የትምህርቱ ርዕስ | የጊዜ ፈጣሪ

“ምናልባትም እየመረመሩ ያገኙት እንደ ሆነ፥ እግዚአብሔርን ይፈልጉ ዘንድ በምድር ሁሉ ላይ እንዲኖሩ የሰውን ወገኖች ሁሉ ከአንድ ፈጠረ” የሐዋ. 17፡26-27
አንድ ራሽያዊ፡- “ትንሽ ድግስ ነበረኝ” አለ ። “ምንድነው ?” ሲሉት “ሚስቴ ሠላሳ ዓመቷን ያከበረችበትን አሥረኛ ዓመት እያከበርን ነበር” አለ ይባላል ። ዕድሜ በቀደመው ዘመን ተጨምሮ ይነገር ነበር ። ባለንበት ዘመን ደግሞ ተቀንሶ ይነገራል ። ኖሮ አልኖርኩም ከማለት በላይ ክህደት የለም ። ዕድሜ የሚደበቀው የሠራሁበት ነገር የለም ብለን ስናስብ ነው ። እኛ ባንሠራም እግዚአብሔር ሠርቶልናል ። እርሱ ባይዋጋልን ኑሮ ይህን ዕድሜ ማግኘት አይቻለንም ነበር ። ዕድሜን የሚሰጥ እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ነገሥታትና ጠቢባን ፣ ደግሞም ባለጠጎች ሊሰጡት የማይችለውን ዕድሜ ካገኘን በጣም ዕድለኞች ነን ። ዕድሜ ለማግኘት ነገሥታትን ለምኑ ብንባል “ያለፈውን ዓመት ግብር ስላልከፈልህ አይሰጥህም” ይሉን ነበር ። ዕድሜን ለማግኘት ጠቢባንን ጠይቁ ቢባል “ተጨማሪ ጥናት ላይ ስለሆንሁ ልረዳህ አልችልም” ይሉናል ። ዕድሜን ለማግኘት ባለጠጎችን ለምኑ ብንባል “ባለፈው ስቀልድ አልሳቅህልኝም ፣ ስለዚህ መኖር አይገባህም” ይሉናል ። ዕድሜን በሰው ፊርማ ብናገኝ ለአንድ ለሁለት ጊዜ ይፈርሙልናል ። ከዚያ በኋላ በራቸውን ዘግተው የለሁም ብለው ይመልሱናል ። ዕድሜ የአንድ አምላክ ስጦታ ነው ። በዚህ ቀን ሥልጣን የማይስበው ፣ ገንዘብ የማይገዛው ፣ ጥበብ የማይጠራው ዕድሜ ስለተሰጠን ልናመሰግን ይገባናል ።
ሐዋርያው ጳውሎስ በአቴንስ ጉብኝቱ እንግዳ ነገሮችን አየ ። የአርዮስ ፋጎስ አደባባይ አዲስ እውቀትና መገለጥ አለኝ ብሎ የሚያስብ ሰው በነጻነት የሚናገርበት ሲሆን እንግዳ ነገርን ለመስማት የተራቡ ጆሮ ያላቸው ግሪካውያንም  ተከማችተው የሚሰሙበት ነው ። ሐዋርያው ጳውሎስም እኔም የምናገርለት ጌታ አለኝ ፣ የደረስኩበት ሳይሆን የደረሰልኝ ጥበብ አለ በሚል ድምፀት መናገር ጀመረ ። አቴንስ ብዙ ሺህ ጣዖታት ያሉባት ብቻ ሳትሆን “ለማይታወቅ አምላክ” የሚል ስም የተጻፈበት አዲስ መሠዊያም የታየባት ናት ። አዲስ አምላክ ሲገኝ ይህ መሠዊያ ይሰየማል ማለት ነው ። ብዙ አማልክት የአምልኮን ጥም አይቆርጡም ። እውነተኛውን አምላክ እስካላመለክን በማምለካችን ብቻ ደስታ አናገኝም ። ማምለካችን ብቻ ክብር አይሰጠንም ፣ የምናመልከው እውነተኛ አምላክ መሆኑን ማወቅ አለብን ።
ሐዋርያው የንግገሩ ማዕከል ሊመለክ የሚገባው ሁሉን የፈጠረ ፣ ዘመንን ያስጀመረ ዳግመኛም ሊፈርድ የሚመጣው ነው እያለ ነው ። ጣዖታት ግን የሰው እጅ ሥራ በመሆናቸው ፈጣሪነት የሌላቸው ፍጡራን ፣ ዘመንን ማስጀመር የማይችሉ ግዑዛን ፣ ሊፈርዱ የማይችሉ ድኩማን ናቸው ። ጣዖታት የምንሸከማቸው ፣ እግዚአብሔር ግን የሚሸከመን አምላክ ነው ። ሐዋርያው፡- “ምናልባትም እየመረመሩ ያገኙት እንደ ሆነ” ይላል ። ምርምሮችን አልነቀፈም ። በምርምሮች ግን ሁለት ነገሮችን አስተውሏል ። የመጀመሪያው ሰው አምላኩን ካላገኘ እረፍት የለውም ። ምርምር እረፍት አልባነት ነውና ። ሁለተኛው በምርምር የሚያገኙ ጥቂቶች ናቸው ፣ ምርምርም ስለ እውነተኛው አምላክ የማሳወቅ አቅሙ አነስተኛ ነው እያለ ነው ። በምርምር ውስጥ ምናልባት “አንድ ኃይል አለ” የሚሉ ሰዎችን ማግኘት ይቻላል ። ያ ኃይል ግን እግዚአብሔር መሆኑን ለማወቅና ለመገንዘብ የስብከት ድምፅ ያስፈልጋል ። እግዚአብሔር ከምርምር ይልቅ በመገለጥ የሚታወቅ አምላክ ነው ። እርሱን ለሚፈልጉት ሁሉ ራሱን ይገልጣል ። የአቴንስ ሰዎች የፍልስፍና ሰዎች ስለሆኑ ወደ እውነተኛው አምላክ መድረስ አልቻሉም ። ፍልስፍና በራስ መመራት ሲሆን እምነት ግን በእግዚአብሔር ፈቃድ መራመድ ነው ። የፍልስፍና መነሻው ምድር ሲሆን እምነት ግን ሰማያዊ መገለጥ ነው ። ፍልስፍና በራስ መተማመን ሲሆን እምነት ግን በእግዚአብሔር መደገፍ ነው ።
ሐዋርያው በመቀጠል፡- “እግዚአብሔርን ይፈልጉ ዘንድ በምድር ሁሉ ላይ እንዲኖሩ የሰውን ወገኖች ሁሉ ከአንድ ፈጠረ” ይላል ። ከአንድ ፈጠረ የሚለው በቀጥታ ከአንድ አዳም የተገኘን እንደሆንን የሚያስረዳ ነው ። ሐረጉ መብዛቱ እንጂ ሥሩ አንድ ነው ። ሁላችንም የአዳም ልጆች ነን ። በሁሉም እምነቶች አዳም መነሻ እንደሆነ ይነገራል ። ስለዚህ ይህ ዓለም ሰፊ ቤተሰብ እንጂ ብዙ ቤተሰብ አይደለም ። ወንድማማች እንጂ ባላጋራ አይደለም ። ከአንድ መፈጠርም ከአንዱ እግዚአብሔር መበጀትም ነው ። በዚያ ዘመን የነበሩ ሰዎች ሁለት አማልክት አሉ ብለው ያምኑ ነበር ። የሚታዩ ነገሮችን የፈጠረ ንዑስ አምላክ ሲሆን ረቂቅ ነገሮችን የፈጠረው ግን ዐቢይ አምላክ ነው ብለው ይናገሩ ነበር ። ይህ ዓለም ግን ሥርዓቱና መገናዘቡ አንድ አምላክ እንዳበጀው ምስክር ነው ። በአንድ ግዛት ውስጥ ብርሃን ፣ ነፋስ ፣ ሙቀት አሉ ። አይገፋፉም ። አንድ አምላክ ስለፈጠረን መገፋፋት አይገባንም ። እግዚአብሔር አምላክ የፈጠረን እርሱን እንድንፈልግ ነው ። ሰው አምላክን መፈለጉ በታሪክ ሂደቱ ያዳበረው ፣ ወይም ያስፈልገኛል ብሎ ያመነበት ሐቅ ሳይሆን ያለ እግዚአብሔር እንዳይኖር ሁኖ የተፈጠረ ነው ። ከብት ዕለቱን ተወልዶ ይቆማል ፣ ሰው ግን ይታቀፋል ። ከብት ፍቅር ባያገኝም አይጎዳም ። ሰው ግን ብቸኝነት መንገዱን ያዘገይበታል ። የሚያቅፈውና አለሁ የሚለው ግን እግዚአብሔር ነው ። መፈለግ ታላቅ ጥማት ነው ። መፈለግ አምልኮ ነው ። መፈለግ የምንፈልገውን ለማወቅ መጓጓት ነው ።
“የተወሰኑትንም ዘመኖችና ለሚኖሩበት ስፍራ ዳርቻ መደበላቸው ። ቢሆንም ከእያንዳንዳችን የራቀ አይደለም” ይላል ። የምንኖርበትን ቦታና ዘመን የመደበ እግዚአብሔር ነው ። ኢትዮጵያ ለመወለድ ለእግዚአብሔር አሳብ ያቀረበ የለም ። እኛን ከዚህ አገር ሲፈጥረን አልተሳሳተም ። እርሱ ቦታችንና ዘመናችንን የመደበ ነው ። የተወሰኑት የሚለው ቃል በእውነት ድንቅ ነው ። የተሰፈረ ዕድሜ ነው ያለን ። ያንን በጉልበታችን ማለፍ አንችልም ። እስከ መቼ እንደምንኖር አናውቅም ። አንዳንድ ነገሮች መሆን አለመሆናቸውን እርግጠኛ አይደለንም ። መሞታችን ግን እርግጥ ነው ። ከእርግጡ ነገር ጀምረን ማሰብ ብንጀምር ሁሉም ነገር ቀና ይሆን ነበር ። ቢሆንም ከእያንዳንዳችን የራቀ አይደለም ። ነገሥታት ሕዝባቸውን የሚያውቁት በነፍስ ወከፍ ሳይሆነ በጅምላና በቊጥር ነው ። እርሱ ግን ከእያንዳንዳችን የራቀ አይደለም ። እውነተኛው አምላክ ከእኛ ዓለም የራቀ ነው ብለው ያስተምሩ ነበር ። የእግዚአብሔርን ሰው መሆን መቀበል ያቃታቸው ቅዱሱ ጌታ ርኩስን ሥጋ ሊለብስ በፍጹም አይችልም ብለው በማመናቸው ነው ። በእነርሱ እምነት ሥጋ ግዙፍ በመሆኑ ርኩስ ነው ። እርሱ ግን ከሥጋችን ሥጋ ፣ ከነፍሳችን ነፍስ ነሥቶ ከእኛ ጋር የተዛመደ ነው ።
ዘመንን የሰጠና ፣ የዕድሜን ዳርቻ ያበጀ እርሱ ነው ። ዘመንን የሚሰጠንም እርሱን እንድናከብርበት ነው ። ስንኖር የተመጸወትነው ዕድሜ እንደሆነ ማሰብ አለብን ። ማንኛውንም ነገር ለማድረግ ስንነሣ ብኖርና እግዚአብሔር ቢፈቅድ ማለት አለብን ። ሐዋርያው ያዕቆብ፡- አሁንም፡- ዛሬ ወይም ነገ ወደዚህ ከተማ እንሄዳለን በዚያም ዓመት እንኖራለን እንነግድማለን እናተርፍማለን የምትሉ እናንተ ፥ ተመልከቱ ፥ ነገ የሚሆነውን አታውቁምና ። ሕይወታችሁ ምንድር ነው ? ጥቂት ጊዜ ታይቶ ኋላ እንደሚጠፋ እንፍዋለት ናችሁና ። በዚህ ፈንታ፡- ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም ይህን ወይም ያን እናደርጋለን ማለት ይገባችኋል።” በማለት አዝዟል ። ያዕ. 4፡13-15 ። እኛ ታይቶ ጠፊ ነን ። ሩቅ አስበን ቅርብ የምናድር ነን ። ለዓመት አቅደን ዛሬ ማታ የምንጠራ ነን ። ፈረንጆቹ፡- “ሰው ሲያቅድ እግዚአብሔር ይስቃል” ይላሉ ። በሰርግ ካርዶች ላይ ብንኖርና ጌታ ቢፈቅድ የሚል ቃል ሰፍሮ ብዙ ጊዜ ይነበባል ። ሰርግ ይደገሳል ግን ብንኖር ነው ። ወረቀት ይበተናል ግን ብንኖር ነው ። ሚዜዎች ይለማመዳሉ ግን ብንኖር ነው ። ከወር በኋላ የሚያገቡ በአደጋ ሞተዋል ። በሙሽርነት ቀናቸው የሞቱ አያሌ ናቸው ። ለደስታ የተተኮሰ ጥይት ሙሽሮችን ገድሏል ። የሰርጉ ድግስ የሬሳ መሸኛ ይሆናል ። እኛ በጣም ደካማዎችና ከእግዚአብሔር ፈቃድ በቀር ምርኩዝ የሌለን አፈር ነን ።
የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አባት ራስ መኰንን ከግዛታቸው ከሐረር ወደ አዲስ አበባ ተጠርተው ሊመጡ ሲሉ የታያቸው ነገር ነበርና “ልጄን ተፈሪን አደራ” አሉ ። ወዳጆቻቸውም ልባቸው ስለ ፈራ፡- “መቼ ይመለሳሉ?” አሏቸው ። ራስ መኮንንም፡- “ስለመሄዴ እንጂ ስለመመለሻ ጊዜዬ አላውቅም” አሉ ። ጥቂት ጉዞ እንደ ጀመሩ ቁልቢ ላይ ታመው እዚያው ሞቱ ። ስለመውጣታችን እንጂ ስለመመለሳችን የሚያውቅ እግዚአብሔር ብቻ ነው ። እኛ አፈርና ትቢያ ነን ። ተንጠራርተን የምንናገር ሳይሆን ትሑት ሁነን ለአምላክ ክብር መስጠት የሚገባን ነን ።
የዓመታት ዘመናት ፈጣሪ እግዚአብሔር ሆይ ጊዜም ሎሌህ ነውና እናመሰግንሃለን ። በጊዜ ውስጥ ልደትና ሞትን ፣ ክብርና ዝቅታን የምታፈራርቅ ፣ ጊዜን መንበርህ መፍረጃህ አድርገህ ስንት የምታሳየን ጌታ ተመስገን ። በሰጠኸን ዕድሜ አንተን አስደስቶ ማለፍ ይሁንልን ። ሥጋችንን ቀድስ ፣ ነፍሳችንን አሳርፍ ። ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለቱ መና 24
ግንቦት 24 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም