የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

የኢትዮጵያ ወጣቶች ችግር /4

የኢትዮጵያ ወጣቶች በሚያልፉባቸው የተለያዩ ችግሮች ምክንያት አሁን ላይ እየታዩ ያሉ ውጤቶች አሉ ።

ገንዘብን የሕይወት ዋስትና ማድረግ

ዓለም በርእዮት መልኩ ባለጠግነትን ታራምዳለች ፣ በሃይማኖት ስምም ባለጠግነት ይሰበካል ። የዚህ ዓለም ገዥ ገንዘብ እንደሆነ ከመቼውም ጊዜ ይልቅ እየታወቀ ነው ። ገንዘብን እያሳዩ የፈለጉትን ስህተት የሚያሠሩ ፣ ብሔራዊ እሴቶችን የሚያጠፉ ፣ የአገራትን እጅ የሚጠመዝዙ የዘመናችን ኃያላን አሉ ። ገንዘብ ብዙዎችን ከሃይማኖትና ከጥሪያቸው ለይቷቸዋል ። ፍቅረ ንዋይን ያወግዙ የነበሩ ሰዎች በዚህ መርዝ ተይዘዋል ። በመጀመሪያው የሰው ልጅ ጉዞ የነበረው ኃጢአት በመጨረሻው ዘመን ላይ መንገሡ ግድ ነው ። ስስት ፣ ትዕቢት ፣ ፍቅረ ንዋይ አዳምን ያጠመዱ የኃጢአት ራሶች ናቸው ። እነዚህ ስህተቶች በመጨረሻው ቀን ይሰለጥናሉ ። የሰው ልጅ በቃኝ የማይል ስስታም ፣ ነጥቆ አዳሪ ፣ በሌላው ንብረት የሚቀና ፣ ለመስጠት የሚፈተን ፣ ሁሉን ላፌ የሚል ፣ ብልጣብልጥነት ያሳነሰው ፍጡር ይሆናል ። ወንዱም ሴቱም ተፈጥሮአቸውን ተቀበሉት እንጂ አልፈጠሩትም ። ትዕቢት ግን እግዚአብሔርን ተክቶ እኔ በማለት ይቆማል ። በዚህ ዘመን ሰዎች ራሳቸውን በመሸጥ ፣ ስለ ራሳቸው በግነት በማውራት ፣ መብቴ ነው በሚል ድምፀት ትዕቢትን ጣዖት አድርገው አጥነዋል ። ካለህ አለህ ፣ ከሌለህ  የለህም እያለ በግልጽ የሚፈክር ዘመን ይህ የእኛ አናሳ ዘመን ነው ። ሰዎች ገንዘብ ለሰጣቸው ሁሉን ለመሆን ዝግጁ ናቸው ። ገንዘብ ሕሊናን የሚያሸጥ ፣ ሰብአዊ ክብርን የሚያስጥል ፣ ከሃይማኖት ማማ የሚያወርድ ነው ። የወንድምን ፍቅር በመሻማት እንደ ገንዘብ የሚፈታተን ነገር የለም ። ብዙ ሰዎች ወዳጃቸውን በገንዘብ ምክንያት አስቀይመዋል ። ይልቁንም የእርሱ የጋራ ፣ የእኔ የግል የሚል አመለካከት እየዳበረ ነው ። በዚህ ምክንያት በሰው እጅ ያለውን በመብት ደረጃ ለመንጠቅ የሚፈልጉ ፣ ቀማኝነትን ያሳደጉ ወገኖች እየበዙ ነው ። ሰውን ለመኖር የሚያስከፍሉ ፣ አፍነው የሚደራደሩትን ወጣቶች ስናይ ገንዘብ የሰው ልጆችን ምን ያህል እንደ በከለ መገንዘብ ይቻላል ።

የአገር አለመረጋጋት ወጣቶችን እንዳይረጋጉ ያደርጋቸዋል ። አንዳንዱ አገር ጥሎ ሲሰደድ ሌላው ደግሞ በትዕግሥት እንዳይኖርና እንዳይሠራ ያደርገዋል ። በዚህ ምክንያት ወጣቶች በአንድ አዳር ሚሊየነር ስለመሆን ያስባሉ ። በአንድ ጊዜ ባለጠጋ ለመሆን የሚያስብ ሰው የዕድገት ሕግን ያፈረሰ ፣ በነገ ላይ ምንም ተስፋ የሌለው ሰው ነው ። በአእምሮ ሰላምና በመረጋጋት የኖሩት ፣ ሌላውንም ለመርዳት የቻሉት እነዚያ የቀደሙት ወላጆቻችን ሕይወት ነገም እንደሚቀጥል ተገንዝበው የዕለት የዕለቱን መኖር በመቻላቸው ነው ። ትርፍ ነገር አልነበራቸውም ፣ ነገር ግን አልጎደለባቸውም ። እንደ ጎርፍ የሚመጣ ዕድል ጠርጎ የሚሄድ ነው ። በአጭር ጊዜ ውስጥ ባለጠጋ ከሆኑት አንዳንዱ አገር ለቆ ተሰዷል ፣ ሌላው እስር ቤት ይገኛል ። ሌላውም በአእምሮ ጭንቀትና በተበላሸ ትዳር ይዳክራል ። የእድገት ሕጎች ነገን ለመኖር ተስፋ የሚሰጡ ናቸው ። እንኳን ሁሉም ነገር ዛሬ ይሁንልኝ ብሎ ማልቀስ ይቅርና ሁሉም ነገር ዛሬ ይሁንላችሁ ተብሎ ብንለመን እንቢ ማለት አለብን ። የሰውን ልጅ የሚያኖረው ያልተፈጸመ ሕልሙ ነው ። በዚህ ዘመን ያሉ ወጣቶች በአብዛኛው ዋጋ ሲጠሩ ፣ ይህን ያህል አምጡ ሲሉ ስቅቅ አይላቸውም ። ይህ የሚያሳየው ጨካኞችና የገንዘብ አምልኮተኞች መሆናቸውን ነው ፣ ፍቅር አልባ የሆነ ሰው አለው ያምጣ የሚል ነው ።

ሁሉንም ነገር ወደ ቢዝነስ የመቀየር ስልት በጣም አደገኛ ነው ። ዛሬ በፐርሰንት ሳይቀር ለቤተ ክርስቲያን የሚያስለምኑ አሉ ። ለገዛ ወላጆቻቸው በገንዘብ የሚሠሩ ትውልዶች እያየን ነው ። ገንዘቡ ቢገኝም ዕድሜው ግን ውድ ሆኗል ። ገንዘብን ለማግኘት የተጠቀሙበት ብልጠት ለመኖርና ሞትን ለማምለጥ አልረዳም ።

ወጣቶች ከሁሉ ለምትበልጠው ጸጋ ለፍቅር ቅኑ!

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኮንን
ታኅሣሥ 10 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ