የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

የሕይወት ውኃ

“ኢየሱስም መልሶ፦ ከዚህ ውኃ የሚጠጣ ሁሉ እንደ ገና ይጠማል፤ እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ሁሉ ግን ለዘላለም አይጠማም፥ እኔ የምሰጠው ውኃ በእርሱ ውስጥ ለዘላለም ሕይወት የሚፈልቅ የውኃ ምንጭ ይሆናል እንጂ አላት” /ዮሐ. 4፥13-14/ ።
ሳምራዊቷ ሴት ለጌታችን መቅጃ የለህም የሚልና ከአባታችን ከያዕቆብ ትበልጣለህን ? የሚል ሁለት ጉዳዮችን አነሣች ። ጌታችን ግን የሰጣት ምላሽ የሕይወት ውኃን የሚያብራራ ነበር ። እርሱ ንግግሩ ፍሰት ስላለው በየስላቹ አይቀርም ። ይናገራል ፣ የተናገረውን ይተረጕማል ፣ ከሕይወት ጋር ያዛምዳል ፣ በረከትን ይሰጣል ። ባዶ እጁን መሆኑን አይታ መቅጃ የለህም በማለት ቊሳዊ ነገር እንደሌለው ተናገረች ። ዕድሜውንም በማየት ከአባታችን ከያዕቆብ ትበልጣለህን ? በማለት ወጣትነቱን ገመገመች ። እርሱ ግን መቅጃ የለውም ፤ ነገር ግን ዓለሙን በእጁ የያዘ ነው ። እርሱ በሥጋ አሁን ቢገለጥም ከያዕቆብ በፊት የነበረ ነው ። እንደውም ያዕቆብን በያቦቅ ወንዝ ያገኘውና ያረጋጋው ነው ። ጌታችን በዚህ በያዕቆብ ጕድጓድ አጠገብ ላይ ሲገኝ ይህን ጕድጓድ የቆፈረውን ያንን ያዕቆብን አስታውሷል ።
ያዕቆብ ብዙ ጊዜ በአታላይነት ይጠቀሳል ። ሲወለድ የወንድሙን ተረከዝ በመያዙ ፣ በምስር ወጥም የወንድሙን በረከት በመውሰዱ ፣ አባቱንም ዔሳው ነኝ በማለት ምርቃትን አታልሎ በመውሰዱ ይታወቃል ። ያዕቆብ ወንድሙን ፈርቶ ወደ አጎቱ ወደ ላባ ወደ ሶርያ ምድር ተሰደደ ። በዚያም አጎቱ ሁለት ጊዜ አታለለው ። ያዕቆብም ለሃያ ዓመታት ያህል በአጎቱ ቤት በመታለል ኖረ ። አሁን ግን ብዙ ልጆች ተወልደውለት ፣ ሀብቱ በዝቶለት ወደ ትውልድ አገሩ ተመለሰ ። ያዕቆብ ምግብና ልብስ ቢኖረኝ በማለት ተስሎ ነበር ። እግዚአብሔር ግን ከዕለት ፍላጎት አልፎ ብዙ ሀብትን ሰጠው። ያዕቆብ 12 ልጆች ተወልደውለታል ፣ ሁለት ሚስቶች ራሔልና ልያ አብረውት አሉ ። ከብቶቹና ንብረቱም ሜዳ የሚሞሉ ነበሩ ። ነገር ግን የኖረለት ነገርና ያገኘው እርካታ አነሰበት ። ወንድሙን ያጣበት ፣ ከአባቱ ቤት የኮበለለበት ፣ ከቤት ወጥቶ የማያውቅ ልጅ ስደተኛ የሆነበት ያ ሁሉ ልፋት ለዚህ ነው ወይ ? በሚል ጥያቄ ባዶ ሆነበት ። ውስጡ ዛለ ፣ የሞተ መንፈሱን ሥጋው መሸከም አቃታት ። ልጆቹንና ሚስቶቹን እንዲሁም ከብቶቹን አሻግሮ እርሱ ግን በያቦቅ ወንዝ ዳርቻ ብቻውን ቀረ ። ሌሊቱን በሙሉ ለመተከዝና ብቻውን ለማልቀስ ፈለገ ። ወንድሙ ዔሳው ስጋቱ ነው። አሁን ሮጦ ለማምለጥ የማይችል በልጆች የታጠረ ነው ። እግዚአብሔር ግን በዚያች የትካዜ ሌሊት ያዕቆብን አገኘው ። ያዕቆብም እግዚአብሔርን መልቀቅ ስላልቻለ ሌሊቱን በሙሉ ሲታገል አደረ ። ልቀቀኝ ቢለውም ያዕቆብ ግን ካልባረከኝ አልቅህም አለው ። ያዕቆብ ሚስቶች ፣ ልጆች ፣ ከብቶች አሉት ። እነዚህ በረከቶች አይደሉም ወይ ? ብንል ያዕቆብ እነዚህ ሁሉ ዕረፍት አልሰጡትም ። በረከት ሰማያዊና መንፈሳዊ መሆኑን ተረድቷል። እነዚህን ነገሮች እስኪያገኝ ያዕቆብ የመጨረሻ ልመናው ይህ ነበር ። ካገኘ በኋላ ግን ሌላ በረከት እንዳለ ገባው ። ስለዚህ ካልባረከኝ አልለቅህም አለ ። እሞትብሃለሁ ፣ ከዚህ በላይ መቆየት የሚችል አቅም የለኝም ማለቱ ነው ። እግዚአብሔርም በዚያች ሌሊት ስሙን እስራኤል ብሎ ለወጠለት ። ያዕቆብ መንፈሳዊ ነገርን በጥልቀት ያስተዋለበት ሌሊት ነውና ስሙ ተለወጠ ።
ያዕቆብም ተባረከ ። ነገር ግን ከትግሉ የተነሣ ያዕቆብ ያነክስ ነበር ። ነገር ግን ፡- “እግዚአብሔርን ፊት ለፊት አየሁት ሰውነቴም ድና ቀረች” አለ /ዘፍ. 32፥30/ ። እያነከሱ ድኖ መቅረት አለ ወይ ? ብንል ያዕቆብ መንፈሱ ዕረፍት ሲያገኝ የእግሩን ማንከስ ረሳው ። የረካ መንፈስ የሚያነክስ ሥጋን መሸከም ይችላል ።
ጌታችን በዚህ በያዕቆብ ጕድጓድ አጠገብ ስለ እርካታ መናገሩ በእውነት ድንቅ ነው ። ያዕቆብ በዚያ ሌሊት የታገለው ከእግዚአብሔር ወልድ ጋር ነው። በነቢዩ በሆሴዕ፡- “በማኅፀን ውስጥ ወንድሙን በተረከዙ ያዘው፥ በጕልማስነቱም ጊዜ ከአምላክ ጋር ታገለከመልአኩም ጋር ታግሎ አሸነፈ አልቅሶም ለመነው። በቤቴልም አገኘው፥ በዚያም ከእኛ ጋር ተነጋገረ።እርሱም የሠራዊት አምላክ እግዚአብሔር ነው የመታሰቢያው ስም እግዚአብሔር ነው”ይላል /ሆሴዕ.12፥4-6።
ሴቲቱ አላወቀችምና አንተ ከአባታችን ከያዕቆብ ትበልጣለህን ? አለችው ። ያዕቆብን ያረካው ጌታ ሊያረካት መጥቶ ነበር ። እርስዋም አምስት ባሎች ዕረፍት ሊሰጧት አልቻሉም ። ሙከራ ያደከማት ሴተ ናት። እቤት ያስቀመጠችውንም ባል ያልሸኘችው ስድስተኛውም ያው ነው ብላ ይመስላል ። አምስተኛውን ባል ከመባረር ያዳነው የእርስዋ መሰልቸትና ሁሉም ነገር ድግግሞሽ ሆኖ ስለታያት ነው ። ከውኃ ጥያቄ በላይ የነፍስ ጥያቄ አለባት ። “ኢየሱስም መልሶ፦ ከዚህ ውኃ የሚጠጣ ሁሉ እንደ ገና ይጠማል፤ እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ሁሉ ግን ለዘላለም አይጠማም፥ እኔ የምሰጠው ውኃ በእርሱ ውስጥ ለዘላለም ሕይወት የሚፈልቅ የውኃ ምንጭ ይሆናል እንጂ አላት” /ዮሐ. 4፥13-14/ ።
ይህ ውኃ ሲል የእርስዋ ሙከራና እርካታን የፈለገችበት መንገድ ነው ። ያ መንገድ የሰው መንገድ ነው ። ይህን ባገኝ እረካለሁ የሚለው የሰው ምኞት ነው ።  ሰው የቆፈረው ጕድጓድ መልሶ ያስጠማል ። ጥያቄው መልስ ካገኘ በኋላ መልሱ ጥያቄ ይሆናል ። የሰው ዓለም ምኞት እስኪሆን መቅበዝበዝ ፣ ከሆነ በኋላ እንደገና መመኘት የሞላበት ፣ ፍለጋ የማያልቅበት ፣ ሕልምና ፍችው የተሰወረበት ነው ። ዛሬም በኑሮው ከተደሰተ ያዘነ ፣ በእሴቱ ካመሰገነ የተማረረ ይበዛል ። የሰው ልብ ሁልጊዜ መንገደኛ ነው ። ወደቡን አያውቀውም ሁልጊዜ ቀዛፊ ነው ። እፎይ የሚያሰኘውን ሕይወት የሚሰጠው ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው ። ያ የሚያረካው ምንጭ ነው ። የሚፈለግ ሳይሆን በሆድ ውስጥ የሚፈልቅ ነው ። ከውጭ ወደ ውስጥ የሚገባ ሳይሆን ከውስጥ ወደ ውጭ የሚፈስስ ነው ።
ጌታችን ፡- “ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነው” ብሏል /የሐዋ. 20፥35/። በገንዘብ ብቻ ሳይሆን በማንኛውም የሕይወት ገጽታ ከሚቀበል የሚሰጥ ደስተኛ ነው ። ፍቅርን ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ደስተኛ ነው ። ምንጩ ውስጣችን ሲተከል ወደ ውጭ መፍሰስ ብቻ ነው ። በመፍሰስ ውስጥ መርካትና ማርካት ፣ መጥራትና መንጻት አለ ። ሙከራ ወይም ድርጊት በሌለበት መሻሻል የለም ። የማይሳሳቱ የማይሠሩ ብቻ ናቸው ። መደናቀፋችን መራመዳችንን ይሳያል ። ከመቀመጫቸው የማይነሡ ሰነፎች አይደናቀፉም ። የሰው ልጅ እውነተኛው እርካታ የሚጀምረው ዘላለማዊ ጥያቄው ሲመለስ ብቻ ነው ። የነፍስ በረከት ለሥጋ ይተርፋል ፣ የሥጋ በረከት ግን ለነፍስ አይተርፍም በማለት የተነገረው ለዚህ ነው ።
ያዕቆብ ምድራዊውን ውኃ ለማግኘት ብዙ ደከመ ። ያ ምድራዊ ውኃ ግን መልሶ ያስጠማል ። ትግሉ የጀመረው ፣ የወንድምን ተረከዝ በመያዝ ገና ከማኅፀን ደጃፍ ላይ ነው ። ያዕቆብ ጭምትና ከቤት የማይወጣ ፈሪ በመሆኑ የኑሮ ስጋት ነበረበት ። ይህ የኑሮ ስጋቱ ለወንድሙ ረሀብ እንኳ እንዳይራራ አደረገው ። የፈለገውን ከፈለገው በላይ አገኘ ። በምኞት ትልቅ ሆኖበት የነበረው ነገር አሁን ሲጨብጠው ሊያረካው አልቻለም ። ጠማኝ የሚለው ጥያቄው አልረካሁም በሚል ከባድ ጥያቄ ተለወጠ ። ጠማኝ ተዳሳሽ ፍላጎት ነው ። ጠማኝ ለሚል ውኃ መስጠት ይቻላል ። ውኃ የሰጡን አልረካሁም ብንላቸው ውኃ ይጨምራሉ እንጂ እርካታ የሚባለውን መንፈሳዊ ነገር ሊሰጡን አይችሉም ። እርካታ መንፈሳዊ ነገር ነው ። ውኃ እንኳ ጠጥተን ከረካን ብዙ ጊዜያችን ነው ። በልጅነታችን ጠጥተን ስንረካ ይታወሰናል ። ዛሬም የያዕቆብ ጉዞ በብዙ የሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ ይደገማል ። ገና በጥዋቱ ከወንድም ከእህት ጋር መታገል ይጀምራል ። በአሻንጉሊት የተጀመረው መነጣጠቅ ፣ እኔን እቀፉኝ በሚል የተጀመረው ቅንዓት እያደገ ይመጣል ። የእኔ በረከት ያለው በእግዚአብሔር እጅ ነው ከማለት ወንድሜ ይዞብኛል ወደሚል አዙሪት ይቀየራል ። ወንድምን ለማጥመድና ለመጥለፍ ከምስር ወጥ እስከ ጸሎት ማሰናከያውን ያሳድጋል ።
ፍቅርን የተራቆትንበት ፣ በወንድማችን ሩጫ ላይ አፈር የደፋንበት ፣ በሥጋዊም በመንፈሳዊም መንገድ ወንድማችንን ለመጣል ያሴርንበት ነገር ሁሉንም ጨብጠን ስናየው ለዚህ ነበር ወይ ? ብለን ራሳችንን እንድንታዘበው ያደርገናል ። ለዚህች ዕድሜ ስንቱን ሆንን ። እግዚአብሔር ያለው ላይቀር ስንቴ ከእምነት ጎደልን ። ጤናችንን አጣን ፣ ጤናም አሳጣን ። በልባችን ዶለትን ፣ በአደባባይ ተካሰስን ። ያገኘነው የተዘጋጀልንን እንጂ የተጠበብንበትን አይደለም ። ያሳለፍነውን ዘመን ለመገምገም ጊዜ ካገኘን ይህችን ለማግኘት ወንድምን ፣ ጤናን ፣ ሃይማኖትን ማጣት ተገቢ እንዳልነበር እንረዳለን ። ዛሬም ጠያቂ ነን ። ቤት ተሠርቷል ፣ ትዳር ተበጅቷል ፣ ልጆች ተወልደዋል ፣ ሀብት ተይዟል ። አሁንም ልባችን መንገደኛ ፣ ውስጣችን ፍለጋ ላይ ነው ። ምክንያቱም መርካት በክርስቶስ ብቻ ነው ። ታዲያ ይህን እርካታ እንዴት ማግኘት ይቻላል ?
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ