መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የደካሞች ብርታት

የትምህርቱ ርዕስ | የደካሞች ብርታት

 

“የተቀጠቀጠን ሸምበቆ አይሰብርም የሚጤስን የጥዋፍ ክርም አያጠፋም።” 

ማቴ. 12 : 20 ።

በሸምበቆ ላይ ቅጥቃጤ ፣ በጥዋፍ ላይ እፍታ ሲጨመር ከባድ ነው ። ሸምበቆ ለወትሮ ደካማ ነው ። ጥዋፍም የማብራት አቅሙ ትንሽ ነው ። ሸምበቆ ምንም ነገር መሸከም አይችልም ፣ ጥዋፍም መላውን ቤት ማብራት አይችልም ። በሸምበቆ ምሰሶነት የሚሠራ ቤት ፣ በጥዋፍም መብራትነት የሚበላ እራት የለም ። በተፈጥሮአዊ ድካሙ ላይ ሸምበቆ ሲቀጠቀጥ ፣ በጥዋፍ አቅም ላይም ነፋስ ሲጨመርበት ጉዳቱ ከፍ ያለ ነው ። ሁሉም ሰው የሸምበቆ አቅም አለው ። አንዳንዶች ግን ቅጥቅጥ ሸምበቆ ናቸው ። ሁሉም ሰው በተፈጥሮ ደካማ ነው ፣ አንዳንዶች ግን ድካማቸው የተገለጠ ነው ። ሁሉም ሰው የጥዋፍ መብራት ነው ፣ አንዳንዶች የሚጤስ የጥዋፍ ክር ናቸው ። ቅጥቅጥ ሸምበቆን ማንም ተስፋ አያደርገውም ፣ ምክንያቱም ተሰንጥሮ ይወጋል ፣ አንዳንድ ሰዎችም የሕይወት ድካማቸው ሲወራ “እኔንም ልጄንም እንዳያበላሹ ፣ አገርንም እንዳይጎዱ መጥፋት አለባቸው” ይባላል ። ከእግዚአብሔር ቀድመን እንፈርድባቸዋለን ። ስህተታቸውን ጆሮ አልለመደውም ፣ ድካማቸውን ስልታዊ ቋንቋ አይሸፍነውም ። መራቆታቸው በአደባባይ ስለሆነ ልብስ መጣል አይቻልም ። ሞተው ማረፋቸውን ባናውቀውም “ምነው ሞተው ባረፉት” እንላለን ። ቅጥቅጥ ሸምበቆን የበለጠ የምንሰብረው እኛን እንዳይወጋን ብለን ነው ። አንዳንድ ሰዎች መወገድ አለባቸው የምንለው ለራሳችን ደኅንነት በማሰብ ነው ። ሸምበቆ ስብራቱ ይጠገናል ተብሎ ተስፋ አይደረግም ። አንዳንድ ሰዎችም ንስሐ ቢገቡም የሚነጹ አይመስለንም ። ንስሐ ገብተናል ፣ ይቅርታ ጠይቀናል ቢሉ እንኳ የልብ እየሠሩ ንስሐ አይገባንም ፣ ይቅርታም አይመጥነንም እንላለን ። 

የሚጤስ ጥዋፍን በእፍታ ወደ መብራትነት መመለስ ከባድ ነው ። እርገጡትና በደንብ አጥፉት ይባላል ። ሽታው ያውካል ፣ ዓይን ይመዘምዛል ። እንደ ገና ያበራል ተብሎ ተስፋ አይደረግም ። በእፍታ ከማብራት ፣ በእግር ማጥፋት ይቀላል ። አንዳንድ ሰዎች ስህተታቸው እምነትን የሚያሸንፍ ይመስላል ፣ ውድቀታቸው ንስሐ ያለው አይመስልም ። ጥፋታቸው ያውካል ። ችግራቸው እየተከተለ ያስለቅሰናል ። ከአጠገባችን እንዲርቁ ወይም ከአጠገባቸው ለመራቅ እንመኛለን ። እነዚህ ሰዎች ቢበረቱ የሚሆኑት የጥዋፍ መብራት ነው ። ጎበዝ የሚባሉትም ጉብዝናቸው የሸምበቆ ጉልበት ነው ። ንስሐ ቅጥቅጡን ሙሉ ሸምበቆ ፣ የሚጤሰውንም ክር የጥዋፍ ብርሃን ያደርገዋል ። ባንሰበርም ሸምበቆ ነን ፣ ባንጠፋም የጥዋፍ ክር ነን ። የሚሸከመን አምላክ እንፈልጋለን እንጂ ሌላውን ለመሸከም አቅም ያንሰናል ። ፀሐዩን ጌታ እንናፍቃለን እንጂ የጥዋፍ ብርሃናችን ዙሪያችንን አያሳየንም ።

እግዚአብሔር የሚያውቀን በሸምበቆነታችን ነው ። ሰይጣን ደግሞ በስህተትና በክስ ይቀጠቅጠናል ። እግዚአብሔር የሚያውቀን በጥዋፍ መብራትነታችን ነው ። ሰይጣን ደግሞ የሰውን አፍ ተጠቅሞ ያጠፋናል ። ብቻ ዓለም ሰባራ በሰንጣራ የሚስቅባት መድረክ ናት ። 

የአንዳንድ ሰዎች አቅም ቅጥቅጥ ሸምበቆ ነውና ተግሣጽን መቀበል እንኳ አይችልም ። የድሮ ልጅ በርበሬ ቢያጥኑትም ጠንካራ ነው ፣ ብረት አግለው ቢጠብሱትም የማይበገር ነው ። የአሁን ልጅ ግን በጥፊ የሚሞት ነው ። የገዛ ካልሲውን አጥቦ እጁ የሚወልቅ ነው ። ብዙ ቅጥቅጥ ሸምበቆዎች አሉ ። በተለመደውና በቆየው የማግባባት መንገዳችን ልናድናቸው አንችልም ። ብዙ ፍቅር ይፈልጋሉ ። ራርቶ የሚያክማቸው ይሻሉ ። የአንዳንድ ሰዎች ሁኔታ የሚጤስ ጥዋፍ ነው ። ከመጨረሻው የሚጀምር አምላክ ካልሆነ የሚችላቸው የለም ። ከእነርሱ ጋር ስንሆን ልቅሶአቸው ይረብሻል ። ብሶታቸው የራሳችንን ብሶት ይቀሰቅስብናል ። እነርሱን ከማድመጥ መሸሽ ይቀናናል ። ተናግረው የማይረኩ ይመስላሉ ፣ ቀኑን እንዳያጨልሙብን እንርቃቸዋለን ። እኛ ለስሜታችን ስንጨነቅ እነርሱ ግን በሞትና በሕይወት መካከል ይዋትታሉ ።

ለደካማ የሚሆን ልብ ያለው በሥጋ የተገለጠው የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። እርሱ ደካማን እንደሚወድና ታሪክን እንደሚለውጥ በቤተ ልሔም መወለዱ ፣ እስራኤልን ወዳሰቃየችው ግብጽ መሰደዱ ፣ በኃጢአተኞች ከተማ በናዝሬት ማደጉ ፣ ከቀራጮች ጋር አብሮ መብላቱ ፣ ከወንበዴዎች ጋር መሰቀሉ ምስክር ነው ። ምሥጢረ ሥጋዌ ለደካሞች ስለተከፈለው ዋጋ የሚናገር የምስኪኖች መጽናኛ ነው ።

ጌታ ቅጥቅጦችን አይሰብርም ። ተስፋ ላጡት ተስፋ ይሆናል ። የሚያስለቅሱ ወገኖችን አጠገቡ አድርጎ ያባብላቸዋል ። ለአልዓዛር በመቃብሩ ስፍራ ፣ ለኢየሩሳሌም በደብረ ዘይት ተራራ እንዳለቀሰ ለእነዚህም ብቸኞች ይራራል ። እንዴት ተበላሹ ? ብሎ ታሪክ አያጠናም ፣ ለምን ተበላሹ ? ብሎ ፍርድ ውስጥ አይገባም ። “እንዴት ልጠግናቸው ?” ይላል ። የደጎች ልብ ከሚችለው በላይ የደከሙ ፣ ጆሮ መስጠት የሚችሉ ሰዎች የማይችሏቸው ጉዳተኞች አሉ ። መድኃኔዓለም ግን የእነዚህ ሁሉ ተስፋ ነው ። 

ለሰው ያታከታችሁ ለክርስቶስ አትከብዱትምና ፈጥናችሁ ወደ እቅፉ ግቡ ።

አቤቱ ከአንተ ርቀን እኛነታችንን የጎዳነውን ወደ አንተ አቅርበን ።

የብርሃን መስኮት /1

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 29 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም