የትምህርቱ ርዕስ | ውኃ አጠጪኝ

“ከሰማርያ አንዲት ሴት ውኃ ልትቀዳ መጣች። ኢየሱስም፦ ውኃ አጠጪኝ አላት” /ዮሐ. 4፥7/ ።
በጌታችን ሰው መሆን ከሚያስደንቁ ነገሮች አንዱ ሰጪው ለማኝ መሆኑ ነው። ከእናቱ ድንግልናዊ ወተትን እየለመነ ያደገው ጌታችን አሁን ደግሞ ውኃ አጠጪኝ በማለት ሳምራዊቷን ሴት ለመነ ። በዚህ ዓለም ላይ ውኃ ርካሽ ነገር ነው ። እግዚአብሔር እንደ ውኃ ያበዛው ነገር የለም ። ውኃን አብዝቶ የሰጠን ለመታጠብ እንዳንሰስት ነው ። በመካከለኛው ምሥራቅ ውኃ ተለምኖ የሚጨክን ሰው የለም ። እንደውም ሰው ሊጠማው ይችላል ተብሎ ቀዝቃዛ ውኃ ከነመጠጫው ደጅ ላይ ይቀመጣል ። መንገደኛውም ቀድቶ እየጠጣ ያልፋል ። እነዚያ ሕዝቦች የሚያስቡት ውኃ የእግዚአብሔር ስጦታ ነው ብለው ነው ። ጌታችንም ይህን ቃል ደግሞታል፡- “የእግዚአብሔርን ስጦታና፡- ውኃ አጠጪኝ የሚልሽ ማን መሆኑንስ ብታውቂ፥ አንቺ ትለምኚው ነበርሽ የሕይወትም ውኃ ይሰጥሽ ነበር አላት” /ዮሐ. 4፥10/ ። ውኃ የእግዚአብሔር ስጦታ ነው ። በአገራችንም ውኃ የሬሣ ማጠቢያ ነው ይባላል ። እንኳን ለቆመ ለሞተም አይከለከልም ማለት ነው ። የጎንደር ሰው “ለውኃ ለውኃ ምን አደረገኝ ቀሃ” ይላል ። የቀሃ ወንዝን እያስታወሰ የሚናገረው ነው ። ጌታችን በሕይወት ዘመኑ ሁለት ጊዜ ውኃ እንደ ለመነ ተጽፏል ። የመጀመሪያው በያዕቆብ ጉድጓድ አጠገብ ሲሆን ሁለተኛው በመስቀል ላይ “ተጠማሁ” በሚለው ጩኸቱ ነው ። ሁለት ጊዜም ውኃ አላገኘም ። ውኃ የእግዚአብሔር ስጦታ ነው ብሎ የሚያስበው ማኅበረሰብ ጌታችን ሲለምነው ለመስጠት ፈቃደኛ አልነበረም ። ጌታችን እንኳን የአምላክነቱን አይደለም የሰው ልጅን ያህል እንኳ አቀባበል አላገኘም ። ትንሽ የሚመስለውን ነገር ለተነፈጉ ቤዛ ሊሆናቸው ትንሹንም ትልቁንም ጥቅም አጣ ።
ሁለቱንም ጊዜ ከውኃው በላይ የተጠማው የሰዎቹን መልካምነት ነው ። ሳምራዊቷ ሴት ካመነች በኋላም ውኃውን አልጠጣም ። በመስቀል ላይም በውኃው ፈንታ ሆምጣጤ ቢያቀርቡለት አልጠጣውም ። ውኃን ለመስጠት ዘርን ጎሣን የሚያስጠይቅ ማንነት በሳምራዊቷ ሴት ነበረ ። ውኃን ለለመነ ሆምጣጤ የሚያቀርብ ማንነት በሰቃዮች ውስጥ ነበረ ። ከስጦታው በላይ ስጦታው የሚወጣበት ልብ እንዲቀደስ ጌታችን ፈለገ ። ልባቸው ቢቀደስ ለውኃ ብቻ ሳይሆን ሕይወታቸውን ለመስጠትም አይሰስቱም ። የመጨረሻውን ስጦታ የዘላለም ሕይወትን የሚሰጠው ጌታችን የመጨረሻውን ትንሽ ስጦታ ውኃን ለመነ ። ውኃን የለመነባቸው ሰዓቶች በሰማርያ ደክሞ ፣ በመስቀል ላይ ታሞ ነው ። ከግለሰብ እስከ ሕዝብ ፣ ከሳምራውያን እስከ አይሁዳውያን ውኃን ነፈጉት ። ራሱ የፈጠረውን ውኃ ተነፈገ ። ያልፈጠርነውን ቢነፍጉን ታዲያ ለምን ደነቀን ?
   ጌታችን ይህችን ሴት ብዙ መንገድ ተጉዞ ፣ በሐሩር ተቃጥሎ ፣ በብርቱ ደክሞ ሊያገኛት መጣ ። ምሥጢሯን እንዳይሰሙ ደቀ መዛሙርቱን የማይበላውን ምግብ እንዲገዙ ወደ ከተማ ላካቸው ። ደቀ መዛሙርቱ የመጡት ይህች ሴት አምና ለምስክርነት ልትሰማራ ስትል ነው ። ምን ያህል ሰዓት እንደሚያናግራት ያውቅ ነበር ። ይህን ሁሉ የሕሊና ጥበቃ ካደረገላት በኋላ አሁን ደግሞ እንዳትደናገር ውኃ አጠጪኝ አላት ። በውኃ ጉድጓድ አጠገብ የውኃ ጥያቄ ማንሣት የሚያግባባ ርእስ ነው ። ጌታችን ትልቅ የስብከት ዘዴ እንደ ተጠቀመ እንረዳለን ። የስብከት ዘዴ ማለት ከሚያግባባው ርእስ መነሣት ማለት ነው ። የሰውን ሕሊናና ክብር ጠብቆ ለንስሐ ማብቃት ፣ በመራራት ሰዎችን ማከም ማለት ነው ። ሰዎች ሕይወታቸውን የሚመለከት ርእስን አይወዱም ። ይህን ርእስ በሚመለከት እንኳን ከሰባኪ ከራሳቸውም እየሸሹ ነው የሚኖሩት ። የሚወዱትም ትምህርት ሕይወትን የማይመለከት በገንዘባቸው ብቻ መልስ የሚሰጡበትን ሙገሳና ድለላ ያለበትን ነው ። እንደ ነቢይ ፣ እንደ ፈዋሽ የሚያደርጋቸው ሰዎች ብዙ ተከታይ ሲኖራቸው ፣ ወንጌል የሚሰብኩት ግን ሌጣ የሚሆኑት ለዚህ ነው ። ሰይፍ እንደ ያዘ እብድ የሚያስፈራራ ሰባኪም ዘዴን ከጌታችን መማር አለበት። ሰው ማለት ነጻ ፈቃድ ያለው ፤ ለባዊት ፣ ነባቢትና ሕያዊት ነፍስን የተቀዳጀ ፣ በአምላክ የፍርድ ዙፋን ፊትም ራሱን ችሎ የሚቆም ክቡር ፍጥረት ነው ። ይህንን ሰው  እንደ እንስሳ ንቆ ፣ እንደ ጣዖት ፈርቶ ሳይሆን እንደ ሰው አክብሮ ማነጋገር ይገባል ። ስብከት ማለት ሰውን በፈቃዱ የምንማርክበት መለኮታዊ መሣሪያ ነው ። እንኳን በግልጽ አዋርደናቸው ይቅርና የሌላውን ንስሐ ለትምህርት ማጣፈጫ ስንጠቀም ሰሚዎቹ ይሰጉናል። ይልቁንም ያለንበት ዘመን የሰዎች አእምሮ በብዙ የሕሊና ትግል ውስጥ የሚያልፍበት ፣ በሕመምና በጭንቀት የተጎዱበት በመሆኑ በጥንቃቄና በፍቅር ልናክማቸው ይገባል እንጂ በጭካኔ ቊስላቸውን ልንነካቸው አይገባም ። “እናትና ልጅ ሲጣሉ ሞኝ እውነት ይመስለዋል” ይባላል ። እግዚአብሔርና ሰውም በጣም ይዋደዳሉና ሲጣሉ እንደ ሞኝ ልናስብ አይገባም ። ነቢዩ ዮናስ የእግዚአብሔርን ምሕረቱን ብቻ ማሰቡ ፍርዱን እንዳስረሳው ፣ እኛም ፍርዱን ብቻ ማሰብ ምሕረቱን እንዳያስረሳን መጠንቀቅ አለብን ። “ካነጋገር ይፈረዳል ካያያዝ ይቀደዳል” የሚባለው ለዚህ ነው ። ንግግር ራሱን የቻለ ጥበብ ይፈልጋል ። ጥበብ ውሸት አይደለም ። ለማን ምን መናገር ፣ እንዴት መናገር እንዳለብን የምናውቅበት ነው። ቀጥሎ ያለውን ንግግር እስቲ ምረጡ ፡-
–    ጫማው ትንሽ ስለሆነ አይበቃዎትም ።
–    እግርዎት ትልቅ ስለሆነ ጫማው አይበቃዎትም ።
 አንድ ጫማ መሸጫ ሱቅ ውስጥ ገብታችሁ የሰማችሁት ድምፅ ነው ። የሁለቱም አሳብ አንድ ዓይነት ነው ። የምትቀበሉት ግን የቱን ንግግር ነው ? አነጋገር ወሳኝ ነው ።
 ይልቁንም ስብከት ማለት ሰውና እግዚአብሔርን ማስታረቅ ማለት ነው ። ሰው የበዳይ አኩራፊ ሁኖ ተቀምጧል ። እግዚአብሔር ደግሞ ከልጄ አስታርቁኝ ብሏል ። አስታራቂ ሰው ሽማግሌ ነውና ጠንቃቃ ፣ ንግግር አዋቂ መሆን አለበት። አሊያ አባትና ልጅን አለያይቶ ሊቀር ይችላል ። በስብከት ያመኑትን ያህል የካዱም አይጠፉም ። ጌታችን ጸሎትን በአቡነ ዘበሰማያት ካስተማረ ስብከትንማ በጣም መማር ይገባናል ። “ከመጠምጠም ትምህርት ይቅደም” የሚባለው ለዚህ ነው ። ትምህርት ለምን ይፈራል ? የቀደሙትን አገልጋዮች መጠየቅ ለምን ይሸሻል ? ልብ አድርጉ የስብከት ዘዴ ማለት የኑሮ ዘዴ ማለት አይደለም ። ካልደፈረሰ አይጠራም የሚል ንግግር ትክክል አይደለም ። ሰው ያደፈረሰው አይጠራምና ።
   ጌታችን በወቅቱ ከሚያግባባው ርእስ ከውኃ በመነሣት ትልቅ የስብከት ጎዳናን አሳየን ። ይህች ሴት ከዚህ በፊት አይታው የማታውቀው ፣ የአለባበሱ ሁኔታ አይሁዳዊ የሚመስል ሰው በማየቷ መደንገጧ እርግጥ ነው ። የንግግሩ መክፈቻ ግን የሚያግባባ በመሆኑ ድንጋጤዋ ወደ መገረም ተለወጠ ። ወገኖቼ ሳምራውያን እንኳ እኔ ባጠለቅሁበት አይቀዱም ፣ እርሱ አይሁዳዊው እንዴት በእኔ ማጥለቂያ ውኃ ይጠጣል ? ወደሚል አግራሞት ተሻገረች ። ሕሊናን የፈጠረው የሕሊናን ምቾት ይጠብቃል ። ጌታም በብዙ ትዕግሥት እምነትዋን አሳደገላት ።
የሚፈለገው ጌታ በመፈለግ መጣ ። የሚጠየቀው ጌታ ጥያቄዋንና መልሷን ይዞ ተገለጠ ። የሚሰጠው ጌታ በልመና ጀመረ ። ፍጻሜው ምን ሆነ?
–    በልመና የጀመረው ግንኙነት የዘላለምን ሕይወት በመስጠት ተደመደመ።
–    በውኃ የጀመረው ርእስ መሢሕና መድኃኔዓለም በማለት ተፈጸመ ።
–    አንዲትን ሴት በመማረክ መላው ከተማ ተማረከ ።
–    በሚያስጠማው ውኃ የሸሿት ሳምራውያን በሕይወት ውኃ ግን ተከተሏት።
–    አንድ ጽዋ ውኃ ለመስጠት የተከራከረች እንስራዋን ጥላ ሄደች ።
ትንንሽ የሚመስሉ ግንኙነቶች ትልቅ በረከት ይወጣቸዋል ። ትንንሽ የሚመስሉ ርእሶች የዘመናትን እንቆቅልሽ ይፈታሉ ። ትንንሽ የሚመስሉ ሰዎች ለብዙዎች መዳን ምክንያት ይሆናሉ ። ትልቅነታችን የማያግዘው ፣ ትንሽነታችን የማይመልሰው ጌታ ስሙ ይመስገን !!
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም