መግቢያ » ከመጻሕፍት » ወዳጄ ሆይ » የአጥቢያ ኮከብ

የትምህርቱ ርዕስ | የአጥቢያ ኮከብ

 

ወዳጄ ሆይ !

ቤትህ ሥርዓት ከሌለው ደስታ እየራቀህ ይመጣል  ። ቢሮህ ሥርዓት ከሌለው ሥራህ ይበላሻል ። አገልግሎትህ ሥርዓት ከሌለው ሰሚ ያጣል ። ኑሮህ ሥርዓት ከሌለው ጎዳና ላይ ይጥልሃል ። አገርህ ሥርዓት ከሌለው ጻድቅ ይጨነቅባታል ። ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ከሌላት ውበትዋ ይጠፋል ። ፍቅርህ ሥርዓት ከሌለው የምትወደው ይጠላሃል ። ጠብህ ሥርዓት ከሌለው ወንጀለኛ ያደርግሃል ። ቸርነትህ ሥርዓት ከሌለው መበተን ይሆናል ። አለባበስህ ሥርዓት ከሌለው ያራቁትሃል ። አቀራረብህ ሥርዓት ከሌለው ሁሉ ይደፍርሃል ። ቅጣትህ ሥርዓት ከሌለው ልጅ ገዳይ ያደርግሃል ። አኗኗርህ ሥርዓት ከሌለው ቶሎ ይጥልሃል ። 

ወዳጄ ሆይ !

የፈጸሙት ተልእኮ ልደት ያዩበት ምጥ ነው ። ያስረከቡት አደራ የነፍስ አርነት ነው ። በሰዓት መድረስ ትልቅ ውለታ ነው ። በቁም የረዱትን ስቀው ይቀብሩታል ። አግኝቶ ያጣው ቶሎ ቶሎ ይከፋዋልና ታገሠው ። አጥቶ ያገኘ ምድር ይጠበዋልና ምክረው ። ከፍታህ ዝቅተኞችን በመርገጥ ፣ ህልውናህ በሌሎች ሬሳ ላይ አይሁን ። የፍቅር ሰው ለመባል ሁሉም ትክክል ነው አትበል ። ግልጽ ጥላቻ የፍቅር ያህል ነው ። ግልጽ ንግግር ሰሚውን ያከበረ ነው ። እጅግ ግልጽነትም የሚያስገምት ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

በስሜትህ ላይ ያገኘኸው ድል በጦር ሜዳ ከምታገኘው ድል በላይ ነው ። ምስክርነት የሰይጣንን ሥራ ማፍረስ ነው ። መልካም ቃል የቀን ጉልበት ነው ። ፀሐይ ሳትጠልቅ ሥራህን ፣ ጨረቃ ሳትሰወር ተግባርህን ፣ ከዋክብት ሳይጠፉ ድርሻህን ፈጽም ። ፀሐይ የተባለ ደግ አባት ፣ ጨረቃ የተባለች እናት ፣ ከዋክብት የተባሉ ወንድምና እኅቶች ናቸው ። ፀሐይ አንዲት ናት ፣ አባትም አንድ ነው ፣ ጨረቃም አንዲት ናት ፣ እናትም አንድ ናት ። ከዋክብት ብዙ ናቸው ፣ እኅትና ወንድሞችም ብዙ ናቸው ። 

ወዳጄ ሆይ !

ሳይማር ማስተዋል ያለው ፣ ማስተዋል ከሌለው ምሁር የተሻለ ነው ። ማስተዋል ትምህርትን ይጠቀልላል ፣ ትምህርት ግን ማስተዋልን ላያመጣ ይችላል ። ጸሎት ትተህ ወሬን ስትመርጥ የሚመጣውን መከራ ለመሸከም ራስህን አዘጋጅ ። ክፉ ቀን እየጠበቅህ የወደቀ ሰውን በቃላት አትጉዳ ። በዚህ ዓለም አንድ ቀንም ለመከራ ረጅም ነውና ጨርሼዋለሁ ብለህ አትመካ ። መልካም ተግባር የሚሠራ ስታገኝ ተቀላቀለው ። ስሜ አልተጠራም ብለህ በጎ ሥራህን አታቁም ። ተራሮችን ካላየህ ኮረብቶች ተራራ ይመስሉሃል ። በሜዳ ያደገ ስለ ጉብታ የሚያወራው እንደ ዳሸን ተራራ ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

በአንድ ጊዜ ጳጳስ ሁን ቢሉህ ከአናጕንስጢስነት/ከአንባቢ ከተላላኪ/ ጀምረህ መሠረት እየያዝህ እደግ ። ትልቅ ወንበር ላይ ለመቀመጥ ስትጓዝ አትኑር ። ምድር ጊዜያዊ ቤት ናትና ማጣትህም ጊዜያዊ ነው ። በአካል ተባብረህ በልብ ከምትለያይ በአካል ተለያይተህ በልብ መቀራረብ ይሻላል ። የአንድነት ትርጉም አንድ አዳራሽ ውስጥ መሰብሰብ ሳይሆን አንድ መንፈስ መያዝ ነው ። የማይደግፍ ባለጠጋ ልጅ ልመና ከልክል ነው ፣ ልጁ አለ እያለ ሁሉ ይጨክንብሃልና ። ልጄ ይጦረኛል ብለህ ሀብትህን አታሟጥ ፣ የድርሻውን ብቻ ስጥ ። ልጅ ከጦረው እጁ የጦረው ይሻላል ። 

ወዳጄ ሆይ ! 

በምድር ላይ ያለው የመኖር ትርፍህ ከምትወደው ጋር ማሳለፍ ነው ። የማትችለውን ነገር እችላለሁ ብለህ አታውራ ፣ በግዳጅ ፈጽም የተባልህ ቀን መድረሻ ታጣለህና ። ያንተ ባልሆነ ጌጥ አታጊጥ ። ድህነትም ከጨዋነት ጋር ሀብት ነውና አትቀላምድ ። በእግዚአብሔር ቃል አታፊዝ ፣ በነገረ እግዚአብሔር ላይ አትቀልድ ። የሕጉ የመጀመሪያው ጠባቂ ንጉሡ ነው ። የበላይ ያከበረውን ሕግ የበታች አይዳፈረውም ። 

ወዳጄ ሆይ !

የወደቀውን ሰው እግዚአብሔር አያልፍም ። ወደሚፈሰው ደም እግዚአብሔር ያያል ። የምትሰጠውም ፍርድ  የነገ መውደቂያህ ይሆናል ። ባልገባህ ነገር መጸለይ ክብር ነው ። ሁሉን ተናግረህ ስለማትዘልቀው ዝም በል ። ፍርድህ በቀል ፣ ቅጣትህ ንዴት ማብረጃ አይሁን ። ፍርድና ቅጣት ትምህርት ብቻ ይሁን ። የሌላው ሌሊት ቀን ይከተለዋልና አትጨክን ፣ ያንተ ቀንም ሌሊት ይከተለዋልና መብራት የሚሆን ተግባር ፈጽም ። 

የክብር ቀን ይሁንልህ !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥቅምት 29 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም