም እግዚአብሔርን ግን አላጣሁም ። ሰው አጣሁ ነጣሁ ማለት ያለበት እግዚአብሔርን ሲከስር ብቻ ነው ። እግዚአብሔር ኪሣራ የሌለው ትርፍ ፣ የማያረጅ ዘመድ ነው ። በተራራው ላይ ሆኜ ከነዓንን ተሳለምኋት ። በዚያም መላእክት አፈር አልብሰውኝ አንቀላፋሁ ። ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ እንዲኖርና እንዲያገለግል የተጠራው ከሞትሁበት ተራራ ፊት ለፊት ባለ ሸለቆ ውስጥ ነው ። ማን ይቀብረኛል ? ብቻዬን ነኝ እንዳይል አፈር አልባሽም ፣ ታሪክ ቀያሽም ፣ ሞትን የሚበቀል ልጅም እግዚአብሔር መሆኑን ሊያስተምረው ነው ። ወላጆቹ ከሄሮድስ ሰይፍ ሊጋርዱት በምድረ በዳ ይዘውት ሸሹ ። እነርሱ ሞቱ ፣ ዮሐንስ ግን አደገ ። አራስ ልጅም በእግዚአብሔር እንደሚያድግ ዮሐንስ መጥምቅ ምስክር ነው ፣ እግዚአብሔር እንደሚቀብርም እኔ ምስክር ነኝ ። እናንተ አገልጋዮች ከፍርሃት ዳኑ ። ምድራዊ መንግሥት እንኳ በጀት አለው ። እግዚአብሔርም ለመንግሥቱ በጀት አለው ። ያለ ከረጢትና ያለ ኮሮጆ ልኮ የማያጎድል አምላክ ነው ።

ኤልያስ ነቢይም ድንገት ብድግ አለና፡- “እግዚአብሔር የሕያዋንና የሙታን ጌታ መሆኑን ሊያስተምር አንተ እንድትሞት ፣ እኔ ወደ ብሔረ ሕያዋን እንድነጠቅ አደረገ ። በደብረ ታቦርም ሞቱን ለማስተማር አንተን ፣ ትንሣኤውን ለማስተማር እኔን አመጣ ። የዘመናት ርቀት ቢኖርም አለመተዋወቅ አልገጠመንም ። የአንድ አባት ልጆች የትም አገርና ዘመን ቢኖሩ ይተዋወቃሉ ። መተዋወቅ መተሳሰብ እንጂ መተያየት አይደለምና ።” የኤልያስን ቃል ሙሴ ነጠቀ ፣ የነቢያት ጉባዔ ነውና ምክሩ ፈለቀ፡-

“የእግዚአብሔር አገልጋዮች ሆይ ! የጣለው በረዶ ጣራችሁን እንዳይነድለው ፣ የመጣው ጎርፍ መሠረታችሁን እንዳይፈነቅለው ቃሉን ሰምቶ ማድረግ ይሁንላችሁ ። የቃሉ የጆሮ ደምበኞች ቃሉን ይሰማሉ ፣ ለጊዜው ተመስጠው ስሜታቸው ሲበርድ ይረሱታል ። ቃሉን ሰምተው የሚያደርጉ ክርስቶስን ጌታ ፣ ሰማይን ዋጋ ያደረጉ ናቸው ። “በአህያ ቆዳ የተሠራ ቤት ጅብ የጮኸ ዕለት ይፈርሳል” እንዲሉ ቃሉን በሕይወታቸው የማያውቁት በፈተናና በመከራ መንገድ ይቀራሉ ። “የእብድ ገላጋይ ድንጋይ ያቀብላል” እንዲሉ እሳትን በውኃ እንጂ እሳትን በእሳት ለማጥፋት አትሞክሩ ። “ከአጋም የተጠጋ ቁልቋል ሲያለቅስ ይኖራልና” እልኸኛ ሕዝብን እንደ እኔ የምታገለግሉ ከሆነ ኑሮአችሁ ልቅሶ ያለበት ነው ። እኔን አንድ ቀን ያላመሰገነኝ ፣ በምድረ በዳ ሲቀማጠልብኝ የነበረ ሕዝብ ስሞት ሠላሳ ቀን አለቀሰልኝ ። ስትኖሩ ርኵስ ፣ ስትሞቱ ቅዱስ ናችሁና አትደነቁ ። እንደው የኢትዮጵያ ምሳሌ ግሩም ነውና፡- “ፀጉራም ውሻ አለ ሲሉት ይሞታል ይላሉ ። እናንተም መዛላችሁን ማንም ሳያውቅላችሁ እንዳትሞቱ ሁልጊዜ ተጠንቀቁ ። ደግሞም “አሽሟጣጭ ዝናብ ወንዝ ዳር ያካፋል” እንዲሉ ቃሉን ጠገብን ካሉ ሰዎች ርቃችሁ የተራበውን አገልግሉ ። የራበው እያለ የሚያቅረውን ለምን ትታገላላችሁ ? “የድሀ ጉልበት በጎመን ዘር ያልቃል” እንዲሉ ጉልበታችሁን በከንቱ አትጨርሱ ! በማገልገላችሁም ውለታ አይሰማችሁ ። ማገልገል መገልገል ነውና !

ይቀጥላል

የነቢያት ጉባዔ/7

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ሚያዝያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም