መግቢያ » ትረካ » የጌርጌሴኖን ታማሚ » የጌርጌሴኖን ታማሚ

የትምህርቱ ርዕስ | የጌርጌሴኖን ታማሚ

ማር. 5፡1-20
በጥብርያዶስ ባሕር በስተደቡብ ምሥራቅ በምትገኘው በጌርጌሴኖን ከተማ ወደብ ላይ ታንኳዋ ረጋች ። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የመንግሥቱን አዋጅ የተራራውን ስብከት ካሰማ በኋላ ለምጻም በማንጻት ፣ በሽተኞችን በመፈወስ ፣ማዕበልን በመገሠጽ ታላላቅ ተአምራትን ፈጽሟል ። ከጤነኞች ሠፈር ፣ ከባለጠጎች ገበታ ፣ ከሹማምንት ቢሮ እስካሁን አልተገኘም ። ድሆችንና ምስኪኖችን እየረዳ ይጓዝ ነበር ። በዱር የተጣለውን ወደ እርሱ አቅጣጫ እየሄደ ያገኘው ነበር ። ያ የዱር ነዋሪ በአጋጣሚ ክርስቶስን ያገኘ ይመስለው ነበር ፣ እርሱ ግን ሥራውን የሚሠራው ለአጋጣሚ የሚሆን ምንም ክፍተት ሳይሰጥ ነው ። ሰው እንዳይቀርባቸውና እንዳይረክስ ይሸሹ የነበሩ ለምጻሞችና ድሪቷሞች እርሱ ግን እንዲዳስሳቸው ቀርበውታል ። ቅድስናው የሚገፈትር ሳይሆን የሚያቅፍ ነበር ። የገዛ መልካቸው የጠፋቸው ራሳቸውን በእርሱ መልሰው አግኝተዋል ። በጓዳ ያለውን ጉድለት ያውቅ ነበር ። ሰዎች በአልጋቸው ሁነው ሲያቃስቱ እርሱ ያንን ድምፅ ይሰማ ነበር ። ላልፈለጉት እየተገኘ ፣ ላልጠሩት እየተገለጠ ብዙ ማዳን አደረገ ። እስኪፈልጉትና እስኪጠሩት ቢጠብቅ እስከ ዛሬ አንድ ሰውም አይድንም ነበር ። ደቀ መዛሙርቱም ለእነ እገሌ ብዙ ተደረገ እያሉ እንዳያስቡ በማዕበል ሲጨነቁ ከሞት አዳናቸው ። የነበራቸውን ዘመን ሳይሆን ያለቀውን ዘመናቸውን ክርስቶስ እንደፈለገውና እንደ ከበረበት አስተውለዋል ። “ዘመኔን ሰጥቼው” እያሉ እንዳይፎክሩ ሞት ካደባበት ዘመናቸው ጀመረ ።

ጌርጌሴኖን ልባቸው ጠንካራ የሆነ ፣ የሰው ዋጋ ያልገባቸው ፣ ክርስቶስን ናልን ሳይሆን ከከተማችን ውጣልን ብለው የሚለምኑ ሰዎች ያሉባት ከተማ ናት ። ጌርጌሴኖን ብዙ የአእምሮ በሽተኞችን የምታስተናግድ የጣር ከተማ ናት ። የሰው ዋጋ በወደቀባቸው ፣ ገንዘብ በዙፋን ተቀምጦ በሚገዛቸው ፣ ራስ ወዳድነት በነገሠባቸው ከተሞች ብዙ የአእምሮ ጭንቀት ይከሰታል ። እነዚህ ፍጹም አቅላቸውን የሳቱና አብደው በከተማ የሚዞሩ ፣ በመቃብር የሚኖሩ በሽተኞች በከተማው የታወቁ ናቸው ። የታወቁት ግን በበሽታቸው ብቻ ነበር ። እያሉ እንደሌሉ የተረሱ ቢሆኑም እነርሱም በኃይለኝነታቸው “አለን” ብለው በፍርሃት ሰዎችን ያስገዙ ነበሩ ። መፈራት ሥልጣን ቢሆን ኑሮ እነዚህ ሰዎች ባለሥልጣን ይባሉ ነበር ። ረጅም ምላሳቸው ተፈርቶ ዝም የሚባሉ ፣ ሌላውን እንዳይበጠብጡ እሺ እሺ የሚባሉ ፣ “ስለ ምጣዱ አይጧ ትለፍ” ተብለው የሚከበሩ በሽተኞች አሉ ። መፈራት ሥልጣን አይደለም ። ተወዶ መከበር ፣ ተከብሮ መፈቀር ለቀናዎች የተሰጠ ነው ።
አያልቅበት ጌታ አንዱን ተአምር አድንቀው ሳይፈጽሙ ሌላ ተአምር ያደርግላቸው ነበር ። በረሃ አቋርጦ ፣ ባሕር ተጋፍቶ የሚደርሰው ለእነዚህ ምስኪኖች ነው ። በቀትር የጨለመባቸው ፣ ከቆሙት ጋር ሳይሆን ከሞቱት ጋር ደባል የገቡ ብዙ አሉ ። ከሕያዋን ሰፈር ቦታ ያጡ ፣ የመቃብር ድንጋይ ላይ መሬት የተመሩ አያሌ አልቃሾችን ምድር ይዛለች ። በትዳር ቢኖሩ የመነኑ ፣ አጠገባቸው ያለው የማይረዳቸው ፣ ችግራቸው የስንፍናቸው ውጤት የመሰለባቸው ፣ የሚወዱትን አጥተው መራራን ለማጣጣም ራሳቸውን የሚያለማምዱ ፣ ጭንቀት የማይደክመው ጓደኛ ሁኖ ሌት ተቀን የሚያዋራቸው ፣ ችግር ጎረቤት ሁኖ የተጣበቃቸው ብዙ ተንከራታቾች አሉ ።ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ እነዚህን ፍለጋ ወደ ጌርጌሴኖን ሄደ ። ሰዎች ባሕር አቋርጠው የሚሄዱት ለመዝናናት ነው ፣ እርሱ ግን ፍቅርን ለመዝራት ባሕር አቋርጦ ሄደ ። ፍቅር በሰው ላይ እንጂ በመሬት ላይ የሚዘራ አይደለም ። ሰው መጥፎ ቢሆን እንኳ ፍቅርን የምንዘራበት የእግዚአብሔር ማሳ ነው ።
የሰው ልጅ በተለያየ ነገር አእምሮውን ይስታል ። ጨርቁን ጥሎ በከተማ ይዞራል ። አንዳንድ የአእምሮ በሽተኞች “አንተን እሾምሃለሁ ፣ ላንተ ሚሊዮን ብር እሰጣለሁ” ይላሉ ። እነዚህ ሰዎች ቢኖረኝ ለእገሌ ይህን አደርጋለሁ እያሉ ያስቡ የነበሩና ያ ችሮታ ምኞት ብቻ ሲሆንባቸው ያበዱ ናቸው ። የአቅማችንን ያህል ፣ አንዳንዴም ከአቅማችን በላይ ልናደርግ እንችላለን ። የራቀን ነገር በምኞት እያወረድን ለምንወዳቸው መነስነስ መጨረሻው አእምሮን ማጣት ነው ። “የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች” እንዲሉ ። አለመቀጠሉ እንጂ በቀን ሦስት ጊዜ የማያብድ ሰው ጥቂት ነው ። ሠራተኞች ሲለግሙብን ፣ ትዳራችን አላውቅልህ ሲለን ፣ ልጆቻችን በራሳቸው መንገድ ሲሄዱ ፣ ጎረቤት እንደ ጦስ ዶሮ ሲዞረን ፣ እኛ ለተሸከምነው ሰዎች የእኛ ችግር ሲከብዳቸው ፣ በሐሜት ጥሬ ሥጋችንን ሲበሉት ፣ በመውደቃችን የደስታ ድቤ ሲደልቁ ፣ የምናምነውን ነገር እንምረጥላችሁ ሲሉ ፣ አለመለመናችንና ኑሮዬ ይበቃኛል በማለታችን መቃብር ሲቆፍሩብን … በእነዚህ ነገሮች በቀን ውስጥ ብዙ ጊዜ እናብዳለን ። መለስ ብለን ደግሞ የተፈለገው እንዲህ እንድሆን አይደል ብለን ብልህ እንሆናለን ። መንፈሳዊነቱ እስቲመጣ ብልህ መሆንም ዕድሜን ያረዝማል ።
ከዚያ ባሻገር ሰዎች በርኩስ መንፈስ ተይዘው ሊያብዱና አቅላቸውን ሊስቱ ይችላሉ ። ሰይጣን በዋናነት የሚፈልገው የሰውን ማስተዋሉን መስረቅ ነው ።ሁሉ የአእምሮ ሕመም ግን ከአጋንንት አይደለም ። ከትንሹ ራስ ምታት ጀምሮ እያደገ የሚመጣ የአእምሮ ሕመም አለና ሰው ሁሉ ነጻ ላይሆን ይችላል ። ጨጓራ እየሠራ ስለሆነ ይታመማል ፣ ከጨጓራ ይልቅ ሥራ ያለበት አእምሮ ቢታመም የሚደንቅ አይደለም ። ልዩነቱ ግን ከጨጓራ ይልቅ ፈጥኖ የሚፈወስ አእምሮ መሆኑ ነው ። ስለ አእምሮ ታማሚዎች ለማወቅ ግን መጀመሪያ አእምሮ ያስፈልጋል ። በአንዳንድ ባሕል በሽታ ሰንጠረዥ አለው ። ይኼማ ይሻላል የሚል አስተሳሰብ አለ ። የባለጠጋ የድሀ ተብሎም በሽታ ክፍል ያገኘባቸው ባሕሎች የትየለሌ ናቸው ። ብቻ አጋንንት የለም የሚሉና ሁሉም ነገር ከአጋንንት ነው በሚሉ ይህች ዓለም ግራ ተጋብታለች ።
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ክብር ምስጋና ይግባውና ገና ከታንኳው ሲወርድ ርኩስ መንፈስ የያዘው አንድ ሰው ከመቃብር ወጥቶ ተገናኘው ። ይህ ሰው ከቆሙት በታች ከሞቱት በላይ ነው ። የመቃብር ስፍራ ሊያልፉበት የሚያስፈራ ፣ ነገ የሚጠብቀን ቢሆንም ማሰብ የማንፈልገው ዘላቂው ቤት ነው ። እግዚአብሔር ካልፈቀደ እንኳን መኖሪያ መቀበሪያም አይገኝም ። በባሕር የሰጠሙትን ፣ በአየር ላይ ተበትነው የቀሩትን ማሰብ ትምህርታችን ነው ። አንማርም እንጂ ። ሰው የወንድሙን መሞት ሲያምን የራሱን መሞት ግን አያምንም ። ባጭር ቋንቋ እኛ ተንቀሳቃሽ ሬሳ ነን ። ለሕይወታችን ክብረት የሚሰጠው የሞተውና የተነሣው ክርስቶስ ኢየሱስ ብቻ ነው ። መሬቴን ነካህብኝ እያልን እንጣላለን ። መሬት የሰው አይደለም ፣ ሰው ግን የመሬት ነው ። የምንረግጣት አፈር አንድ ቀን ትረግጠናለች ። የክርስቶስ ደም ዋጋ ባይሆነን ኑሮ እኛ ሰባና ሰማንያ ኪሎ አፈር ነን ።
ይህ ሰው የጌርጌሴኖኑ እብድ ነው ። ብዙ በሽተኞች ቢኖሩም የእርሱ ግን ለየት ያለ ነበረ ። ቢያንስ አራት ታላላቅ ችግሮች ነበሩበት ።
ይቀጥላል
ሰኔ 13 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ 
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም