መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » የአበው ተስፋ ተወለደ

የትምህርቱ ርዕስ | የአበው ተስፋ ተወለደ

አበው መንገዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር አደረጉ ። በጽድቃቸው እንኳን ሌላውን ራሳቸውንም ማዳን ባልቻሉ ጊዜ የክርስቶስን መወለድ ናፈቁ ። አዳም ገነትን አጥቶ ተስፋን ይዞ ወጣ ። ከነበረችው ገነት ይልቅ ፣ የገነት ጌታ የእርሱ ልጅ እንደሚሆን በሰማ ጊዜ ልቡ በደስታ ዘለለ ። ውድቀቱ ያመጣው መዳን ቢሆን ኖሮ እንኳን ወደቅሁ ባለ ነበር ፣ ለወደቀ ሰው የሚሆን ፍቅር ያለው አምላክ ግን አዳምን ከበደሉ በላይ ካሣ ሰጠው ። ተስፋ የሚነገረው/የሚሰጠው በእግዚአብሔር ደግነት ፣ የሚፈጸመውም በእግዚአብሔር ታማኝነት ነው ። አበውም ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚቀባበሉት ዕንቈ ነበራቸው ፤ እርሱም ክርስቶስ ይወለዳል የሚል ነው ። የከፋውና ሁሉ የተነባበረበት ሕፃን “ቆይ አባቴ ይምጣ” እያለ እያለቀሰ ይስቃል ። አባቱ እንባውን ያብስለታል ፣ ጠላቶቹን ያሸንፍለታል ። አበውም የክርስቶስን መወለድ ባሰቡ ጊዜ እያለቀሱ ሳቁ ።

ጨርሶ እንዳይጨልም ለማታው ክፍለ ጊዜ ጨረቃና ከዋክብትን ያስቀመጠ እግዚአብሔር ፣ የሰው ልጅም በኃጢአት ፣ በመቃብርና በሲኦል ተጨንቆ እንዳይኖር ልደተ ክርስቶስን ተስፋ አድርጎ ሰጠ ። አንድ ወንድ ልጅ ይወለዳል እየተባለ ለዘመናት ተስፋ ተደረገ ። ያ ልጅ ከተወለደ በኋላም ዳግም ይመጣል እየተባለ ይሰበካል ። ከገነት እስከ ምጽአት ፣ ከውድቀት እስከ ፍርድ ቀን የክርስቶስ መምጣት የሰው ልጆች ተስፋ ነው ። ይህች ዓለም ያለ ክርስቶስ አድራ አታውቅም ። የመጣውና የሚመጣ ጌታ አለን ። በመጀመሪያ ምጽአቱ አዳነን ፣ በዳግም ምጽአቱ ይፈርድልናል ። በመጀመሪያ ምጽአቱ ከሲኦል ወደ ገነት አፈለሰን ፣ በዳግም ምጽአቱ ከገነት ወደ መንግሥተ ሰማያት ያፈልሰናል ። ከክብር ወደ ክብር እንሻገራለን ። በመጀመሪያው ምጽአቱ አጋንንት አፈሩ ፣ በዳግም ምጽአቱ የናቀን ዓለም ያፍራል ። በመጀመሪያው ምጽአቱ ሞት ተገደበ ፣ በዳግም ምጽአቱ መከራ ይገደባል ።

አብርሃም አገሩና ተስፋው ሩቅ ነበረ ። ክርስቶስ ወደሚወለድበት ምድር ተጠራ ። ዕድሜው እየመሸ ቢሆንም ሠርኩን ማለዳ የሚያደርገው ፣ በሞት ላይ ልደት የሚያውጀው እግዚአብሔር በመልካም አሰበው ። ለሞት ሲሰናዳ ለሕይወት ተጠራ ። ሌጣውን ሊሞት መሆኑን አምኖ ከተስፋ ጋር ሊቀበር ሲል እግዚአብሔር የብዙዎች አባት አደረገው ። የብዙዎች አባት መሆኑን እርሱ አላየም ። አብርሃም ጥቂት ልጆችን ብቻ በዓይኑ አየ ። እግዚአብሔር ባየለት ነገር ተደሰተ ። ተስፋ ማለት እግዚአብሔር ባየልን “ነገ” መደሰት ማለት ነው ። አብርሃም የተዘዋወረበትና ድንኳኑን የተከለበት ምድር በኋለኛው ዘመን ክርስቶስ የሚወለድበትና የማዳን ግብሩን የሚፈጽምበት ነው ። አብርሃም ወደ ቤተልሔም በሄደ ጊዜ “እኔ በድንኳን ኖርሁ ፣ አንተ በበረት ተወለድህ ፣ ቤት አልባ ሆንህ” ብሎ ክርስቶስን በሩቅ ተሳለመው ። ወደ ሞሪያ ተራራ ፣ ወደ ቀራንዮ መጥቶ ልጁን ይስሐቅን ሊሠዋ ባለ ጊዜ ፣ በይስሐቅ ሞት የሚድን ዓለም የለምና የክርስቶስን ቤዛነት ናፈቀ ። ከመልከ ጼዴቅ ኅብስትና ጽዋውን ሲቀበል ፣ ዛሬ በሳሌም የተቀበልሁት ኅብስትና ወይን ፣ ነገ በኢየሩሳሌም በታላቁ ካህን በክርስቶስ የሚሰጠው ሥጋና ደሙ ነው ብሎ ተደነቀ ። አብርሃም ያመነውና የኖረው የዛሬው አማኝ የሚያምነውና የሚኖረውን እውነት ነው ። እምነት በዘመናት መካከል አንድ መልክ ለአማኞች በመስጠት የሚታወቅ ነው ።

ይስሐቅን ከሞት ያዳነው ፣ በዱር የተገኘው ፣ ያለ ቦታው የታየው ፣ ኃይል እያለው እንደሌለው የሆነው የእግዚአብሔር በግ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። አብርሃም የመሥዋዕቱን በግ እግዚአብሔር ያዘጋጃል አለ ፣ ዮሐንስ መጥምቅም “የእግዚአብሔር በግ እነሆ!” አለ ። ያዕቆብ በኤፍራታ ራሔልን ቀበረ ። ራሔል በመውለድ ሞተች ፣ ሕያው ልጅን ሰጥታ እርስዋ አንቀላፋች ። ራሔል በያዕቆብ መወደድዋ ከሞት አላዳናትም ። ወድዶ ከሞት የሚያድን ክርስቶስ ብቻ ነው ። መዝሙረኛው “ወዶኛልና አዳነኝ” ያለው ለዚህ ነው ። የቤተ ልሔም የቀድሞ ስምዋ ኤፍራታ ነው ። ተስፋ ባደረጉት አባቶች ርስት ክርስቶስ ተወለደ ። የይሁዳ አንበሳ የይሁዳ ግዛት በሆነችው ቤተ ልሔም ተወለደ ። የዳዊት ቤትን አልከዳም ብሎ የቀረው ፣ እናቱ በቤተ ልሔም የሞተችበት ፣ የራሔል ልጅ ብንያም ነው ። በታማኙ በብንያም ርስት ክርስቶስ ተወለደ ። ዛሬም እርሱ በሚጠብቁት ርስት በፍቅር ፣ በሰላም ይወለዳል ። ታማኞችን መለኮት አድራሻ ያደርጋቸዋል ። ብዙዎች የከዱትን እኔ አልከዳውም የሚሉ ፣ የቀድሞ ወዳጅነትን የሚያስቡ ዛሬም የክርስቶስ ቤተ ልሔም ናቸው ። እርሱ የሚጸየፈው በረትን ሳይሆን ክዳትን ነው ።

አብርሃም ፣ ይስሐቅና ያዕቆብ ክርስቶስ ከእኔ ወገን ይወለዳል እያሉ ቤታቸውን ንጹሕ አደረጉ ። መጻተኝነታቸውን ረሱት ። ወደውም ለክርስቶስ ድሀ ሆኑ ። በዓለም መጠላታቸውን ናቁት ። ነገሥታት አብርሃምን ተጋጠሙት ። አንድም ቀን በቤተ መንግሥት አልተጋበዘም ። ሁለት ጊዜ ግን ሚስቱን ነጥቀው ፈርዖንና አቤሜሌክ አስደነገጡት ። አማኒ በቤተ መንግሥት ለግብዣ ሳይሆን ያመነውን እንዲጥል ይጠራል ። እግዚአብሔር ቃሉን አክባሪ ነውና ደግሞም በአብርሃም ላይ የተጠራውን ስሙን አክብሯልና ፣ አሁንም እርሱ የሚወጣበትን ዘር ይከላከላልና ሣራን ከነገሥታት እጅ ፈልቅቆ አወጣት ። ክርስቶስ ከነገሥታት ሳይሆን ከመጻተኞች ቤት መወለድን መረጠ ። በአብርሃም ድንኳን ሥላሴ አደሩ ። ወደ ድንግል ማርያም ሥላሴ መጡ ። አብ አጸናት ፣ ወልድ ልጅ ሆናት ። መንፈስ ቅዱስ አከበራት ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 25 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም