መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » የይሉኝታ ነዋሪ

የትምህርቱ ርዕስ | የይሉኝታ ነዋሪ

የስድብ ክፉ “አቅሙን አያውቅ” የሚለው ነው ። ሦስት ነገሮች ለኑሮአችን አስፈላጊ ናቸው፡- እነርሱም አቅምን ማወቅ ፣ በልክ መኖር ፣ በኑሮአችን መደሰት ናቸው ። አቅማችንን ባለማወቃችን ለታላላቅ ጭንቀቶች እንዳረጋለን ፣ በልክ ባለመኖራችን ልጆቻችንን ነገ የማይዘልቅ ነገር እናስለምዳቸዋለን ። በዚህ ምክንያት ለዛሬ ጭንቀት ፣ ለነገ ፍርሃት አለብን ። የምንኖረው በጎረቤት አቅም ሳይሆን በራሳችን አቅም ነው ። እነዚያ የሌላቸው እኛ ያለ ጸጋ አለ ። በሁሉ ነገር ሙሉ ፣ በሁሉ ነገርም ጎዶሎ አይደለንም ። ደስታ የሚመጣውን በመቀበል ሳይሆን የያዝነውን በመቀበል የሚገኝ ነው ። በእጁ የያዘው ቀሎበት ከምስጋና የጎደለ ብዙ ሰው አለ ። በርግጥ ከምንቀበለው የተቀበልነው ይበልጣል ። በልካችን መኖር ደስተኛ ያደርገናል ። ከጎረቤት ጋር መወዳደር የራሳችንን ኑሮ እንዳንኖረው ፣ በመንጠራራት መሬት እንድንለቅ ፣ ሳናውቀው ቀናተኛ እንድንሆን ያደርገናል ። ይሉኝታ ከአቅማችን በላይ በመኖር ፣ የነገውን በጀት ዛሬ ላይ እንድንበላው ያደርገናል ። የለኝም ማለት ሐፍረት የሚሆንብን ጊዜ ብዙ ነው ። የለውም እንዳይሉን አይገቡ ቦታ እንገባለን ። የሚያሳፍረውን ከማያሳፍረው መለየት አልቻልንም ።

ፈጥኖ ምላሽ መስጠት ብዙ ጊዜ ዋጋ ያስከፍላል ። ከተበሳጨን አለመናገር ፣ ስሜታዊ ከሆንን እሰጣለሁ ብለን ቃል አለመግባት መልካም ነው ። ስንበሳጭ ዓለም ሁሉ ተሳስቶ እኛ ብቻ እውነተኛ የሆንን ይመስለናል ። ብስጭት የራሳችንን ጉድለት ፣ የሰዎቹን መልካምነት ይጋርድብናል ። ስሜታዊ ስንሆንም ሁሉም ነገር ያለን መስሎ ስለሚሰማን እሰጣለሁ ብለን ቃል ለመግባት እንቸኩላለን ። አምጡ ስንባልም ከቦታው እንጠፋለን ፣ የስልክ ቍጥራችንን ቀይረን እንጠፋለን ። ይህ ሁሉ እግዚአብሔር ያላሸከመን ሸክም ነው ። ይሉኝታ ግን ካላሰብንበት እንድንውል ፣ በሌለን ነገር እሰጣለሁ ብለን ቃል እንድንገባ ያደርገናል ። ዓለምን ለመለወጥ የምናደርገውን ጥረት አቁመን ራሳችንን መለወጥ ያስፈልገናል ። እኛ ስንለወጥ ዓለሙ ይለወጣልና ። ከባለጸጋ ጋር ጽዋ መጠጣት ሥርን ይነቅላል ። በአቅም መኖር ብቻ ሳይሆን በአቅም መዋልም ያስፈልጋል ። እነዚያ ቀሏቸው የሚያደርጉትን እኛ ሥራችን ተነቅሎ እናደርገዋለን ። ልጆቻችን እንዲያዝኑልን ፣ የሚከፈልላቸው ዋጋ እንዲገባቸው ፣ ነገ ላይ ለወጡበት ቤት ራእይ እንዲኖራቸው በልካችን ማሳደግ ይገባናል ። የልጅን ፍቅር የምናተርፈው ብዙ በመስጠት አይደለም ። በገንዘባችን የገዛናቸው ሲመስላቸው ልጆች እየጠሉን ይመጣሉ ። ለዚህ ነው የድሀ ልጅ ወላጆቹን በጣም ሲወድድ የባለጠጋ ልጅ ግን ለወላጆቹ ግድ የለውም ። ሁሉንም ማለታችን አይደለም ።

በሕይወት ላይ ከእግዚአብሔርም ፣ ከሕሊናም ፣ ከገንዘባችንም የማንሆንበት ጊዜ አለ ። እርሱም በይሉኝታ የምናደርገው ነገር ነው ። የይሉኝታ አድራጎታችን በእግዚአብሔር ዘንድ ግብዝ ያሰኘናል ። በሕሊና ፊትም ውሸታም የሚል ስም ይሰጠናል ። የሆንነውን መሆን እንጂ ያልሆነውን እንደሆነው ለመምሰል መሞከር ከንቱ ነው ። ብዙዎች ያልሆኑትን ሲመስሉ ይሰነብታሉ ፣ ወደ ትዳር ሲገቡ ግን እውነተኛው ማንነት አልደበቅ እያለ ሰላም ያጣሉ ። ያኛው ሰውም ይህን ጠባይ እሸከመዋለሁ ብሎ ተዘጋጅቶ እንዲገባ ማስመሰልን ማቆም አለብን ። ሳያውቁ የወደዱን ፣ ሲያውቁን ከጠሉን በጣም ያሳፍራል ። ባለጠጋ ለመሆን መሥራት አንፈልግም ፣ ባለጠጋ መስለን ከተማ መዞር ግን እንፈልጋለን ። የቅብ ኑሮ ፀሐይ ሲወጣ የሚቀልጥ ነው ፣ ሳያውቁ ያከበሩን ለዘላለም ይንቁናል ። ፊታቸውን ሜካፕ የተቀቡ ኀዘናቸውን ለመግለጥ ማልቀስ እንኳ አይችሉም ። ከውስጥ ስሜታቸው ፣ ከደጅ ልፋታቸው እየታገላቸው በሽተኛ ይሆናሉ ። ይሉኝታ ስሜትን እንኳ እንዳንገልጥ ያደርገናል ፣ የቅብ ኑሮ ነውና ። የሚያስጨንቅ ስንት ነገር እያለ ጭንቀት የምንፈጥረው ለምን እንደሆነ ግራ የሚያጋባ ነው ።

የብድር ኑሮ አድካሚ ነው ። አብዛኛው ኑሮአችን ደስ ያለንን ማድረግ ሳይሆን ብድር መመለስ ላይ የተመሠረተ ነው ። የማንም አያልፍብኝም የሚል ንግግር አለን ። የእኛ ወደ እነርሱ ሊያልፍ የእነርሱም ወደ እኛ ሊያልፍ ይችላል ። ወዳጅነት ልብን መሰጣጠት እንጂ በቁስ የሚለካ አይደለም ። ወዳጅነት ቃል ኪዳን ነው ። ቢወድቅ ልናነሣው ፣ ቢሞት ልጆቹን ልናሳድግለት ግድ የሚለን ነው ። ወገኖቼ እባካችሁ አብሮ መብላት ቀላል አይደለም ። ይሉኝታ የብድር መመላለስ ኑሮ ውስጥ ይከተናል ። ለወዳጅ የሚሰጠው ትልቅ ስጦታ ገና አለና ባደረግነው መኩራት አይገባንም ። ክቡር ቃሉ እንዲህ ይላል፡- “ነፍሱን ስለ ወዳጆቹ ከመስጠት ይልቅ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር ለማንም የለውም።” ዮሐ. 15፡13።

ልብን ኩላሊትን በሚፈትን አምላክ ፊት አልዋሽም ብለን እውነተኛ ኑሮ መኖር ይገባናል ። የሕልውናችን መሠረት እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ሰው የሕይወታችንን መብራት ለማብራትም ለማጨለምም ድርሻ የለውም ። የእኔ ሕይወትና የእኔ ጉዳይ በእግዚአብሔር እጅ ነው ብለን በእምነት መኖር ይገባናል ። ዕለታዊ ኑሮአችን የይሉኝታ እስረኛ ነው ። ሰዎችን በጣም እንፈራለን ። ተረታችንም፡- “ይሉሽን ብታውቂ ገበያ ባልወጣሽ” የሚል ነው ። ሰዎችን እኛ የምንላቸው ፣ በሕሊናችን የሰጠናቸው መልክ አለ ፣ ሰዎችም እኛን የሚሉን ነገር አለ ። የምባለውን አላውቅምና ገበያ አልወጣም ካለች በረሀብ መሞትዋ ነው ። ሰዎች መልካም ቢሉን መልካም ፣ ክፉ ቢሉን ክፉ አንሆንም ። የምንሆነው የሆነውን ነው ። ደግሞም ትርፉም ኪሣራውም የእኛው ነውና ሰዎች ለሚሉን ነገር መጨነቅ አይገባንም ። ስመኛ አገርና ዘመን ሲገጥመን ንቀን መኖር ይገባናል ። ወረኞችን የሚያነግሣቸው የሰጠናቸው ጆሮ ነው ። በልባችን ዋጋ ሊኖራቸው የሚገባው የሚጸልዩልን ሰዎች ብቻ ናቸው ። የሚሸፍኑንን ትተን የሚገልጡንን ማክበር ነውር ነው ። ይሉኝታ ከግለሰብ ወደ አገር የሚያድግ ነውና ልንጠነቀቀው ይገባል ።

እግዚአብሔር ከይሉኝታ ሰንሰለት ይፍታን !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 17 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም