የትምህርቱ ርዕስ | የውሳኔ ሰው

“የማትናከስ ከሆነ ጥርስህን አታሳይ ።” ስፔናውያን

በዚህ ዓለም ላይ ማንም ላይ አልደርስም ፣ ስለዚህ ክፉ አያገኘኝም ማለቱ ከንቱ ስሌት ነው ። ሰው ላይ መድረስ ደስ የሚላቸው ብዙ ሰዎች አሉ ። የተኛውን በሬ ቆስቁሰው ቆስቁሰው አውሬ የሚያደርጉ ፣ ዝምተኛውን እንደ መብረቅ የሚያስጮኹ ፣ መስመሩን ጠብቆ የሚጓዘውን ከመስመር የሚያስወጡ አያሌ ናቸው ። እነዚህ ሰዎች ባይኖሩ ኖሮ ሕግም መንግሥትም አስፈላጊ አይሆኑም ነበር ። ልንጠነቀቅ የምንችለው ሰዎችን ላለመንካት ነው ፣ እንዳይነኩን የምናደርገው ጥንቃቄ ላይሰምር ይችላል ። በዚህም ሁለት ነገሮችን እናስታውሳለን፡- የእግዚአብሔር ትእዛዝ እኛን እንጂ ሰዎቹን እያየ የተሰጠ አይደለም ። አትስረቅ እንጂ አይስረቁህ አይልም ። ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ እንጂ እንደ ራሳቸው ይውደዱህ አይልም ። የእግዚአብሔርን ቃል ለራሳችን ማንበብ እንጂ ለሰዎቹ ማንበብ ጥቅም የለውም ። ሁለተኛው ነገር እየበረረና መስመር ስቶ የመጣ መኪናን እየበረርን መስመር ስተን ብንጋጠመው አደጋው ሰው ለወሬ ነጋሪ የማይተርፍበት ነው ። አደጋውን ማስቀረት ባይቻልም መቀነስ ግን ይቻላል ። ከማንም ሰው ጋር ያለን ቆይታ አጭር ነው ። የዚህ ዓለም ዘመኖች በእርቦ የተሰፈሩ እፍኝ ናቸው ።

ሰዎች መስመራቸውን ጠብቀው የማይሄዱት የመጀመሪያው መስመራቸውን አለማወቃቸው ነው ። መስመራቸውን የሚስቱት የመጀመሪያ እኛ እግር እያላቸው እንዘላችሁ ፣ እጅ እያላቸው እናጉርሳችሁ በማለታችን ነው ። ሰዎችን ማንቀራበጥ ለጊዜው ደስ ይላል ። አቅማችን የተወሰነ ፍጡራን ነንና አንድ ቀን ይደክመናል ። የለመዱትን ያጡት ቅምጥሎቻችን እንደ መብት ይጠይቁናል ። እኛው መስመሩን አበላሽተንባቸው እኛው እንበሳጫለን ። ለግንኙነቶቻችን መበላሸት የመጀመሪያ ተጠያቂዎቹ እኛ ነን ። ብላታ ወልደ ጊዮርጊስ፡- የሰው ዘፋኝ ተጫውቶ በመጨረሻ ገንዘብ አምጡ በማለቱ ደስታን ይቀንሳል ። ቢከለክሉት ይሳደባል ።።

ሰዎች መስመራቸውን ጠብቀው የማይሄዱት በአስተዳደጋቸው ያልተገሩ ሆነው ሊሆን ይችላል ። ሰዎች የሚኖሩት የአስተዳደጋቸውን ውጤት ነው ። አስተዳደጋቸውን ደጋግመው ይኖሩታል ። በጊዜ ሂደት እንደተጣመሙ በጊዜ ሂደትም ሊቃኑ ይችላሉ ። አማካሪ እቤቱ ፣ ሐኪምም እመኝታው ክፍል ሳይሆን ሥራው ቦታ ያክማል ። ያልተገሩ ሰዎችንም ወደ ኑሮአችንና ወደ ትዳራችን አካባቢ አምጥቶ መግራት ዋጋ ሊያስከፍል ይችላል ። ስፍራና ጊዜ መድበን ማነጽ ግን መልካም ነው ። አንድ ሰው መልካምነትን ገንዘብ ሲያደርግ ከዚህ በኋላ ለሚያገኙት ሰዎች መልስ እንጂ ጥያቄ እንዳይሆን እናደርገዋለን ። እኛ ዋጋ ከፍለን ሰዎቹን እናሳርፋለን ። ከሁሉ በላይ ያንን ሰው በማትረፋችን እግዚአብሔር ይደሰትብናል ። ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ፡- “አንተ ከሥጋና ከነፍስ መከራ ስትድን ከምትደሰተው በላይ እግዚአብሔር በመዳንህ ይደሰታል።”

ሰዎች መስመር የሚስቱት በአእምሮ መዛባት ሊሆን ይችላል ። በሱስ ውስጥ ካሉ ፣ በኃጢአት እስራት ከተተበተቡ መስመር ይስታሉ ። ኃጢአት ከእኛ ፣ ከሰዎችና ከእግዚአብሔር የሚጠበቀውን እንዳናውቅ ያደርጋል ። ቢሆንም አህያ ረገጠን ብለን ፈረስ መሆን አይገባንም ። “ከለማበት የተጋባበት” እንዲሉ ። ሰዎች መስመራቸውን ስተው መስመራችንን የሚያውኩት ሊቋቋሙት ያልቻሉት ቅናት ስላሳበዳቸው ሊሆን ይችላል ። በዚህ ዓለም ላይ እንደ ቀናተኛ የተቸገረ የለም ። የሚረዳው የእርዳታ ድርጅት ግን እስካሁን አልተቋቋመም ።

የሊባኖሱ ፈላስፋ ካህሊል ጅብራን፡- “አዋቂ ሰው ሁለት ልብ አለው ፤ አንዱ ሲደማበት በሁለተኛው ይታገሣል” ብሏል ። ላለመጎዳት ጥንቃቄ ማድረግ ይገባናል ። የተወረወረው ጦር ሥጋችንን እንዳይነካ መከላከል አንችል ይሆናል ፤ ልባችንን እንዳይነካ ግን በጸሎትና በእውቀት መከላከል ይቻላል ።

በዚህ ዓለም ላይ ስንኖር ረባሾችን በብዙ መንገድ ማስታገሥ ይቻላል ። የመጀመሪያው የጸጋ መንገድ ነው ። እግዚአብሔር ሰባት ቢሊየን ሕዝብን ተሸክሞ እኔ አንድ ሰው ብሸከምለት ተገቢ ነው በማለት መቻል ቀላል ነው ። ሁለተኛው የሕግ መንገድ ነው ። ሕግ በዓለም ላይ ገደብ እንጂ ፍቅር አይሰጥም ። ሦስተኛው በተሰጠን ሥልጣን መጠን ክፉዎችን ማስታገሥ ነው ። ብዙ ጊዜ መንግሥት ትዕግሥተኛ ሁኖ ነው ይላሉ ። መንግሥት ሥራው መታገሥ ሳይሆን ሕግ ማስከበር ነው ። የሚታገሥማ የተበደለ ነው ። አባት ፣ መምህር ፣ ንጉሥ የማያደርጉትን ነገር ከመናገር ዝም ቢሉ ይሻላቸዋል ። አደርጋለሁ ያሉትን ሲያደርጉ በሚያስተዳድሯቸው ዘንድ ክብር ያገኛሉ ። ቢሆንም የአባትም ፣ የመምህርም ፣ የንጉሥም ሥልጣን የተገደበ ነው ።

ዝምታ የማይፈታ ቅኔ ነው ፣ ሊቃውንት አይደርሱበትም ። ዝምታ እንደ ፈላስፋ እንድንታይ የሚያደርግ ነው ፣ ሰዎች አይንቁትም ። ዝምታ የተከፈቱ አፎችን የሚያዘጋ ነው ፣ ተሳዳቢዎች አይዳፈሩትም ። ዝምታ ሁልጊዜ መልካም አይደለም ። ዝምታ በውስጡ እግዚአብሔርን መጠበቅ ሲኖርበት ኃይል አለው ። ላይቀጣ የሚፎክር አባት ፣ ላይገዝት ዋ የሚል መምህር ፣ ሕግ ላያስከብር ሕግ የሚተነትን ንጉሥ ይናቃሉ ። ብቻ ስፔናውያን፡- “የማትናከስ ከሆነ ጥርስህን አታሳይ” ብለዋል ። አባቶች ይወስናሉ ፣ ውሳኔአችን የት ደረሰ ካላሉ ፣ መምህራን ያስተምራሉ ፣ ትምህርቴ ምን እያፈራ ነው ብለው ካልመዘኑ አደገኛ ነው ። ሁልጊዜ ፎካሪ ፣ ሁልጊዜ ዋ ባይ ሆነን ከመናቅ ዝም ማለት ያስከብራል ። ሥርዓት አልበኞች አፋችንን ሳይሆን ልባችንን ያደምጣሉ ። ውሳኔአችንን አሊያም ዝምታችንን ይፈራሉ ።

ጥርሳችን መንከስ ፣ ውሳኔአችን መከበር ሲጀምር መስመር የሳቱ ሰዎች ወዲያው ዝቅ ይላሉ ። ዝቅታው ግን የመለወጥ ሳይሆን ስሜታችን እስኪበርድ ነው ። ስሜታውያን ሳይሆን እውነታውያን መሆናችንን ሲያረጋግጡ መስመራቸውን ይይዛሉ ።

አቤቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የቀናውን መንገድ ምራን ።

የብርሃን ጠብታ 16
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥቅምት 19 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም