የትምህርቱ ርዕስ | የአእምሮ ከንቱነት

“እንግዲህ አሕዛብ ደግሞ በአእምሮአቸው ከንቱነት እንደሚመላለሱ ከእንግዲህ ወዲህ እንዳትመላለሱ እላለሁ በጌታም ሆኜ እመሰክራለሁ።” ኤፌ. 4 ፡ 17 ።

አእምሮ እውቀት ፣ የማወቂያ መሣሪያ ፣ የአመክንዮ/የምክንያታዊነት/ ሞተር ፣ የአሳብ ሙግት ፣ የጥበብ አውድማ ነው ። ሰው አዲስ ነገር አወቅሁ የሚለው እርሱ ስለ ደረሰበት እንጂ ዓለም ሲፈጠር ፣ ዘመን ሲቆጠር የነበረ ነው ። አእምሮ ተመጋቢ በመሆኑ እውቀት ካላገኘ ይዝጋል ። ለመጓጓዣ የተሠራ መኪና ህልውናውን የሚጠብቀው በመጓዝ እንደሆነ አእምሮም ራሱን ከዝገት የሚጠብቀው በማወቅ ነው ። አእምሮ ደመ ነፍሳዊ እውቀት ያለው ቢሆንም በየዕለቱ በአፍም በመጽሐፍም የሚነገረውን ይዞ ማዳበር አለበት ። አእምሮ ምክንያታዊ በመሆን ነገርን ከሥሩ ፣ ውኃን ከጥሩ ይቀዳል ። ሕሊናዊ በመሆንም በምሕረት ያልፋል ፣ ጥፋተኛውን ከጥፋቱ ለይቶ ያየዋል ። አእምሮ የፍጭት ሜዳ ነው ። አሳብና አሳብ መፋጨታቸው ብረትና ብረት መሳሳላቸው ነው ። ሁለት ደነዝ ቢላዋ ሲሳሳል ሁለት ስል ቢላዎች ይወጣቸዋል ። አእምሮ አሳብን የሚፈራ አይደለም ። በመምህርም በመጽሐፍም መሠረት ከያዘ ለመስማት የሚፈራ አይደለም ። አአምሮ እንደ ምላስ ማጣጣሚያ የሚኖረው መርዙን ከምግቡ የሚለየው መሠረት ሲኖረው ነው ። መሠረቱን የመሠረተ ሰው የሚያገኘውን አዲስ አሳብ በዚያ ላይ ይክበዋል ። መሠረት ያልመሠረተ ግን የሚሰማው ሁሉ ያፈርሰዋል ፣ የዕለት ቤት ፣ የበረሃ ዳስ ፣ የዘላን ድንኳን አድርጎ ይሠራዋል ። በየዕለቱ አዲስ ሃይማኖትና ፍልስፍና ይዘው ሲሰክሩና ሲያሰክሩ የሚውሉ ሰዎች መሠረት የሌላቸው ሰዎች ናቸው ። ባነበቡት ሁሉ እየተወሰዱ በየሳምነቱ አዳዲስ ፍልስፍና የሚያራምዱ ዘግይተው ማንበብ የጀመሩ ፣ በመምህር ተወቅረው ያልተገነቡ ናቸው ። እውቀት ዲሲፕሊን የሚኖረው በመምህር ነው ። እነዚህ ሰዎች “ደንቆሮ የሰማ ቀን ያብዳል” እንዲሉ ሁለት ሺህ ዓመት የሞላውን ኑፋቄ አዲስ መገለጥ ብለው ይይዛሉ ።

አእምሮ ጥበብን ይመገባል ፣ በጥበብ ይወዛል ፣ በጥበብ ይወረዛል ፣ በጥበብ ይረጥባል ፣ በጥበብ ያረጥባል ። ልብ አድርጉ ጥበብ ማለት ፀጉርን ማንጨብረር አይደለም ። ይህ ጥበብም የጥበብ መገለጫም አይደለም ። ስንፍና ነው ። ጥበብ ክርስቶስ ነውና ክርስቶስ የሌለበት ጥበብ ከንቱ ነው ። ስለ ዓለም ብናውቅ የሠራውን ካላወቅን ምንም አይጠቅመንም ። ባለቤት ስለሌለው ቤት እንደ ማጥናት ነው ። የመጨረሻ ጥበብ እግዚአብሔር ነው ። እግዚአብሔርን ተምሮ የምስክር ወረቀት የሚቀበል ማንም የለም ። ታውቆ አይፈጸምምና ሰው ሁልጊዜ ተማሪ ነው ። በአእምሮ አውድማ ላይ ጥበብ ይወቃል ። ገለባው ከስንዴው ይለያል ። የሚለየውም ነፋስ ነው ። ነፋስ መንፈስ የተባለ መንፈስ ቅዱስ በአእምሮ ሜዳ ላይ ጥበብን ከገለባ ይለያታል ። አእምሮ በአንደበት የሚነገሩ ነገሮች የሚጣሩበት ነው ። አንደበት በምድር ላይ ካሉ ታላላቅ ኃይሎች ቀዳሚ ነው ። ጦርነት የሚቀሰቀሰውም የሚቆመውም በአንደበት ነው ። እሳትን እፍ ብለን የምናቀጣጥለው እፍ ብለን የምናጠፋው በአንደበት ነው ። “እፍ ያነዳል ፣ እፍ ያጠፋል” እንዲሉ ። አእምሮ በእውቀት ያጣራል ፣ በጥበብ ያስውባል ፣ በማስተዋል ይተምናል ። ያልተጣራ እውቀት ፣ ያልተዋበ ጥበብ ፣ ያልተተመነ ማስተዋል አይባልም ። መረጃና እውቀት ልዩነት አለው ። በዛሬው ምግባችን ላይ ብርቱካን ላይበላ ይችላል ። በእንጀራ ግን መዋል ይቻላል ። እንጀራ መደበኛ ምግባችን ነው ። መረጃ ተጨማሪ የዕለት እውቀት ነው ። ጋዜጣ አንድ ቀን ካለፈው ያደረ የወሬ ቋንጣ ነው ። አእምሮን ሕያው የሚያደርግ እግዚአብሔርን ማሰብ ፣ ጸሎት ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ፣ በጎ እውቀትን መናገር ፣ ማሰላሰል ፣ ያለ ማቋረጥ መማር ተጠቃሽ ነው ።

አሕዛብ በአእምሮ ከንቱነት ይመላለሳሉ ። ክርስቲያኖችም በአእምሮ ከንቱነት የሚመላለሱበት ጊዜ ብዙ ነው ። ሐዋርያው የአእምሮ ከንቱነት ምን እንደሆነ ቀጥሎ ይናገራል፡- “እነርሱ ባለማወቃቸው ጠንቅ በልባቸውም ደንዳንነት ጠንቅ ልቡናቸው ጨለመ ፥ ከእግዚአብሔርም ሕይወት ራቁ ፤ ደንዝዘውም በመመኘት ርኵሰትን ሁሉ ለማድረግ ራሳቸውን ወደ ሴሰኝነት አሳልፈው ሰጡ ።” ኤፌ. 4 ፡ 19-19 ። የአእምሮ ከንቱነት ማወቅ አለመፈለግ ነው ። አለማወቅ በሰላም ለመኖር ፣ አለማወቅ ሃይማኖትን ለመጠበቅ አስፈላጊ እንደሆነ ማሰብ የአሕዛብ አመለካከት ነው ። አሕዛብ ያመኑትን በሥጋዊ ኃይል ማስጠበቅ ይፈልጋሉ እንጂ የአሳብን የበላይነት አያምኑም ። በዱላ የሚያስብ በአእምሮ ማሰብ አይችልም ። ሁለቱም አንድ ጊዜ አይሠሩም ። ዱላና አእምሮ ። ዱላ ሲነሣ አእምሮ የዓመት ፈቃዱን ሞልቶ ይሄዳል ። አእምሮ ሲነሣ ዱላን ይጥላል ፣ ያስጥላል ። አለማወቅ ጠንቅ ነው ። አስቸጋሪ በሽታዎች አሉ ይባላል ፣ ከባዱ ጠንቅ ግን አለማወቅ ነው ። ከንቱ አእምሮ ሁለተኛ መገለጫ አለው ። የልብ ደንዳናነት ። ደንዳና የተለያየ ነው ። አንገተ ደንዳና ሲባል ለማቀፍ የማይመች ፣ አንገቱ የወፈረ ፣ ሲወዱት የሚጨንቀው ፣ ሲያቀርቡት የሚርቅ ፣ ወፈፌነት የተጠናወተው ፣ የፍቅርና የጥላቻን ልዩነት የማያውቅ ድንዙዝ ማለት ነው ። ልበ ደንዳና ማለት ደግሞ ፍቅር ወደ ውስጡ እንዳይገባ የሚከላከል ፣ ውለታ ቢስና ይገባኛል ባይ ፣ ቀምቶ ራጭ ፣ ይሉኝታ ቢስ ነው ። የአእምሮ ከንቱነት ልበ ደንዳናነት ነው ። ይህ በሽታ ክርስቲያንንም ሊያጠቃ ይችላል ።

ከንቱ አእምሮ ሦስተኛው ጨለምተኛ ልብ ነው ። በውስጡ ምንም ተስፋ የማይታየው ፣ ሁሉን ነገር በዜሮ የሚያባዛ ፣ ለኖረበት ዘመን ዋጋ የማይሰጥ ፣ የኖሩ ነገሮችን የማያከብር ፣ በአጭር ቃል አጥፍቶ ጠፊ ነው ። ጨለማ ልብ ያለው ሰው እግዚአብሔርን ሳይሆን ጊዜን በማየት ብቻ ሕይወት እንዲህ ነው ብሎ ብይን የሚሰጥ ነው ። ከንቱ አአምሮ አሳልፎ የሚሰጠው ከሕይወት ለመራቅ ነው ። ከሕይወት የራቀ ሰው ከፀሐይ እንደ ራቀ ሰው ይገረጣል ። በሰሜን ንፍቀ ክበብ የሚኖሩ መልካቸው ሊጥ ፣ በምድር ወገብ የሚኖሩ መልካቸው አራራ የሚመስለው ከፀሐይ ጋር ባላቸው ርቀትና ቅርበት ነው ። ነጭና ጥቁር ማለት የመመጻደቂያ ቀለም ሳይሆን ፀሐይን በጣም መቅረብና መራቅ የሚያመጣው ጣጣ ነው ። ፀሐዩ መንግሥት ይባላል ። ንጉሥም ሲቀርቡት ያሳርራል ፣ ሲርቁት ይበርዳል ። በመካከለኛው ስፍራ መቀመጥ ይገባል ።

ከንቱ አእምሮ በመመኘት የተያዘ ነው ። መመኘትም ሴሰኝነትን ወይም ዝሙትን ይወልዳል ። በምስሉ ፣ በፊልሙ ፣ በጨዋታው ሁሉ ከዝሙት ወሬ የማያርፉ አሕዛብ ናቸው ። የአሕዛብነት ምንጩ ግን እግዚአብሔርን ለማወቅ አለመውደድ ነው ። አሕዛብነት ዘር አይደለም ፣ ምርጫ ነው ። የአእምሮ ከንቱነት ምንም አለማወቅ አይደለም ። ስለ ተፈጥሮ ስለ ዘመን ሠራሽ ነገር የሚመራመሩ ፣ ኑሮን እያቀለሉ ሕይወትን እያከበዱ ያሉ ብዙ አዋቂዎች አሉ ። የአእምሮ ከንቱነት የሚድነው እግዚአብሔርን በማወቅ ነው ።

አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ ፣ ዘወትር አንተን እናይህ ዘንድ የልቡናችንን ዓይን አብራልን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 13 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም