መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » የጌታችን ጥምቀት

የትምህርቱ ርዕስ | የጌታችን ጥምቀት

እንኳን ለ2016 ዓ.ም. የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት በሰላም አደረሳችሁ!

ጌታችን ከሰማይ በትሕትና ወረደ ። የበላዮች ወርደው የሚያስተዳድሩትን ሕዝብ እንዲያዩ የነገሥታት ንጉሥ አርአያ ሆነ ። የሕዝብ ሁሉ ጥያቄ “ወርዳችሁ እዩን” የሚል ነው ። በስማ በለው ሕዝባቸውን የሚያነጋግሩ ለሕመሙ እውነተኛ መድኃኒት መስጠት አይችሉም ። የነገሥታት ፀሐፊዎች ወደ ቤታቸው በጊዜ ለመግባት ደግ ፣ ደጉን ብቻ ያወራሉ ። የጸጥታ ኃላፊዎች የት ነበራችሁ? እንዳይባሉ ሰላም ሳይሆን ሰላም ነው ይላሉ ። ጌታችን ወርደህ እየን ሳይሉት ወርዶ እንደሚያየን ተስፋ ሰጠ ። ተስፋውንም ፈጸመ ። እርሱ ለኑሮችን ሩቅና እንግዳ አለመሆኑን ገለጠ ። ጌታችን በዮርዳኖስ ተጠመቀ ። ጥምቀት ለእኛ እንጂ ለእርሱ ልጅነትን አያስገኝለትም ። በጥምቀቱ ልጅነቱ ተመሰከረ ። የወለደው አብ መሰከረ ።

ጌታችን የመሰወር ወራትን አደረገ ። ሠላሳ ዓመት ተሰወረ ። ብዙ መገለጥ የሚወድዱ ያለ ጊዜአቸው ይጨልማሉ ። በዝተንም እንዳንረክስ ፣ አንሰንም እንዳንረሳ ከሰዎች ጋር በወጉ መገናኘት ይገባል ። ሰው በር ቢዘጉ ጠንቋይ ነው ይላል ፣ በር ቢከፍቱ ዟሪ ነው ይላል ። ቢያቀርብ ክብሩን አይጠብቅም ይባላል ። ቢያርቅ አውሬ ነው ይሉታል ። የመሰወር ወራትን ማክበር ግን ያለ ጊዜው ከመሞት ይጋርዳል ። ጌታችን በሠላሳ ዓመቱ ተገልጦ በ33 ዓመቱ ሞተ ። በዚህ መሠረት በ15 ዓመቱ ቢገለጥ በ18 ዓመቱ ሊገድሉት ይነሣሡ ነበር ።

ጌታችን ሠላሳ ዓመት ቅድስት እናቱን አገለገለ ። ሠላሳ ዓመት ከሕዝብ ማንነቱን ሰወረ ። ይልቁንም ላለፉት 18 ዓመታት በናዝሬት እንደ ተራ ሰው ኖረ ። የናዝሬት ነዋሪዎችም አልጠረጠሩትም ። በእውነት ወርዷልና ፣ በእውነት ታዝዟልና ። መጥረጊያ ይዘው የሚታዩ ባለሥልጣናት ፣ አቧራ የሚያጸዱ የበላዮች በእውነት ወርደው እንደሆነ አይታወቅም ። ቀጥለው በወርቅ ዙፋን እንደሚቀመጡ ይታወቃል ። ለቆፈረ እጃቸው የሐር መከዳ ይደረግላቸዋል ። ጭቃ ላልነካ እጃቸው ወንዝ ጠልፈን እናስታጥብ የሚል ይበዛላቸዋል ። ክርስቶስ ግን በእውነት ወርዶ ፣ በእውነት ታዝዞ ነበርና የናዝሬት ሰዎች አላወቁትም ። የምድር ገዥዎች ሌላውን ለማነሣሣት ለሠላሳ ደቂቃ መጥረጊያ ይይዛሉ ፣ ጌታችን ግን ሠላሳ ዓመት ሁሉን ታዘዘ ። በእውነት እንድንወርድ ፣ በእውነት ዝቅ እንድንል ይህ በዓል ያስተምረናል ። የጠላትነት ሁሉ መንስኤው አለመውረድ ነው ። አለመታዘዝ ነው ።

በዓሉን በባሕል ሳይሆን በአምልኮ ልብ ማክበር ይገባል። ቀኑ የተነሣሕያን ቀን እንጂ ኃጢአት የሚጨምሩበት ቀን አይደለምና ተራ ነገሮችን እናርቅ !

ይቀጥላል

በዓለ ጥምቀቱን የሰላም ያድርግልን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 10 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም