መግቢያ » ስብከት » የእግዚአብሔር ባሪያ » የእግዚአብሔር ባሪያ/2

የትምህርቱ ርዕስ | የእግዚአብሔር ባሪያ/2

ፓፒረስ እየተባለ የሚጠራ በዓባይ ወንዝ ዳርቻ በሚበቅለው የሸምበቆ ተክል የሚሠራ ጥንታዊ የመጻፊያ ወረቀት ነው ። ሙሴ አምስቱን ብሔረ ኦሪት የጻፈው በዚህ ጥንታዊ መጻፊያ ፓፒረስና በብራና እንደሆነ ይታመናል ። ይህ የሸምበቆ ተክል ሙሴ ወደ ዓባይ ወንዝ በደንገል ተደርጎ በተጣለ ጊዜ ደግፎ የያዘው ፣ እንዳይርቅ የከለለው ፣ ነፋስ እንዳይወስደው የጠበቀው ፣ እንዳይታይ የሸፈነው ነው ። የዓባይ ወንዝ ምንጩ ኢትዮጵያ ነው ፣ ወንዙ ያፈራው ሸምበቆ ፓፒረስን ሲያስገኝ ሙሴ ደግሞ መጽሐፍ ቅዱስን ጻፈበት ። ዓባይ የሚነሣበት ምንጩ ኢትዮጵያ ናትና ሙሴ ኢትዮጵያይቱን ሴት አገባ ። ኢትዮጵያና ሙሴ የሚተዋወቁት ከክርስቶስ ልደት በፊት ከ1600 ዓመት ቀደም ብሎ ነው ። ሙሴ ኢትዮጵያይቱንም አገባ ። ያ ወንዝ የተጣለው ሕፃን ባሕረ ኤርትራን ከፍሎ ሕዝቡን ያሻግር ዘንድ እግዚአብሔር ጠራው ። ሙሴን ለእስራኤል ታዳጊነት ያዘጋጁ ሁለት ሴቶች ሊረሱ አይገባም ። ሦስተኛይቱ ሴትም የፈርዖን ልጅ የሆነችም ልዕልት ናት ። ልትደነቅ ይገባታል ። አባቷ ሰው ያንቃል ፣ እርሷ ደግሞ ሕፃን ታሳድጋለች ። ሰው በአባቱ መመዘን የለበትም ። ቤተሰቦች በሥጋ ቅርብ ቢሆኑም በአሳብ ግን ልዩ ናቸው ። የአባትን ዕዳ ልጅ መሸከም በክርስቶስ የተሰረዘ ነው ።

የዓባይ ወንዝ ዳር ያለው የሸምበቆ ተክል እንደ ደግ ሰው አግዟታል ። ነፋስ ደንገሉን ሊወስደው ሲል ይይዝላታል ። እስከ አንገቷ ወደ ወንዙ ጠልቃ ደንገሉንና ሕፃኑን ለሸምበቆው አደራ ብላ ትወጣለች ። ሕፃኑ በውኃው ዥዋዥዌ ቢጫወትም ያች ሴት ግን በምጥ ትውል ነበር ። ሸምበቆ ድጋፍ ፣ ባሕር መሠረት የሆነውን ያንን ደንገል በሩቅ በዓይኖቿ የምትጠብቀው አንዲት ሴት ነበረች ። ሰጎን እንቁላሏን ያለ ማቋረጥ ካላየች እንቁላሉ ይበሰብሳል የሚል አስተሳሰብ አለ ። ያንን ደንገል ያለ ማቋረጥ ካላየች ያ ደንገል ሊርቅ ፣ ውኃ አስገብቶ ሊሰጥም ይችላል ፤ ባለ ራእዩም ሊሰጥም ይችላል ። ባለ ራእዩን እንዲህ የምትንከባከበው ያች ሴት ልትደነቅ ይገባታል ። ከሚታዩ ሰዎች ጀርባ የማይታዩ ሰዎች አሉ ። ይህች ሴት እናት አይደለችም ፣ የእናት አንጀት ግን ተሰጥቷታል ። እናት ሁነው እንደ እህት የሚያስቡ ፣ እህት ሁነው እንደ እናት የሚያስቡ አሉ ። አባትነት ከሚሰየምበት የአብ ዙፋን እናትነትም ይሰየማል ። ያልወለዱም የእናት አንጀት አላቸው ። እናትነትን ዋጋ የሰጠው ምጡ ብቻ አይደለም ፍቅሩም ነው ። በአካል የሚያምጡ ከምጥ በኋላ ይታደሳሉ ። በአሳብ የሚያምጡ ግን ከአሳብ በኋላ ይዳከማሉ ። ከአንድ አሳብ ኩንታል ተሸክሞ መዋል ይቀላል ። የአሳብ ጭነት ላግዝህ የማይባል ፣ መሸከሙን የተሸከመው ብቻ የሚያውቀው ነው ። ይህች የእናትነት አንጀት የነበራት ሴት የንጉሥን አዋጅ ሽራ ሕፃኑን ወንድሟን ትጠብቃለች ። እናቱ ለምን አትጠብቅም ቢባል የሦስት ወር አራስ ናት ። እንዳትጎዳባት በማለት ነው ። ወዲህ የእናት ውለታን ትከፍላለች ፣ ወዲህ ለወንድሟ ውለታ ታቆያለች ። ሕይወት ለማዳን ሕይወቷን አደጋ ላይ ጥላ ነበር ። ቆይታ ግን ትጠብቅ የነበረው አንድ ሚሊየን እስራኤልን እንደሆነ ተረድታለች ። ከባለ ራእዩ ጀርባ ባለ ራእዩን የጠበቁ ሰዎች አሉ ። ጾታቸው የተናቀ ፣ አቅማቸው የደከመ ፣ ከእልፍኝ የማይወጡ ይሆናሉ ፤ ኃያላንን ግን የሚያሰናዱ እነዚህ ናቸው ። አመድ ሁነው እሳት ያደረጉንን ልናመሰግን ይገባናል ። የእሳት ልጆችም አመድ በመሆናቸው ልናዝን ይገባናል ።

ሁኔታው እስራኤል ከረሀብ ሸሽተው ሰባ ነፍስ ሁነው ወደ ግብጽ የወረዱበት ነው ። ነገር ግን “ከእባብ ጉድጓድ አምልጦ ዘንዶ ጉድጓድ” የሚባለው አባባል የተፈጸመበት ነው ። ሞት ሸሽተው ወደ ሞት እየሄዱ ነበረ ። ተስፋ አድርገው የወጡት ገደልነው ያሉትን ዮሴፍን ነው ። ሟቹ ሕይወት ሰጪ ሆነ ። ዮሴፍ ሞቱ በከነዓን ሲነገር በግብጽ ግን ነግሦአል ። ክርስቶስም አይሁድ ገደልነው ብለው ሲደሰቱ በሰማይ የድል ነሺነቱን ምሥጋና እየተቀበለ ነው ። በዚያው በከነዓን የዮሴፍ ወንድሞች ገዳይ ሁነው አባቱ ደግሞ አልቃሽ ሁኖ ተቀምጠዋል ። በዚያው በኢየሩሳሌም የክርስቶስ ሰቃዮችና የክርስቶስ ወዳጆች ሐዋርያት ነበሩ ። ገደልነው ባሉትና በሸጡት በዮሴፍ ከረሀብ እንደ ዳኑ ዛሬም በሠላሳ ብር በተሸጠው ክርስቶስና በሰቀሉት ጌታ እስራኤል ከመላው ዓለም በሚመጣ ጎብኚ እንጀራ ትበላለች ። ክርስቶስ ለሚጠሉትም እንጀራ ነውና ።

ዮሴፍ ጠዋቱ መከራ ነበረበትና ማታው አምሮለት በሰላም ተሸኘ ። ጠዋቱን በክፋት የተጓደዱ ወንድሞቹ ግን ማታው አላማረላቸውም ። በአባታቸውና በወንድማቸው በረከትና ጸሎት ኖሩ ። አባታቸውና ወንድማቸው እልፍ ሲሉ መዓቱ ያለ ከልካይ መፍሰስ ጀመረ ። በበደላችን ልክ መዓቱ እንዳይፈስ የሚከለክለው የቅዱሳን ጸሎት ነው ። እግዚአብሔር ቅዱሳኑ ልባቸው እንዳይሰበር ያጠፉትን ኀጥአን ያልፋል ። የቅዱሳን ጸሎት መዓት ከልካይ ነው ። እኛ ከተማ እየዘለልን በድንግልና በምንኩስና ጠፈር ታጥቀው በየገዳማቱ የተቀመጡት ለአንድ ነፍሳቸው ብቻ አይደለም ። የጸሎት ዘብ ለመሆንና ወገናቸውን ለማትረፍ ነው ።

ዮሴፍን የማያውቅ ንጉሥ ተነሣ ። የእስራኤልን መብዛት ለመቆጣጠር ንድፍ አወጣ ። ነገ ሕዝቡ እየበዛ ሲመጣ አልገዛም ሊልና ከጠላት ጋር ሁኖ ሊቆጣጠረን ይችላል ብሎ ሰጋ ። ጠላት ለቀጣይ ሃያና ሠላሳ ዓመታት አንዳንዴም መቶ ዓመታት ያቅዳል እኛ ግን የአምስት ዓመት ዕቅድ እንኳ የለንም ። ሄሮድስ የተወለደውን ሕፃን ሊገድል የፈለገው ከሃያ ዓመት በኋላ ዙፋኔን ይነጥቀኛል ብሎ ነው ። ሄሮድስ ግን የቀረው ዕድሜ ሦስት ዓመት ነበረ ። ለካ የምንገድለው ብዙ የምንኖር እየመሰለን ነው ። ፈርዖንም ሕዝቡን በባርነት ግብር ያዘ ። አዲስ የሚወለዱ ወንዶች ግን ከማኅፀን ደጃፍ ላይ እየታነቁ እንዲገደሉ ብሎ አዋጅ አወጀ ። በፈርዖን ዱላ እስራኤል ግብጽ መኖሪያቸው እንዳልሆነች ተገነዘቡ ። እግዚአብሔር ምቾትን በመንሣት የእኛ ካልሆነው ሰፈር ያስወጣናል ። ሁለተኛ በሰማይ ያለውን የቃል ኪዳን አምላክ አስታወሱ ። ክፉዎች ደጉን አምላክ እንድንጠራው ያደርጉናል ።

ለግብጽ አዋላጆች ትእዛዝ ተሰጠ ። ወንድ ሲወለድ ወዲያው አንቀው እንዲገድሉት ፣ ሴት ከሆነች ግን ውኃ ለመቅዳት ፣ እንጨት ለመስበር እንድትተርፍ ጥብቅ መመሪያ በቀጥታ በንጉሡ ተላለፈላቸው ። ንጉሡ ወርዶ የሚወለዱ ሕፃናት ላይ ጦርነት ከፈተ ። ፈርዖን ማለት ይላሉ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፡- “ግፈኛ ፤ ግፍ ሠሪ ፤ ሙት አስገባሪ ማለት ነው ። ላንድ ሰው መቃብር 200 ብር ይቀበል ነበረ ይባላል” ብለዋል ። /መጽሐፈ ሰዋስዉ ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ ፤ ገጽ 733 ።/ እኛ ሰማንያ ሺህ ብር የደረሰው የመቃብር ሽያጫችን ምን ያሰኘን ይሆን  ዛሬም ሙት አስገባሪ ፈርዖን ነን ። የእስራኤል ልጆች በሥራ ጫናና በልጆቻቸው ኀዘን ተሰበሩ ። ያ ዘመን መሐን እልል ትበል የተባለበት ዘመን ነበር ። መሐንም ግን በጎረቤት ልጅ ታዝናለች ። ያሳደገችው ነውና ። እንደውም ብዙዎች መሐን የሚሆኑት በጣም ሩኅሩኅ ስለሆኑና ለልጅ ስለሚሳሱ ራሳቸውንም ልጁን አስጨንቀው ከጤና ዓለም እንዳይወጡ ነው ። እጅግም ርኅራኄ እስር ቤት ነውና ።

ንጉሡ ያዘዛቸው የዕብራውያን አዋላጆች ሲፓራና ፉሐ ግን እግዚአብሔርን ፈሩ ። ብዙ ወንዶች ሕፃናትን አዳኑአቸው ። ዛሬም የሚወለዱ ብዙ ነገሮች ቢኖሩም ሞት ግን ታውጆባቸዋል ። የሚታደጉ አዋላጆች ፣ የንጉሥን ቍጣ የማይፈሩ ጎበዞች ይኖሩ ይሆን  በአገራችን ልደት እንጂ ዕድገት አይታይም ። የሚወለዱ ነገሮች በነገሥታት ቅናት ወዲያው ታንቀው ይገደላሉ ። ስለዚህ አገራችን ሁልጊዜ በጅምር ናት ። ያለቀ ነገር እስቲ ጥሩ ብንባል መጥራት የሚያቅተን ይመስላል ። መጽሐፍም ልጅ ነው ። ጽንሰት ፣ እርግዝና ፣ ምጥና ልደት አለው ። ትልቁን መዝገበ ቃላት ለማሰናዳት ያሰቡት አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በትንሹ መጽሐፋቸው “መዝገበ ፊደላት ሴማውያት” ላይ እንዲህ ብለዋል፡-

ይህን ጨቅላ መጽሐፍ የምታዩ ኹሉ ፣
ዐደራ ስለኔ ማሪያም ማሪያም በሉ ፤
በሆዴ ያለውን የትምርት ሽል ፣
አለጭንቅ እንድወልድ እንድገላገል ፤
ከኻያ ስድስቱ ወንዶች ፊደላት ፣
አርግዣለሁና መዝገበ ቃላት ።

መጽሐፍ እርግዝና ነውና አዋላጆች ያስፈልጉታል ። በርታ ፣ ግፋ ፣ ደርሷል ፣ ትንሽ ነው የቀረው እያሉ የሚያግዙ ያስፈልጉታል ። ሕፃኑን የወለደቸው ሳትሆን ያዋለዱት መጀመሪያ እንደሚያዩትና እንደሚያነሡት መጽሐፍም በረከቱ መጀመሪያ ለአንባብያን ነው ። እንደ ፈርዖን ጨቅላ ደራስያንን ፣ ለማነቅ የሳንሱር ሕግ ያወጡ ፣ አሳብ እንዲጨቆን የወረቀት ታክስ የጨመሩ ነገሥታት በዘመናችን አይተናል ። እግዚአብሔርን የሚፈሩ አዋላጆች በርታና ጻፍ ሲሉ ነገሥታት ደግሞ እንዳይታተም በመከልከላቸው የገዛ መጻሕፍቶቻቸውን በኀዘን ያቃጠሉ ምሁራንን ተመልክተናል ። ያ ዘመን አልፎ ያውም በቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት ሲቃጠሉ አይተናል ። አንድ ሰው እንዳለው፡- “መጻሕፍት ሲቃጠሉ ቀጥሎ ሰው ይቃጠላል” የተባለው ደርሶ ብዙ ሰው ሲቃጠል ፣ ብዙ አብያተ ክርስቲያናት ሲቃጠሉ አየን ። ብቅ የሚሉትን ማነቅ ፣ ፈርዖናዊው አዋጅ ዛሬም አለ ። አዋላጆች ግን እግዚአብሔርን ከፈሩ ፣ ምእመናን በርቱ ብለው ካበረታቱ ብዙ የመጻሕፍት ልጆች ይወለዳሉ ።

ይቀጥላል

የእግዚአብሔር ባሪያ/2
ሰኔ 2 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን መኰንን

https://t.me/Nolawii

እባክዎ ይህን ቻናል ይቀላቀሉ፣  ለሌሎች ወገኖቻችንም ያስተዋውቁ

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም